Popular Posts

Wednesday, October 30, 2019

ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል?


ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ፥ ወይስ ጭንቀት፥ ወይስ ስደት፥ ወይስ ራብ፥ ወይስ ራቁትነት፥ ወይስ ፍርሃት፥ ወይስ ሰይፍ ነውን? ወደ ሮሜ ሰዎች 8፡35

Sunday, October 27, 2019

ሰላም ለእናንተ ይሁን የሉቃስ ወንጌል 24፡36

ሰላም ለእናንተ ይሁን
የሉቃስ ወንጌል 24፡36

Thursday, October 24, 2019

ወደሚቀጥለው የህይወት ምዕራፍ መሸጋገሪያ ጥበብ



እያንዳንዳችን ማደግ መለወጥ ወደሚቀጥለው የህይወት ምእራፍ መሸጋገር እንፈልጋለን፡፡ በህይወት ላለ ሰው ይህ ፍላጎት የጤነኛ ሰው ፍላጎት ነው፡፡
ወንድሞች ሆይ፥ እኔ ገና እንዳልያዝሁት እቈጥራለሁ፤ ነገር ግን አንድ ነገር አደርጋለሁ፤ በኋላዬ ያለውን እየረሳሁ በፊቴ ያለውን ለመያዝ እዘረጋለሁ፥ በክርስቶስ ኢየሱስ ከፍ ከፍ ያለውን የእግዚአብሔርን መጥራት ዋጋ እንዳገኝ ምልክትን እፈጥናለሁ። ወደ ፊልጵስዩስ ሰዎች 3፡13-14
ነገር ግን ወደሚቀጥለው ምእራፍ መሻገር ወደሚቀጥለው ምእራፍ ለመሻገር እንደመፈለግ ቀላል አይደለም፡፡ ወደሚቀጥለው ምእራፍ በጥንቃቄ ለመሻገር ጥበብ ይጠይቃል፡፡  
ሰው በፍሬያማነት ወደ ሚቀጥለው ምእራፍ የሚሻገርበትን መጽፅሃፍ ቅዱሳዊ ጥበብ እንመልከት
1.      ለእግዚአብሄር አላማ ጊዜ አለው
እግዚአብሄር ለህይወታችን ሙሉ እቅድ አለው፡፡ እኛ በፈለግንበት ጊዜ ወደ ሚቀጥለው ምእራፍ መሸጋገር አንችልም፡፡ እግዚአብሄር የህይወት እቅዳችንን በትጋት በጊዜው እየሰራው ነው፡፡ ወደሚቀጥለው የህይወት ምእራፍ ለመሻገር ማድረግ የምንችለው ነገር ባለንበት ምእራፍ ላይ ታማኝ ሆነን የምእራፍ መለወጫውን ጊዜ መጠበቅ ብቻ ነው፡፡
ለሁሉ ዘመን አለው፥ ከሰማይ በታችም ለሆነ ነገር ሁሉ ጊዜ አለው። ለመወለድ ጊዜ አለው፥ ለመሞትም ጊዜ አለው፤ ለመትከል ጊዜ አለው፥ የተተከለውንም ለመንቀል ጊዜ አለው፤ መጽሐፈ መክብብ 3፡1
2.     ባለንበት ምእራፍ መቆየት
እግዚአብሄር ሁኔታዎችን ሁሉ እስኪመቻች ባለንበት ምእራፍ እንደመቆየት የመሰለ ቦታ የለም፡፡ እግዚአብሄር እንድትለውጥ እስካልመራህ ድረስ ስታደርግ የቆየኸውን እንደማድረግ ምቹ ቦታ የለም፡፡ እግዚአብሄር ሳይልህ እርምጃ መውሰድ ብዙ ዋጋ የሚያስከፍል እርምጃ ነው፡፡ ስለወደፊቱ የህይወት ምእራፍህ ግልፅ ካልሆነ ጊዜው አይደለም ማለት ነው፡፡ ስለሚቀጥለው የህይወት ምእራፍህ አቅጣጫ ምሪት ካጣህ ካለምሪት ከመንቀሳቀስ ይልቅ ስታደርግ የቆየኸውን እንደማድረግ አስተማማኝ ነገር የለም፡፡
በእስያም ቃሉን እንዳይናገሩ መንፈስ ቅዱስ ስለ ከለከላቸው በፍርግያና በገላትያ አገር አለፉ፤ በሚስያም አንጻር በደረሱ ጊዜ ወደ ቢታንያ ይሄዱ ዘድን ሞከሩ፥ የኢየሱስ መንፈስም አልፈቀደላቸውም፤ የሐዋርያት ሥራ 16፡6-7
3.     ባለንበት ምእራፍ መትጋት
ወደሚቀጥለው ምእራፍ የምንሻገረው እንደው ወደሚቀጥዐው ምእራፍ ለመሻገር ብለን ብቻ አይደለም፡፡ ወደሚቀጥለው ምእራፍ የምንሸጋገረው የእግዚአብሄርን አላማ በሚቀጥለው ምእራፍ ውስጥ የእግዚአብሄርን አላማ ለማስፈፀም ነው፡፡ ወደ ሚቀጥለው ምእራፍ በስኬት መሸጋገር የምንችለበት አንደኛው መንገድ ያለንበትን ምእራፍ በትጋት በመጨረስ ነው፡፡ በትጋት ካልጨረስነው ያለንበት የህይወት ምእራፍ ወደሚቀጥለው ምእራፍ አይለቀንም፡፡
ስለዚህ እኔ ከሰው ሁሉ ደም ንጹሕ እንደ ሆንሁ ዛሬ በዚች ቀን እመሰክርላችኋለሁ። የእግዚአብሔርን ምክር ሁሉ ነግሬአችኋለሁና፥ ምንም አላስቀረሁባችሁም። የሐዋርያት ሥራ 20፡26-27
ያለንበት የህይወት ደረጃ ራሱ ትልቅ ግብ ነው፡፡ ስለዚህ ወደሚቀጥለው ለመሻገር እየሰራን ስለአሁኑ እግዚአብሄርን ማመስገንና የአሁኑን ማክበር ለሚመጣው እንድንታጭ ያደርገናል፡፡
እንግዲያስ በዓመፃ ገንዘብ ካልታመናችሁ፥ እውነተኛውን ገንዘብ ማን አደራ ይሰጣችኋል? በሌላ ሰው ገንዘብ ካልታመናችሁ፥ የእናንተን ማን ይሰጣችኋል? የሉቃስ ወንጌል 16፡11-12
4.     የቆየንበትን የህይወት ምእራፍ ላይ በሩን አለመጠርቀም፡፡
የነበርንበት የህይወት ምእራፍ መርገም አይደለም፡፡ የነበርንበት የህይወት ምእራፍ ወደሚቀጥለው የህይወት ምእራፍ የማያስተላልፍ በር ነው፡፡ የነበርንበት የህይወት ምእራፍ ለሚቀጥለው የህይወት ምእራፍ የሚያዘጋጅ የዝግጅት ጊዜ ነው፡፡ ወደሚቀጥለው የህይወት ምእራፍ አለፍን ማለት ባለፈው የህይወት ምእራፍ በር ላይ ጠርቅመን እንወጣለን ማለት አይደለም፡፡ ወደሚቀጥለው የህይወት ምእራፍ በር ስንገባ ያለፈውን ምእራፍ በር ቀስ ብለን ዘግተን መውጣት አለብን፡፡ የነበርክበትን የህይወት ምእራፍ ማጣጣል የብስለት ማጣት ምልክት ነው፡፡ የነበርክበት የህይወት ምእራፍ መናቅ በአዲሱ የህይወት ምእራፍ እርግጠኛ እንዳልሆንክ የሚያሳይ የስጋት ምልክት ነው፡፡ ሰው ለዘመናት ሲጠጣበት የነበረውን ምንጭ ልክ ሊወጣ ሲል መጣላትና ውሃውነ ማደፍረስ ጤነኝነት አይደለም፡፡  
እነዚህም ጌታን ሲያመልኩና ሲጦሙ መንፈስ ቅዱስ፦ በርናባስንና ሳውልን ለጠራኋቸው ሥራ ለዩልኝ አለ። በዚያን ጊዜም ከጦሙ ከጸለዩም እጃቸውንም ከጫኑ በኋላ አሰናበቱአቸው። የሐዋርያት ሥራ 13፡2-3
5.     ያለፍንበት የህይወት ምእራፍ ሰዎችን መርዳት
እኛ ካለፈው የህይወት ምእራፍ ተሻገርን ማለት ሌሎች ሰዎች በቀድሞው ይህይወት ምእራፍ ውስጥ የሉም ማለት አይደለም፡፡ ላለፍንበት የህይወት ምእራፍ ሰዎች መራራት እና አብረናቸው መቆም የህይወትን ምእራፍ መለወጥን አስፈላጊነት በአግባቡ መረዳት ነው፡፡ ወደሚቀጥለው ምእራፍ የተሻገርነው ሌሎችን ለማሻገር እንደሆነ መርሳት የለብንም፡፡
ደግሞ የተሰጠኝን ጸጋ አውቀው፥ አዕማድ መስለው የሚታዩ ያዕቆብና ኬፋ ዮሐንስም እኛ ወደ አሕዛብ እነርሱም ወደ ተገረዙት ይሄዱ ዘንድ ለእኔና ለበርናባስ ቀኝ እጃቸውን ሰጡን፤ ድሆችን እናስብ ዘንድ ብቻ ለመኑን፥ ይህንም ደግሞ ላደርግ ተጋሁ። ወደ ገላትያ ሰዎች 2፡9-10
ከላፍንበት የህይወት ምእራፍ ሰዎች ጋር መጣላት ያሳንሰናል፡፡ ሰዎችን ባለመጣላት በመታገስ ወዳጆችን ይበልጥ እያፈራንና እያበዛን እንጂ በጥል እየቀነስን መሄድ አይገባንም፡፡
ወንድምህም ቢበድልህ፥ ሄደህ አንተና እርሱ ብቻችሁን ሆናችሁ ውቀሰው። ቢሰማህ፥ ወንድምህን ገንዘብ አደረግኸው፤ የማቴዎስ ወንጌል 18፡15
6.       በትጋትና በታማኝነት መጨረስ
ያለንበትን የህይወት ምእራፍ ለመረዳት ራሳችንን መስጠት ጥበብ ነው፡፡ ያለንበት አዲሱ የህይወት ምእራፍ አዲስ እድል እንጂ በራሱ ውጤት እንዳልሆነ አውቀን በትጋትና በታማኝነት ሩጫችንን መጨረስ ይጠበቅብናል፡፡
መልካሙን ገድል ተጋድዬአለሁ፥ ሩጫውን ጨርሼአለሁ፥ ሃይማኖትን ጠብቄአለሁ፤ 2ኛ ወደ ጢሞቴዎስ 4፡7
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.dinsa.37/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ጌታ #ኢየሱስ #ትጋት #ታማኝነት #ጊዜ #ፅናት #መጠበቅ #ምስጋና ##ሃሳብ #ቃል #እግዚአብሄር #ትጋት #መንፈስቅዱስ #ንስሃ #መለወጥ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #መጨረስ #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ 

Wednesday, October 23, 2019

ሰው ማርጀቱን የሚያውቀው



“አንድ ሰው ማርጀቱን የሚያውቀው በተስፋ መኖሩን ትቶ በትዝታ መኖር ሲጀምር ነው” የሚባል የተለመደ አባባል አለ፡፡
እውነተኛ አባባል ነው፡፡ ሰው ለመውጣትና ለመውረስ ሙሉ ጉልበትን ይዞ ልቡ ግን ካረጃ ምንም ሊያደርግ አይችልም፡፡ 
ኢያሱ ሊወርሰው የሚችለው ብዙ ምድር ቢኖርም ኢያሱ ግን ስላረጀ መውረስ እንደማይችል እግዚአብሄር ስለኢያሱ ሲመሰከር እንመለከታለን፡፡
ኢያሱም ሸመገለ በዕድሜም አረጀ እግዚአብሔርም አለው፦ አንተ ሸመገልህ፥ በዕድሜህም አረጀህ፤ ያልተወረሰች እጅግ ብዙ ምድር ገና ቀርታለች፤ መጽሐፈ ኢያሱ ወልደ ነዌ 13፡1
ሰው እድሜው እየጨመረ ሲሄድ በጥበብና በማስተዋል እያደገ ይሄዳል፡፡ ሰው በእድሜ እየጨመረ ሲሄድ በህይወት የሚሰራበትንና የማይሰራበትን መንገድ በልምድ ማወቅና መረዳት ይጀምራል፡፡ ሰው በእድሜ እየጨመረ ሲሄድ ጥፋት እየቀነሰ ልማት እየጨመረ ይሄዳል፡፡ ሰው በእድሜ ጥበብን በጨመረ መጠን ብክነት እየቀነሰ ውጤታማነትን እየጨመረ ይሄዳል፡፡  
ጠንካራ ምግብ ግን መልካሙንና ክፉውን ለመለየት በስራቸው የለመደ ልቡና ላላቸው ለፍጹማን ሰዎች ነው። ወደ ዕብራውያን 5፡14
ሰው የመጀመሪያዎቹ የክርስትና ህይወቱ ዋናው ፈተናው የእግዚአብሄርን አሰራር መረዳት ነው፡፡
ሰው በጌታ ቤት በእድሜ እየጨመረ ሲሄድ ክፉውንና መልካሙን ለመለየት ሰፊ ልምድን ያካብታል፡፡ ሰው በጌታ ቃል እየኖረ ሲሄድ እግዚአብሄርን ይበልጥ እያወቀ ከብዙ እስራቶች ነፃ እየወጣ ይሄዳል፡፡ ሰው ከእግዚአብሄርን ጋር በኖረ መጠን እግዚአብሄር የሚሰራበትንና የማይሰራበትን መንገድ በቀላሉ ስለሚረዳ ጌታን በቅርብ ለመከተል ይቀለዋል፡፡
ኢየሱስም ያመኑትን አይሁድ፦ እናንተ በቃሌ ብትኖሩ በእውነት ደቀ መዛሙርቴ ናችሁ፤ እውነትንም ታውቃላችሁ እውነትም አርነት ያወጣችኋል አላቸው። የዮሐንስ ወንጌል 8፡31-32
ሰው ከእግዚአብሄር ጋር ኖሮ ጌታ ኢየሱስን ተከትሎ የእግዚአብሄርን አሰራር መረዳት ሲጀምር ፈተናው የልብ እርጅና ፈተና ይሆናል፡፡ የእርጅና ፈተና የሚመጣው የእግዚአብሄር ቃል እንዴት እንደሚሰራ መረዳት ስንጀምር ነው፡፡
ስለእርጅና ስናወራ የምናወራው ስለእድሜ መጨመር አይደለም፡፡ የእድሜ መጨመረ ማንም ሊያመልጥበት የማይችል በምድር ላይ የሚኖር  ሰው ሁሉ እጣ ፈንታ ነው፡፡ እንዲያውም የሰው እድሜ መጨመር እግዚአብሄር እንደታገሰው የክብር ምልክት ነው፡፡
የሸበተ ጠጕር የክብር ዘውድ ነው፥ እርሱም በጽድቅ መንገድ ይገኛል። መጽሐፈ ምሳሌ 16፡31
እድሜያችን ሲጨምር ታዲያ የመውጣትና የመውረስ ፍላጎታችን እየጨመረ እንጂ በፍፁም እየቀነሰ መሄድ የለበትም፡፡
ስለእርጅና ስናወራ የምናወራው ከጊዜው በፊት ዋጋን የመክፈልና የመውረስ ፍላጎት ማጣትን እያወራን ነው፡፡ ስለእርጅና ስናወራ የምናወራው በመውረሻ ጊዜያችን ለመውጣት ፈቃደኛ አለመሆንንና የልብን መቀዝቀዝን ነው፡፡ ስለእርጅና ስናወራ የምናወራው ከጊዜው በፊት የልብን ፍላጎት ማጣትን ነው፡፡ ስለእርጅና ስናወራ የምናወራው ከጊዜው በፊት የልብን እሳት ማጣት እና አላግባብ ዋጋ ለመክፈል መሳሳትን ነው፡፡
ሰው እንዳይወጣ እንዳይወርስ በእድሜ ከመጨመሩ በላይ የሚፈታተነው የልብ እርጅና ነው፡፡ ሰው በመጀመሪያዎቹ ጌታን በተከተለባቸው አመታት ደስ ብሎት ለጌታ ዋጋን ይከፍላል፡፡ ሰው እየቆየ ሲሄድ ግን ለእግዚአብሄር ነገር ዋጋ ላለመክፈል ይፈተናል፡፡ ሰው እየቆየ ሲሄድ ሰው ከመጠን በላይ ለራሱ እየሳሳ ይሄዳል፡፡ ሰው እየቆየ ሲሄድ ራሱን አደጋ ላይ ላለመጣል "ሪስክ" ላለመውሰድ ይሳሳል፡፡ ሰው እየቆየ ሲሄድ በህይወቱ ከገጠመው ውድቀት አንፃር አዲስ ነገርን ለመሞከር ይበልጥ እይፈራ ይሄዳል፡፡ ሰው እየቆየ ሲሄድ ላለመጎዳት ከመጠን በላይ መጠንቀቅ ይጀምራል፡፡ ሰው እየቆየ ሲሄድ የምቾት ቀጠናውን ለመተው እምቢተኛ ይሆናል፡፡
በክርስትና ህይወትና አገልግሎት ደግሞ ስኬታማ የሚኮነው በእምነት ብቻ ነው፡፡ እምነት ደግሞ እግዚአብሄር ያለውን ሰምቶ ተጋላጭ የመሆን ወይም ሪስክ የመውሰድ ጉዳይ ነው፡፡ 
ሰው እግዚአብሄር ለመራው ነገር ዋጋ መክፈል ካቃተው በልብ እርጅና ተይዟል ማለት ነው፡፡ ሰው እግዚአብሄር ለመራው ነገር የሚከፍለው ዋጋ ከሚያገኘው ጥቅም ከበለጠበት በልብ እርጅና በሽታ እየተቃየ ነው ማለት ነው፡፡  
እግዚአብሄር የእስራኤልን ህዝብ የገባላቸውን የተስፋ ምድር ተዋግቶ እንዲያስወርስ ለመላክ አልቻለም ነበር፡፡  ኢያሱን በእርጅና ምክኒያት ያልተወረሱትን ምድሮች ለመውረስ በእግዚአብሄር መላክ አይችልም ነበር፡፡
ሰው ልቡ ሲያረጅ መውጣት መግባት መውረስ እየቻለ ልቡ ድክም ይላል፡፡ ሰው ልቡ ሲያረጅ መውጣት መግባት መውረስ እየቻለ እግሩን ዘርግቶ እንዳይራመድ ስንፍና ይጫጫነዋል፡፡ ሰው ልብ ሲያረጅ የሚያወጣውን ወጭ በጣም ከማጋነኑ የተነሳ የሚያገኘውን እግዚአብሄርን በመታዘዝ የሚያገኘውን ዘላለማዊ ትርፍ አያስበውም፡፡ ሰው ልቡ ሲያረጅ ያለውን መጠበቅ እንጂ ሌላ መጨመር አያስብም፡፡ ሰው ለመውጣት ለመውረስ ያለው እድል በህይወት እስካለ ድረስ ብቻ ነው፡፡ ሰው ወደሚሄድበት እነዚህ ሥራና አሳብ እውቀትና ጥበብ አይኖሩም፡፡  
አንተ በምትሄድበት በሲኦል ሥራና አሳብ እውቀትና ጥበብ አይገኙምና እጅህ ለማድረግ የምታገኘውን ሁሉ እንደ ኃይልህ አድርግ። መጽሐፈ መክብብ 9፡10
ከእግዚአብሄር ጋር በኖርን መጠን የመውጣትና የመውረስ ፍላጎታችን በዚያው መጠን መጨመር እንጂ መቀነስ የለበትም፡፡ በጌታ ያለን ልምምድ እየጨመረ ሲሄድ የመውጣት የመውረስ እምነታችን ካልጨመረ ችግር አለ ማለት ነው፡፡ በጌታ ቤት በቆየን መጠን ጌታን ለመታዘዝ ለመውረስ እየሰነፉ መሄድ የመንፈሳዊ ጤንነት ምልክት አይደለም፡፡ ትክክለኛው እድገት በእድሜያችን መጠን ልባችን ሲታደስ ፍሬያችንም ሲበዛ ነው፡፡
ጻድቅ እንደ ዘንባባ ያፈራል፥ እንደ ሊባኖስ ዝግባም ያድጋል። በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ ተተክለዋል፥ በአምላካችንም አደባባይ ውስጥ ይበቅላሉ። ያን ጊዜ በለመለመ ሽምግልና ያፈራሉ፤ ደስተኞችም ሆነው ይኖራሉ። መዝሙረ ዳዊት 92፡12-14
የህይወት ፈተና አላማው እምነታችንን እንዲያጠራና እንዲያከብረው እንጂ እንዲያጠፋው አይደለም፡፡ 
በዚህም እጅግ ደስ ይላችኋል፥ ነገር ግን በእሳት ምንም ቢፈተን ከሚጠፋው ወርቅ ይልቅ አብልጦ የሚከብር የተፈተነ እምነታችሁ፥ ኢየሱስ ክርስቶስ ሲገለጥ፥ ለምስጋናና ለክብር ለውዳሴም ይገኝ ዘንድ አሁን ለጥቂት ጊዜ ቢያስፈልግ በልዩ ልዩ ፈተና አዝናችኋል።  1ኛ የጴጥሮስ መልእክት 1፡6-7
ካሌብ እድሜው በጨመረ ቁጥር ሃይሉን እንደዚያው ይጨምር ነበር፡፡
አሁንም፥ እነሆ፥ እግዚአብሔር ለሙሴ ይህን ቃል ከተናገረ በኋላ፥ እስራኤል በምድረ በዳ ሲዞሩ፥ እርሱ እንደ ተናገረኝ እግዚአብሔር እነዚህን አርባ አምስት ዓመት በሕይወት አኖረኝ፤ አሁንም፥ እነሆ፥ ለእኔ ዛሬ ሰማንያ አምስት ዓመት ሆነኝ። ሙሴም በላከኝ ጊዜ እንደ ነበርሁ፥ ዛሬ ጕልበታም ነኝ፤ ጕልበቴም በዚያን ጊዜ እንደ ነበረ፥ እንዲሁ ዛሬ ለመዋጋት ለመውጣትም ለመግባትም ጉልበቴ ያው ነው። መጽሐፈ ኢያሱ ወልደ ነዌ 14፡10-11
የክርስትያን ህይወት ሙሉ ቀን እስከሚሆን ካለማቋረጥ እየጨመረ እንደሚበራ የንጋት ፀሃይ እንጂ እንደሚጠልቅ የምሽት ጀንበር አይደለም፡፡
ጫማህ ብረትና ናስ ይሆናል፤ እንደ ዕድሜህ እንዲሁ ኃይልህ ይሆናል። ኦሪት ዘዳግም 33፡25
እግዚአብሄርን የሚጠብቅ ሰው ሃይሉ እየታደሰ አስከመጨረሻው በብቃት ይጨርሳል እንጂ ከመንገድ አይመለስም፡፡
ምኞትሽን ከበረከቱ የሚያጠግባት፥ ጕልማስነትሽን እንደ ንስር ያድሳል። መዝሙረ ዳዊት 103፡5
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.dinsa.37/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ኢየሱስ #ጌታ #እሳት #ህብረት #ቃል #ሽበት #ሽምግልና #ድፍረት #መቀጣጠል #ክብር #አገልግሎት #መዋረድ #መርካት #ፀጋ #እውቀት #ኢየሱስንተመልክተን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ብፅእና #እምነት #ታላቅነት #ማገልገል #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

Tuesday, October 22, 2019

ፈጻሚውን ኢየሱስን



የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን ተመልክተን፥ በፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግሥት እንሩጥ፤ ወደ ዕብራውያን 122
ህይወት ሩጫ ነው፡፡ የህይወት ሩጫ አሸናፊነታችን የሚለካው በምናተኩርነት ነገር ላይ ነው፡፡ በትክክለኛ ነገር ላይ ካተኮትን ሩጫውን በድል እንወጣዋለን፡፡ ትክክለኛውን ነገር ካልተመለከትን ሩጫውንም መጨረስም ሆነ አሸናፊ መሆን እንችልም፡፡
ኢየሱስን ተመልከተን እንድንሮጥ በኢየሱስ ላይ እንድናተኩር መፅሃፍ ቅዲስ ያስተምረናል፡፡
ነገር ግን በህይወት እኔን ስማኝ በእኔ ላይ አተኩር የሚሉ ብዙ ተፎካካሪ ነገሮች አሉ፡፡ እኔን ካልተመለከትክ አይሳካልህም፡፡ እኔን ካለሰማህ ዋ የሚሉ የሚያስፈራሩ ብዙ ነገሮች በዙሪያችን አሉ፡፡ አንዳንዶቹ እኔን ካጣህ ዋጋ የለህም ብለው ያስፈራራሉ፡፡ እኔን ካገኘህ ህይወትህ ይለወጣል ብለው ካላቅማችው ቃል የሚገቡ ብዙ ነገሮች ናቸው፡፡
ሰው በአንድ ጊዜ ሁለት ነገር ላይ ማተኮር አይችልም፡፡ ኢየሱስ ላይ ብቻ በማተኮር ሮጠን ይድሉን እክሊል ከተጎናፀፍን ማተኮር የሌሉብንን ነገሮች ከእግዚአብሄር ቃል እንመልከት፡-
1.      በደስታ እና በሃዘን ላይ ማተኮር ትኩረታችንን ከኢየሱስ ላይ እንድንመልስ ያደርጋል፡፡  
ደስታም ሆነ ሀዘን ይመጣሉ ይሄዳሉ፡፡ የትኛውንም ደስታ አይናችንን ከኢየሱስ ላይ እንድናነሳ እንዲያደርገን መፍቀድፍ የለብንም፡፡ እንዲሁም የትኛውም ሃዘን በኢየሱስ ላይ እንዳናተኩር ለማድረግ ከተሳካለት ተሸንፈናል፡፡
የሚያለቅሱም እንደማያለቅሱ፥ ደስ የሚላቸውም ደስ እንደማይላቸው፥ የሚገዙም ምንም እንደሌላቸው፥ በዚችም ዓለም የሚጠቀሙ በሙሉ እንደማይጠቀሙባት ይሁኑ፤ የዚች ዓለም መልክ አላፊ ነውና። 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 7፡30-31
2.     አድናቆትና ትችት ላይ ማተኮር አይናችንን ኢየሱስ ላይ እንዳናተኩር ያደርጋል፡፡
የሰው አድናቆት ላይ ልባችንን መጣል የለብንም፡፡ አንዳንድ ጊዜ ሰው የሚያደንቀንም ሆነ የሚጥለን ስለማያውቀን ነው፡፡ በሰው አድናቆት ላይ ልባችንን ከጣልን ህይወታችንን እንጥላለን፡፡ የሰውን ክፉም ወሬም ይሁን አድናቆት መጠበቅ ያለብን በልባችን ውስጥ ሳንከት በውጭ ነው፡፡ በክፉ ወሬም ሆነ በመልካመ ወሬ ራሳችንን ማማጠን አለብን፡፡
በክፉ ወሬና በመልካም ወሬ ራሳችንን እናማጥናለን፤ አሳቾች ስንባል እውነተኞች ነን፤ 2ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 6፡8
ጠላትህ ቢወድቅ ደስ አይበልህ፥ በመሰናከሉም ልብህ ሐሤት አያድርግ፥ መጽሐፈ ምሳሌ 24፡17
አስተማማኙ ደስታ በጌታ ደስ የምንሰኝበት ደስታ ብቻ ነው፡፡ ከጌታ ውጭ ያለው ደስታ ሁሉ ጊዜያዊ ደስታ ነው፡፡
ዳሩ ግን፥ ወንድሞች ሆይ፥ ይህን እናገራለሁ፤ ዘመኑ አጭር ሆኖአል፤ ከእንግዲህ ወዲህ ሚስቶች ያሉአቸው እንደሌላቸው ይሁኑ፥ የሚያለቅሱም እንደማያለቅሱ፥ ደስ የሚላቸውም ደስ እንደማይላቸው፥ የሚገዙም ምንም እንደሌላቸው፥ በዚችም ዓለም የሚጠቀሙ በሙሉ እንደማይጠቀሙባት ይሁኑ፤ የዚች ዓለም መልክ አላፊ ነውና። 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 7፡29-31
3.     በክብርም በውርደትም ላይ ማተኮር አደገኛ ነው፡፡
የምድራዊ ክብርም ሆነ ውርደት ልናተኩርባቸውና ልንደገፍባቸው የማንችላቸው ጊዜያዊ ነገሮች ናቸው፡፡
የተዋረደው ወንድም ግን በከፍታው፥ ባለ ጠጋም በውርደቱ ይመካ፤ እንደ ሣር አበባ ያልፋልና። ፀሐይ ከትኵሳት ጋር ይወጣልና፥ ሣርንም ያጠወልጋልና፥ አበባውም ይረግፋልና፥ የመልኩም ውበት ይጠፋልና፤ እንዲሁ ደግሞ ባለ ጠጋው በመንገዱ ይዝላል። የያዕቆብ መልእክት 1፡9-11
4.     ነገና ትላንት ላይ ማተኮር ኢየሱስ ላይ እንዳናተኩር ያደርገናል፡፡  
የእግዚአብሄር ምህረት ማለዳ ማለዳ አዲስ ነው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር ባለፈው በሰራው በትላንት ላይ ከቆምን ከዛሬ በረከት ሰላምና ስኬት ጋር እንተላፋለን፡፡ ዛሬን ንቀን ደግሞ በነገ ብቻ ላይ ካተኮርን እንሳሳታለን፡፡ ነገን ጎትተን ዛሬ ላይ ለመኖር ከፈለግን ነገራችን ይዛባል፡፡
ነገ ለራሱ ይጨነቃልና ለነገ አትጨነቁ፤ ለቀኑ ክፋቱ ይበቃዋል። የማቴዎስ ወንጌል 6፡34
በጌታ ላይ ማተኮር ትተን በማናውቀው ነገ ላይ ማተኮር ውድቀት ያመጣል፡፡
አሁንም፦ ዛሬ ወይም ነገ ወደዚህ ከተማ እንሄዳለን በዚያም ዓመት እንኖራለን እንነግድማለን እናተርፍማለን የምትሉ እናንተ፥ ተመልከቱ፥ ነገ የሚሆነውን አታውቁምና። የያዕቆብ መልእክት 4፡13
5.       በውድቀትና በስኬት ላይ ማተኮር በኢየሱስ ላይ እንዳናተኩር ይሸፍነናል፡፡
ውድቀት ላይ ማተኮር ኢየሱስን ተመልከተን ሩጫችንን በትግስት እንዳንሮጥ ሊያግደን ይችላል፡፡ ከውድቀታችን ተምረን እንደገና ኢየሱስ ላይ ማተኮር ግን ወደፊታችንን ያሳምረዋል፡፡ እግዚአብሄር ከማንም ጋር ውድድር ውስጥ አይገባም፡፡ እግዚአብሄር ሆን ብሎ ለመጣል ብሎ ማንንም በክፉ አይፈትንም፡እግዚአብሄር ከውድቀታችን የሚጠቀመው ነገር ትሁት መሆናችን ራሳችንን ይበልጥ ማወቃችንና ለመስማት መዘጋጀታችንን ብቻ ነው፡፡  
እንዲሁም በስኬት ላይ ማተኮራችን ትልቁን የእግዚአብሄርን አላማ እንዳናይ ያደርገናል፡፡ ስኬትን የሚሰጠን እግዚአብሄር ላይ እንጂ ስኬቱን ላይ ካተኮርን መውደቃችን አይቀርም፡፡ ያለፈው ስኬታችን ላይ ካተኮርነና በስኬታችን ከተኩራራን የሚበልጠውን የወደፎረቱን ስኬት ለመያዝ እናዳንዘረጋ ጠላት ይሆንብናል፡፡
ወንድሞች ሆይ፥ እኔ ገና እንዳልያዝሁት እቈጥራለሁ፤ ነገር ግን አንድ ነገር አደርጋለሁ፤ በኋላዬ ያለውን እየረሳሁ በፊቴ ያለውን ለመያዝ እዘረጋለሁ፥ ወደ ፊልጵስዩስ ሰዎች 3፡13
6.       በድካማችንም ይሁን በጥንካሬያችን ላይ ማተኮር እንዲሁ ሩጫውን በትግስ እንዳንሮጥ እና እንዳንፈፅመው ያግደናል፡፡
ማግኘታችንም ሁሉን እንድንችል አያደርገንም፡፡ ማጣታችንም ሁሉን እንድንችል አያግደንም፡፡ ማጣትም ማግኘትም ምንም አይደሉም፡፡
መዋረድንም አውቃለሁ መብዛትንም አውቃለሁ፤ በእያንዳንዱ ነገር በነገርም ሁሉ መጥገብንና መራብንም መብዛትንና መጉደልን ተምሬአለሁ። ኃይልን በሚሰጠኝ በክርስቶስ ሁሉን እችላለሁ። ወደ ፊልጵስዩስ ሰዎች 4፡12-13
7.       በሰዎች ላይ ማተኮር
በመልካም ሰዎችም ላይ ይሁን በክፉ ሰዎች ላይ ማተኮር የብርታታችን ምንጭ በሆነው በክርስቶስ ላይ እንዳናተኩር ያደናቅፈናል፡፡ ሰዎች መልካም የሚሆኑልን እግዞአብሄር ሲጠቀምባቸው ብቻ ነው፡፡ የሰዎች የመልካምነታችው ምንጭ እግዚአብሄር ነው፡፡ ሰዎች ክፉ ቢሆኑብን እንዲሁ ተጠቃሚው ሰይጣን እንጂ ሰዎች አደሉም፡፡ የበደሉን ሰዎችን ይቅር አለማለት ትኩረታችንን ከኢየሱስ ላይ አንስተን ሰዎች ላይ እንድናደርግ ያደርገናል፡፡ በሰዎች ላይ ማተኮር ውድቀትን ያመጣል፡፡
በህይወታችን ራሳቸውን ሰጥተው ከሚያገለግሉን ሰዎች አልፈን ካላየን እንሰናከላለን፡፡ ሰዎች በስጦታ ቢያገለግሉን የእግዚአብሄር ስጦታ እንጂ የሰዎች አይደለም፡፡
እኔ ተከልሁ አጵሎስም አጠጣ ነገር ግን እግዚአብሔር ያሳድግ ነበር፤ እንግዲያስ የሚያሳድግ እግዚአብሔር እንጂ የሚተክል ቢሆን ወይም የሚያጠጣ ቢሆን አንዳች አይደለም። 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 3፡6-7
8.       በሰይጣን ላይ ማተኮር የእግዚአብሄርን በጎነት እንዳናጣጥመው ያደርገናል፡፡
ሰይጣንን ምንም እንደማያደርግ መናቅ መልካም አለመሆኑ ያህል ሰይጣን ላይ ማተኮር መልካመ አይደለም፡፡ ሰይጣን የተሸነፈ ጠላት ነው፡፡ ሰይጣን የሚሰራው ሰውን በማስፈራራት ስለሆነ ሁልጊዜ ትኩረትን ይፈልጋል፡፡ ትኩረታችሁን ከኢየሱስ ላይ በማንሳታችሁ ብቻ ሰይጣን ይጠቀማል፡፡   
እኛ የምንኖረው በሰይጣን ምህረት አይደለም፡፡ እኛ የምንኖረው አስኮናኞች ኑሩ ብሎ ሰይጣን ስለፈቀደለን ሳይሆን በተሰጠን በልጅነት ስልጣናችን ተጠቅመን በግድ ነው፡፡ እኛ የምንኖረው በእግዚአብሄር ምህረት ብቻ ነው፡፡
ስለ ፍርድም፥ የዚህ ዓለም ገዥ ስለ ተፈረደበት ነው። የዮሐንስ ወንጌል 16፡11
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.dinsa.37/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ኢየሱስ #ጌታ #ተመልክተን #እይታ #ማጣት #ማግኘት #ትላንት #ነገ #ውድቀት #ስኬት #አድናቆት #ትችት #ደስታ #ሃዘን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ቃል #አሸናፊ #አማልክት #የእግዚአብሄርእቅድ #የእግዚአብሄርፈቃድ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

Friday, October 18, 2019

ቸርነትህና ምሕረትህ በሕይወቴ ዘመን ሁሉ ይከተሉኛል



ቸርነትህና ምሕረትህ በሕይወቴ ዘመን ሁሉ ይከተሉኛል፥ በእግዚአብሔርም ቤት ለዘላለም እኖራለሁ። መዝሙረ ዳዊት 23፡6
እግዚአብሄር ፈጣሪያችን ነው፡፡ እኛ ለእግዚአብሄር ተፈጥረናል፡፡ እኛ የእግዚአብሄር ነን፡፡ እግዚአብሄር የህይወታችን ባለቤት ነው፡፡
እኛ የእግዚአብሄርን ቸርነትና ምህረት ለማግኘት ከምንፈልገው በላይ እግዚአብሄር የእኛን ምህረትና ቸርነት ማግኘት ይፈልገዋል፡፡
በእኛ ቸርነቱንና ምህረቱን በመከተል ላይ ብቻ እግዚአብሄር አይተማመንም፡፡ እኛ የመከተል ችሎታችን እንከን የለሽ ስላይደለ የእግዚአብሄርን ምህረትና ቸርነት ብንከተል በትክክል ላንከተለው እንችላለን፡፡ እኛ እውቀታችን ፍፁም ስላይደለ የእግዚአብሄርን ምህረትና ቸርነት በትክክል ላንከተል ልንሳሳት እንችላለን፡፡
እግዚአብሄር የምህረትና የቸርነትን ነገር ለእድል አልተወውም፡፡ እግዚአብሄር የቸርነትና የምህረትን ነገር ለእኛ ፍፁም ያልሆነ ችሎታም አልተወውም፡፡ ምህረትና ቸርነት እኛን የመከተሉን ነገር እግዚአብሄር ራሱ የሚያደርገው ሃላፊነቱ አድርጎ ወስዶታል፡፡
እግዚአብሄር ግን እንደ ህይወታችን ባለቤት በምህረትና በቸርነት ከተከተለን ምህረትና ቸርነት ያገኙናል እንጂ አይስቱንም፡፡
አንድ ሰው በህልሙ አባቱ እጁን ይዞት አየ፡፡ ህልሙ ሲፈታለት እኔ አግዚአብሄር አባተህ እጅህን ይዤሃለሁ፡፡ አንተ እጄን ብትይዘኝ በመንገድ ላይ ከፍታና ዝቅታ ልትለቀኝ ትችላለህ፡፡ አንተ ምንም አስቸጋሪ ነገር ውስጠ ብታለፍ እኔ ስለያዝኩህ አስተማማኝ ነው፡፡
እግዚአብሄር የሚይዘን እስከጊዜው አይደለም፡፡ ከማኅፀን እስካሁን የተሸከመን እግዚአብሄር እስከሽምግልና ይሸከመናል፡፡
እናንተ የያዕቆብ ቤት ሆይ፥ የእስራኤልም ቤት ቅሬታ ሁሉ፥ ከሆድ ያነሣኋችሁ ከማኅፀንም የተሸከምኋችሁ፥ ስሙኝ። እስከ ሽምግልና ድረስ እኔ ነኝ፥ እስከ ሽበትም ድረስ እሸከማችኋለሁ፤ እኔ ሠርቻለሁ እኔም አነሣለሁ፤ እኔ እሸከማለሁ እኔም አድናለሁ። ትንቢተ ኢሳይያስ 46፡3-4
በእናንተ መልካምን ሥራ የጀመረው እስከ ኢየሱስ ክርስቶስ ቀን ድረስ እንዲፈጽመው ይህን ተረድቼአለሁና፤ ወደ ፊልጵስዩስ ሰዎች 1፡6
እንደዚህ የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን መገለጥ ስትጠባበቁ አንድ የጸጋ ስጦታ እንኳ አይጎድልባችሁም፤ እርሱም ደግሞ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ቀን ያለ ነቀፋ እንድትሆኑ እስከ ፍጻሜ ድረስ ያጸናችኋል። ወደ ልጁ ወደ ጌታችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ኅብረት የጠራችሁ እግዚአብሔር የታመነ ነው። 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 17-9
ህይወታችንን ዘመናችንን የሰጠነው እግዚአብሄር ታማኝ ነው፡፡
ስለዚህም ምክንያት ይህን መከራ ደግሞ ተቀብዬአለሁ፥ ነገር ግን አላፍርበትም፤ ያመንሁትን አውቃለሁና፥ የሰጠሁትንም አደራ እስከዚያ ቀን ድረስ ሊጠብቅ እንዲችል ተረድቼአለሁ። 1ኛ ወደ ጢሞቴዎስ 1፡12
ቸርነትህና ምሕረትህ በሕይወቴ ዘመን ሁሉ ይከተሉኛል፥ በእግዚአብሔርም ቤት ለዘላለም እኖራለሁ። መዝሙረ ዳዊት 236
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ያድርጉ!
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.dinsa.37/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ኢየሱስ #ጌታ #ቸርነት #ምሕረት #ሽምግልና #መሪነት #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ልብ #እምነት #ምሪት #ድምፅ #አስተምርሃለሁ #መንገድ #እመራሃለሁ #ዓይኖቼን #አጠናለሁ #ሰላም #ደስታ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #መናገር #ፅናት #ትግስት #መሪ

Thursday, October 17, 2019

የንቀት መድሃኒት



እግዚአብሄር በእኛ ውስጥ ለሌሎች ሰዎች በረከት የሚሆንን ነገር አስቀምጧል፡፡ እንዲሁም እግዚአብሄር የእኛን ህይወታችንን በረከት ያስቀመጠው በሌላው ሰው ውስጥ ነው፡፡ ሌላውን ሰው መናቅ የእግዚአብሄርን ስጦታ መናቅ ነው፡፡ ሌላውን ሰው መናቅ የእግዚአብሄርን ስጦታ መጣል ነው፡፡ ሌላውን ሰው መናቅ ከእግዚአብሄር በረከት ጋር መተላለፍ ነው፡፡
እውነት ነው ሁላችንም የህይወት ደረጃ አለን፡፡ ሁላችንም የምናከብረውና የምንንቀው ነገር አለ፡፡ በተለምዶ አብረን ለመስራት የምንመርጠውና የማንመርጠው ሰው አለ፡፡ ለጓደኝነት የምንመርጠውና የማንመረጥው ሰው ሊኖር ግድ ነው፡፡ ነገር ግን የምንመርጥበት መመዘኛ መዛባት ምርጫችንን ከትእቢት የመነጨ ንቀት ያደርገዋል፡፡  
ሁላችንም በተለያየ ጊዜ ሌሎችን ለመናቅ እንፈተናለን፡፡ በተለይ ድካም ያየንበትን ሰው ይህ ሰው ለምንም አይጠቅምም አይረባም በማለት ለመናቅ በእጅጉ እንፈተናለን፡፡ ሰውን አይረባም አይጠቅምም ብሎ መናቅ እና ዝቅ ዝቅ አድርጎ ማየት ግን ከእግዚአብሄር አይደለም፡፡ በሰው ላይ ሙሉ ለሙሉ ተስፋ መቁረጥ ግን የክፉ እግዚአብሄራዊ ምዘና አይደለም፡፡
መፅሃፍ ቅዱስ እንደ እነርሱ የሰው ልጆች የሆኑትን ሰዎች ዝቅ ዝቅ አድርገው ለሚያዩና ለሚንቁ ሰዎች ብርቱ ማስጠንቀቂያ አለው፡፡ ነው፡፡
እኔ ግን እላችኋለሁ፥ በወንድሙ ላይ የሚቆጣ ሁሉ ፍርድ ይገባዋል፤ ወንድሙንም ጨርቃም የሚለው ሁሉ የሸንጎ ፍርድ ይገባዋል፤ ደንቆሮ የሚለውም ሁሉ የገሃነመ እሳት ፍርድ ይገባዋል። የማቴዎስ ወንጌል 5፡22
አንተ ከሌላው እንድትለይ እና እንዳትናቅ ያደረገህ እግዚአብሄር ነው፡፡ ከእግዚአብሄር በተቀበልከው ነገር መልሰውህ እንዳንተው በእግዚአብሄር የተፈጠረውን ሰው ለመናቅ መጠቀም አግባብ አይደለም፡፡
አንተ እንድትበልጥ ማን አድርጎሃል? ያልተቀበልኸውስ ምን አለህ? የተቀበልህ ከሆንህ ግን እንዳልተቀበልህ የምትመካ ስለ ምንድር ነው? 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 4፡7
ንቀት ከትእቢት ይመጣል፡፡ ንቀት ያለን ነገር ባለቤቱ እኛ እንደሆንን በስህተት ከማሰብ ይመጣል፡፡
እርሱን እንድትንቀው ያደረገው የሃጢያት ፍላጎት በአንተም ውስጥ አለ፡፡ እርሱን እንደዚህ እንድትንቀርው ያደረገውን የሃጢያት ፍላጎት ይዘህ እንደአንተው የተፈጠረውን ሰው መናቅ አለማስተዋል ነው፡፡
ንቀት በክፉ ከመፍርድ ይመጣል፡፡ ንቀት ማሰብ ከሚገባው አልፎ ራስን ከፍ አድርጎ ከማየት ይመጣል፡፡ ንቀት ማሰብ ከሚገባው አልፎ ሌላውን ዝቅ አድርጎ ከማየት ይመጣል፡፡
ወንድሞቼ ሆይ፥ በክብር ጌታ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ያለውን እምነት ለሰው ፊት በማድላት አትያዙ። የወርቅ ቀለበት ያደረገና የጌጥ ልብስ የለበሰ ሰው ወደ ጉባኤአችሁ ቢገባ፥ እድፍ ልብስም የለበሰ ድሀ ሰው ደግሞ ቢገባ፥ የጌጥ ልብስም የለበሰውን ተመልክታችሁ፦ አንተስ በዚህ በመልካም ስፍራ ተቀመጥ ብትሉት፥ ድሀውንም፦ አንተስ ወደዚያ ቁም ወይም ከእግሬ መረገጫ በታች ተቀመጥ ብትሉት፥ ራሳችሁን መለያየታችሁ አይደለምን? ክፉ አሳብ ያላቸውም ዳኞች መሆናችሁ አይደለምን? የያዕቆብ መልእክት 2፡1
ሰው እግዚአብሄር እንዴት እንደሚያከብረው እንደ አይኑ ብሌን እንደሚጠነቀቅለት ሲያውቅ እግዚአብሄር ሌላውንም ሰው እንደሚያከብረው ስለሚያውቅ ሌላውምን ለመናቅ አይደፍርም፡፡
ሰው እግዚአብሄር እንዴት እንደወደደው ሲረዳ እግዚአብሄር ደግሞ ሁሉንም ስለሚወድ ከእግዚአብሄር ጋር ተባብሮ ሰዎችን ሁሉ ይወዳል ያከብራል እንጂ ማንንም አይንቅም፡፡ ሰዎችን የሚንቅ ሰው እግዚአብሄር እንዴት እንደወደደው በደንብ ያልተረዳ ሰው ነው፡፡
የእግዚአብሔር ልጆች ተብለን ልንጠራ አብ እንዴት ያለውን ፍቅር እንደ ሰጠን እዩ፥ እንዲሁም ነን። ስለዚህ ምክንያት ዓለም እርሱን ስላላወቀው እኛን አያውቀንም። 1 የዮሐንስ መልእክት 3፡1
ሰው በእግዚአብሄር መልክና አምሳል እንደተፈጠረ ሲረዳ ፣ ራሱን ሲያከብርና ሲወድ ሌላውን ያከብራል ማንንም አይንቅም፡፡
ሰውን የሚንቅ ሰው መናቅ የጀመረው ራሱን ነው፡፡ ሰውን የሚንቅ ሰው ለራሱ የሚገባ ፍቅርና አክብሮት የለውም፡፡ ሰውን የሚንቅ ሰው ራሱን እንደሚገባ አያከብርም አይወድም፡፡ ሰውን የሚያከብር ሰው ራሱን እንደሚያከብር ማረጋገጫው ነው፡፡

ሁለተኛይቱም ይህችን ትመስላለች፥ እርስዋም፦ ባልንጀራህን እንደ ነፍስህ ውደድ የምትለው ናት። የማቴዎስ ወንጌል 22፡39
ሰው ሰው ቢደክም እና ቢወድቅ እንኳን አንተ እንዳትወድቅ ያደረገህ ያው እግዚአብሄር የወደቀው እንዲነሳ ያደርገዋል፡፡
አንተ በሌላው ሎሌ የምትፈርድ ማን ነህ? እርሱ ቢቆም ወይም ቢወድቅ ለገዛ ጌታው ነው፤ ነገር ግን እግዚአብሔር ሊያቆመው ይችላልና ይቆማል። ወደ ሮሜ ሰዎች 14፡4
ንቀት በራስ ካለመተማመን ይመጣል፡፡ እውነተኛ የከበረ ሰው ሰውን በማክበር ይታወቃል፡፡ እውነተኛ ከአጉል ፉክክር የዳነ ሰው ሌላውን በማክበር ይታወቃል፡፡ ሰው ትልቅነቱ የሚታወቀው በእያንዳንዱ ሰው ውስጥ ታላቅነትን በማየት ችሎታው ነው፡፡ ሰው ትልቅነቱ የሚታወቀው ከድካም አልፎ ብርታት በማየት ችሎታው ነው፡፡ ሰው ታላቅነቱ የሚያወቀው በትንሹ ሰው ድካም ላይ ሳይሆን በሰው ጥንካሬው ላይ በማተኮር ችሎታው ነው፡፡
ሰውን የሚንቅ ሰው መረዳት የጎደለው ሰው ነው፡፡ ሰው እግዚአብሄር የሰውን ልጅን በመልኩና በአምሳሉ እንደፈጠረውና ምን ያህል እንደሚወደው ከእግዚአብሄር ቃል እየተረዳ ሲሄድ ሌላውቅን ሰው ለመናቅ አቅም ያነሰዋል፡፡ ሰው መረዳቱ ሲጨምርና ነገሮችን እንደ እግዚአብሄር መረዳት ሲጀምር የሚንቀውን እየተወ የሚያከብረውን እያበዛ ይሄዳል፡፡ 
እነሆ፥ እግዚአብሔር ኃያል ነው፥ ማንንም አይንቅም እርሱም በማስተዋል ብርታት ኃያል ነው። መጽሐፈ ኢዮብ 36፡5
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.dinsa.37/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ኢየሱስ #ጌታ #ንቀት #ትህትና #ትእቢት #ጥንካሬ #ብርታት #ቃል #ህይወት #አገልግሎት #አምልኮ #ፀሎት #ጥሪ #ተመልክተን #መቃጠል #መቀጣጠል #ክብር #አገልግሎት #መዋረድ #መርካት #ፀጋ #እውቀት #ኢየሱስንተመልክተን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ብፅእና #እምነት #ታላቅነት #ማገልገል #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ