Popular Posts

Friday, October 13, 2023

የዝምታ ጥበ

 


የተፈጠርነው ለእግዚአብሔር ክብር ነው፡፡ የተፈጠርነው እግዚአብሔርን እንድንከተል ነው፡፡ የተፈጠርነው እርሱን እንድናመልክ እና እንድናገለግለው ነው፡፡

ታዲያ እንዴት እንደምናገለግለው የሚወስነው እርሱ እንጂ እኛ አይደለንም፡፡ የእኛ ድርሻ እርሱን መስማት እና በቅርበት መከተል ብቻ ነው፡፡ እርሱን ለማስደሰት እርሱን በየእለቱ እና በየሰአቱ መስማት እና መከተል አለብን፡፡

እርሱ ሲነሳ አብረን ልንነሳ ፣ እርሱ ሲራመድ አብረን ልንራመድ ፣ እርሱ ዝም ሲል አብረን ዝም ልንል እንዲሁም እርሱ ሲናገር አብረን ልንናገር ለእርሱ ክብር እንኖራለን፡፡

ለራሳችን ምኞት እና ፍላጎት ሞተናል፡፡ ለራሳችን አላማ እና ግብ ሞተናል፡፡ ለራሳችን ጥበብ እና ማስተዋል ሞተናል፡፡

ህያው የሆንነው ለእርሱ ምኞት እና ፍላጎት ብቻ ነው፡፡ የእርሱ አላማን ለማሳካት በህይት እንኖራለን፡፡ በእርሱ ጥበብና መስተዋል ብቻ ላይ እንደገፋለን፡፡

እርሱ አላማውን የሚያስብበት የእርሱ አእምሮ ነን፡፡ እርሱ ፍላጎቱን የሚፈፅምበት የእርሱ እጅ ነን፡፡ እርሱ የሚጓዝበት የእርሱ እግር ነን፡፡ እርሱ የሚናገርነት የእርሱ አፍ ነን፡፡

እርሱ የሚኖርብን እንደመሆናችን መጠን እርሱ ሲነሳ እንነሳለን፡፡ እርሱ ሲራመድ አብረንው እንራመዳለን፡፡ እርሱ ሲያርፍ ደግሞ አብረነው እናርፋለን፡፡

እርሱ ሲራመድ አብረን መራመድ እንደሚያስፈልገን ሁሉ እርሱ ሲያርፍ አብረን ማረፍ ግዴታችን ነው፡፡ እርሱ ሲናገር አብረን ለመናገር እንደምንወስነው ሁሉ እርሱ ዝም ሲል ባይገባንም አብረነው ዝም ለማለት መጨከን አለብን፡፡ እርሱ ሲራመድ በደስታ አብረነው እንደምንራመድ ሁሉ እርሱ ቁጭ ሲል አብረነው መቀመጥን መለማመድ አለብን፡፡

ከክርስቶስ ጋር ተሰቅዬአለሁ፤ እኔም አሁን ሕያው ሆኜ አልኖርም ክርስቶስ ግን በእኔ ይኖራል፤ አሁንም በሥጋ የምኖርበት ኑሮ በወደደኝና ስለ እኔ ራሱን በሰጠው በእግዚአብሔር ልጅ ላይ ባለ እምነት የምኖረው ነው። ወደ ገላትያ ሰዎች 2፡20

አቢይ ዋቁማ ዲንሳ  Abiy Wakuma Dinsa

ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #እምነት #ልብ #ማመን #ቃል #ክርስቶስ #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ማሰላሰል #ማድረግ #መከተል #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ                                     


Wednesday, October 11, 2023

የፓለቲከኝነት ሙያ

ፖለቲካ የአገር አስተዳደር ሙያ ነው፡፡ ማንኛውም ሙያ በመልካም ሰው እጅ በአግባብ እንደሚያዝ ሁሉ ፖለቲካም ለህዝብ ጥቅም በአግባብ ሊያዝ ይችላል፡፡ ፖለቲከኝነት ብቻ ሳይሆን ማንኛውም ሙያ ደግሞ አላግባብ እንደሚያዝ ሁሉ ፖለቲካም አላግባብ ሊያዝ ይችላል፡፡

ብዙ ጊዜ ፖለቲካን ከክፋት ፣ ከውሸት ፣ ከማጭበርበር እና ከራስ ወዳድነት ጋር ብቻ እናያይዘዋለን፡፡ እውነት ነው ሁሉም አይሁኑ እንጂ ክፉ ፣ ውሸታም ፣ አጭበርባሪ ፣ ራስ ወዳድ ፖለቲከኞች አሉ፡፡

ነገር ግን ደግሞ ህዝብን በቅንነት የሚያገለግሉ መልካም ፣ እውነተኛ ፣ የሚያገለግሉትን ህዝብ የሚወዱ ብዙ ፖለቲከኞች አሉ፡፡

ፖለቲከኝነት ስለአንድ አገር ወይም ህዝብ ባለ ራእይነት ይጠይቃል፡፡ አንድ ፖለቲከኛ ህዝብ እንዴት በሰላም እንደሚተዳደር እና ወደ ስኬት እና ብልፅግና እንደሚደርስ የሚታየው ሰው መሆን አለበት፡፡ አንድ አገር ወይም ህዝብ እንዴት እንደሚተዳደር ፣ በሰላም እንደሚኖር ፣ እንደሚሰራ እና እንደሚያድግ ማቀድ ፣ መመሪያ ማውጣት ብሎም ህዝብን ማስተማር እና ማንቀሳቀስ የአንድ ፖለቲከኛ ሃላፊነት እና ሸክም ነው፡፡

እግዚአብሔር ህዝብን ስለሚወድ መልካም ፍትሃዊ ፖለቲከኞችእን ይሰጣል፡፡ ሰይጣን ደግሞ አለማው መስረቅ ማደር እና ማጥፋት ስለሆነ ፖለቲከኛ ሰዎችን ስግብግብ ክፉ ለህዝብ ሰላምም ይሁን ብልፅግና ግድ የሌላቸው ሊያደርጋቸው ይጥራል፡፡

ንጉሥሽ ሕፃን የሆነ፥ መኳንንቶችሽም ማልደው የሚበሉ፥ አንቺ አገር ሆይ፥ ወዮልሽ! ንጉሥሽ የከበረ ልጅ የሆነ፥ ለብርታት እንጂ ለስካር ያይደለ በጊዜ የሚበሉ መኳንንት ያሉሽ፥ አንቺ አገር ሆይ፥ የተመሰገንሽ ነሽ። መጽሐፈ መክብብ 10፡16-17

አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa

#ኢየሱስ #ጌታ #ፖለቲካ #አስተዳደር #መመሪያ #ወንጌል #ቅዱስመንፈስ #ቤተክርስቲያን #መፅሐፍቅዱስ #ቃል #እግዚአብሔር #ሀገር #ንጉስ #ክርስቶስ


 

Saturday, October 7, 2023

ባህልና ሃይማኖት

 

ባህል የአንድ የተወሰነ ህዝብ ወይም ማህበረሰብ ሀሳቦች፣ ልማዶች እና ማህበራዊ ባህሪ መገለጫ እንደሆነ ኦክስፎርድ መዝገበ ቃላት ይናገራል።

ባህል በጣም ጠቃሚና እንደ ህብረተሰብ የህይወትን ተግዳሮት ተቋቁሞ ለማለፍ አስፈላጊ ነገር ነው፡፡

ባህል እና ሃይማኖት ፈፅሞ የተለያዩ አይደሉም፡፡ ባህል ደግሞ ብዙውን ጊዜ ከሃይማኖት ጋር ይቀላቀላል፡፡ ባህል ከሃይማኖት ጋር ሲቀላቀል የባህሉ ባለቤት ህብረተሰብ ሃይማኖትን እንደባህል እንዲወሰድ እና ተቀባይነት እንዲኖረው ተፅእኖ ያደርጋል፡፡

በዚህ ተፅእኖ ውስጥ ወድቀን የትኛውም ባህል ከሃይማኖት ከበለጠንም ባህሉ ራሱ ሃይማኖት ሆኖብናል ማለት ነው፡፡ ተቀባይነት ያላቸው ባህሎች በሃይማኖት ተቀባይነት ያላቸው ባህሎች ብቻ ናቸው፡፡ በሃይማኖት ተቀባይነት የሌላቸው ባህሎች በሃይማኖተኛው ዘንድ ተቀባይነት ሊኖራቸው አይገባም፡፡

ክርስትና ከሃይማት ጋር የተገናኙትን ባህሎች አይቀበልም፡፡ ክርስትና የሚቀበላቸው እና የማይቀበላቸው ባህሎች አሉ፡፡ ክርስትና የሚቀበለው ከመፅሃፍ ቅዱስ ጋር የማይጋጨውን ባህል ብቻ ነው፡፡ ባህልን ለመቀበል እና ለመጣል ከመፅሃፍ ቅዱስ ጋር መሄዱ ወይም አለመሄዱን በመመልከት ነው፡፡

ከሃይማኖት ጋር የማይጋጩ ባህሎችን መከተል እንደ ህብረተሰብ ወሳኝ ነው፡፡ አንድ ሰው ባህሉን መውደድ ምንም ችግር የለውም፡፡ ባህሉ ከባህልነት ድንበር አልፎ ሃይማኖት ውስጥ ከገባ ግን ተቀባይነት ያጣል፡፡

ለምሳሌ በክርስትና ስለባህል ብሎ ስለሃጢያታችን በመስቀል ላይ ደሙን ያፈሰሰውን ክርስቶስ ኢየሱስን የማያከብር መንፈስን መከተል አደገኛ ነው፡፡  ባህሉን ስለወደድን ብቻ ከመንፈስ ቅዱስ የተለየ መንፈስን ማክበር በእሳት እንደመጫወት አደገኛ ነገር ነው፡፡

ከመፅሃፍ ቅዱስ ጋር የሚጋጭ ሌላን መንፈስ ወደ ማምለክ እና ወደ መከተል ከሚመራ ባህል ውጭ ያለው ማንኛውም ባህል ሁሉ መልካም ነው፡፡

አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa

#ኢየሱስ #ጌታ #ባህል #ሃይማኖት #መንፈስ #ወንጌል #ቅዱስመንፈስ #ቤተክርስቲያን #መፅሐፍቅዱስ #ቃል #እግዚአብሔር #መስቀል #ሰይጣን #ክርስቶስ



Thursday, October 5, 2023

ሁለቱ አይነት መንፈሶች

 

በአለም ላይ ብዙ የመንፈስ አሰራሮች ቢኖሩም ግን በአለም ላይ በዋነኝነት ሁለት አይነት መንፈሶች ብቻ ይገኛሉ፡፡ ሁለቱ አይነት መንፈሶች የእግዚአብሔር መንፈስ እና የሰይጣን መንፈስ ናቸው፡፡ ከሁለቱ መንፈሶች ውጭ ያለ ገለልተኛ መንፈስ የለም፡፡ የእግዚአብሔር መንፈስ ካልሆነ የሰይጣን መንፈስ ነው፡፡ የሰይጣን መንፈስ ከሆነ የእግዚአብሔር መንፈስ አይደለም፡፡

ወዳጆች ሆይ፥ መንፈስን ሁሉ አትመኑ፥ ነገር ግን መናፍስት ከእግዚአብሔር ሆነው እንደ ሆነ መርምሩ፤ ብዙዎች ሐሰተኞች ነቢያት ወደ ዓለም ወጥተዋልና።1 የዮሐንስ መልእክት 4፡1

መንፈስ ወይም ከእግዚአብሔር ወይም ደግሞ ከሰይጣን ነው፡፡ ልእለ ተፈጥሮአዊ ብቻ ስለሆነ አንድን የመንፈስ አሰራር ከእግዚአብሔር ከመሰለን እንስታለን፡፡ ከተፈጥሮ በላይ የሆነ ነገር ግን ከእግዚአብሔር ያልሆነ አሰራር አለ፡፡ ከተፈጥሮ በላይ የሆነ ነገር ግን ከእግዚአብሔር ያልሆነው ሁሉ ከሰይጣን የሆነ አሰራር ነው፡፡ በልእል ተፈጥሮ ሃይል የሚሰራ ቅዱስ እና ክፉ መንፈስ አለ፡፡ ማንኛውም ድንቅ ታእምር በቅዱስ መንፈስ ካልተደረገ የተደረገው በሰይጣን መንፈስ ነው ማለት ነው፡፡

ሲሞን የሚሉት አንድ ሰው ግን፦ እኔ ታላቅ ነኝ ብሎ፥ እየጠነቈለ የሰማርያንም ወገን እያስገረመ ቀድሞ በከተማ ነበረ። ከታናናሾችም ጀምሮ እስከ ታላላቆቹ ድረስ፦ ታላቁ የእግዚአብሔር ኃይል ይህ ነው እያሉ ሁሉ ያደምጡት ነበር።ከብዙ ዘመንም ጀምሮ በጥንቈላ ስላስገረማቸው ያደምጡት ነበር። የሐዋርያት ሥራ 8፡9-11

በሽታንም ፈወሰ ፣ መስተፋቅር አሰራም ፣ የሰውን ሚስጥር ተናገረም ፣ ልጅ ትምህርት እንዲገባውም አስደረገ በእግዚአብሔር መንፈስ ካላደረገው ያደረገው በሰይጣን መንፈስ ነው ማለት ነው፡፡ የሚሰራው ታእምር በልእለ ተፈጥሮ ሃይል ስለሆነ ሊያስደንቅ ይችላል ነገር ግን ሰውየው ከእግዚአብሔር ነው ወይም የሚሰራው በእግዚአብሔር መንፈስ ሃይል ነው ማለት አይደለም፡፡

ጴጥሮስ ጠንቋዩ ስምኦን በሰይጣን አስራት ውስጥ እንደነበረ የሚናገረው ስለዚህ ነው ፡፡

እስራት   በመራራ መርዝና በዓመፅ እስራት እንዳለህ አይሃለሁና፡፡ የሐዋርያት ሥራ 8፡23

እንግዲህ ስለዚህ ክፋትህ ንሰሐ ግባ፥ ምናልባትም የልብህን አሳብ ይቅር ይልህ እንደ ሆነ ወደ እግዚአብሔር ለምን፤ የሐዋርያት ሥራ 8፡22

አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa

#ኢየሱስ #ጌታ #መንፈስ #ክፉመንፈስ #ወንጌል #ቅዱስመንፈስ #ጥንቆላ #ቤተክርስቲያን #መፅሐፍቅዱስ #ቃል #እግዚአብሔር #መስቀል #ሰይጣን #ክርስቶስ