Popular Posts

Wednesday, May 9, 2018

የዋናተኛው ታሪክ

እግዚአብሄር ክቡር ነው፡፡ እግዚአብሄርን ማወቅ ርካሽ አይደለም፡፡ እግዚአብሄርንብ በየመንገዱ አንረዳውም፡፡ እግዚአብሄርን ማወቅ የሚጠይቃቸው ነገሮች አሉ፡፡
እግዚአብሄር ርካሽ እየደለም፡፡ እግዚአብሄር በመጀመሪያው ቀን ራሱን አያፈስልንም፡፡ እግዚአብሄር አንድ ነገር ያሳየንና ምላሻችንን ይጠብቃል፡፡ እግዚአብሄር ራሳችንን በሰጠነው መጠን ብቻ ነው ራሱን የሚሰጠን፡፡
የእግዚአብሔር ክብር ነገርን መሰወር ነው፤ የነገሥታት ክብር ግን ነገርን መመርመር ነው። ምሳሌ 25፡2
እግዚአብሄር በድንገት አይታወቅም፡፡ ሰው ካላረፈ እግዚአብሄርን አያውቀውም፡፡ እግዚአብሄርን ለማወቅ ውሳኔ ይጠይቃል፡፡ እግዚአብሄርን ለማወቅ ትጋት ይጠይቃል፡፡ እግዚአብሄርን ለማወቅ አንድ ሃሳብነት ይጠይቃል፡፡
እናንተ ትሹኛላችሁ፥ በፍጹም ልባችሁም ከሻችሁኝ ታገኙኛላችሁ። ኤርምያስ 29፡13
እግዚአብሄር ሁልጊዜ በህይወታችን መስራት ይፈልጋል፡፡ ነገር ግን የሚሰራው እኛ ስናርፍ ነው፡፡ እኛ ከተቅበዘበዝንና ካላረፍን እርሱ መስራት አይፈልግም፡፡ እኛ እየተቅበዘበዝንና እየተወራጨን ቢሰራም እግዚአብሄር የሰራ አይመስለንም፡፡ እኛ እየተቅበዘበዝንና እየተወራጨን ቢሰራ ክብሩን እኛ እንጂ እርሱ አይወስድም፡፡
ዕረፉ፥ እኔም አምላክ እንደ ሆንሁ እወቁ፤ በአሕዛብ ዘንድ ከፍ ከፍ እላለሁ፥ በምድርም ላይ ከፍ ከፍ እላለሁ። መዝሙር 46፡10
ለዚህ ነው እግዚአብሄር የስጋ ሃይላችንን አስክንጨርስ የሚጠብቀን፡፡ ለዚህ ነው ከስጋ ሃይላችን ጋር ሃይሉን ማቀላቀል የማይፈልገው፡፡ ለዚህ ነው እርሱን እንድንለይውና እንድንቀድሰው ከምንም ነገር ጋር እንዳናቀላቅለው የሚፈልገው፡፡
ዳሩ ግን ጌታን እርሱም ክርስቶስ በልባችሁ ቀድሱት። በእናንተ ስላለ ተስፋ ምክንያትን ለሚጠይቁአችሁ ሁሉ መልስ ለመስጠት ዘወትር የተዘጋጃችሁ ሁኑ፥ ነገር ግን በየዋህነትና በፍርሃት ይሁን። 1ኛ ጴጥሮስ 3፡15
ታዋቂው የመፅሃፍ ቅዱስ አስተማሪው ዎች ማን ኒ ክርስትና እንዲህ ነው ተብሎ ወደ አማርኛ በተተረጎመው The Normal Christian Life በሚለው መፅሃፋቸው ላይ በመንፈስ ቅዱስ ላይ እንዴት መደገፍ እንዳለብን ሲፅፉ አንድን ታሪክ ይናገራሉ፡፡ 
በድሮ ጊዜ ሰውነታችንን የምንታጠበው ወንዝ ወርደን ነበር፡፡ አንድ ጊዜ አንዱ ዋና የማይችል ጓደኛችን ውሃ ውስጥ ይወድቃል፡፡ አንድ ሌላ ጓደኛችን ዋና ይችል ስለነበር አውጣው ብለን ጮኽን፡፡ እሱ ግን ፈጥኖ አላወጣውም ነበር፡፡ ቶሎ አውጣው ብለን በጣም ብንጮኽም ረጋ ይል ነበር፡፡ ከዚያም በኋላ ግን ውሃ ውስጥ ገብቶ አወጣው፡፡ በኋላ በጣም ተገርመን ምን ሆነህ ነበር ወዲያው ያላወጣኸው? ብለን ጠየቅነው፡፡ እርሱ ሲመልስ እኔ ውሃ ውስጥ የወደቀ ጊዜ ወዲያው ላወጣው ውሃ ውስጥ ብገባ እስከ ሙሉ ጉልበቱ ስለነበር እኔም ላይ ይጠመጠምና እንዳልዋኝ እንቅ አድርጎ ይዞኝ እኔም እርሱም ልንሞት እንችል ነበር፡፡ ቆየት ካለ በኋላ በራሱ ሞክሮ ከደከመ በኋላ ግን በቀላሉ አወጣሁት በማለት አስረዳቸው፡፡
እኛም ካላረፍን በራሳችን ጉልበት እንደምናደርገው ካሰብን እግዚአብሄር አይገባበትም፡፡ ለእግዚአብሄር ስፍራ ልንሰጠው ይገባል፡፡ እግዚአብሄር እንዲሰራ እኛ ልናርፍ ይገባል፡፡
ተወዳጆች ሆይ፥ ራሳችሁ አትበቀሉ፥ ለቍጣው ፈንታ ስጡ እንጂ፤ በቀል የእኔ ነው፥ እኔ ብድራቱን እመልሳለሁ ይላል ጌታ ተብሎ ተጽፎአልና። ሮሜ 12፡19
እኛ ስንጨርስና ስናርፍ እርሱ ይጀምራል፡፡ እኛ ስናርፍ እርሱ ይሰራል፡፡
የእስራኤል ቅዱስ፥ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላልና፦ በመመለስና በማረፍ ትድናላችሁ፤ በጸጥታና በመታመን ኃይል ይሆንላችኋል፤ ኢሳያስ 30፡15
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ክርስቶስ #ጌታ #እረፍት #ቅድሚያ #እምነት #እውቀት #መደገፍ #ሰንበት #በመንፈሴ #በሃይል #በብርታት #ፀጥታ #መመለስ #ማረፍ #ፅድቁን #ኢየሱስ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #ፀጥታ #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #መታመን #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment