Popular Posts

Saturday, May 19, 2018

አትብሉ አትንኩትም

እባብም እግዚአብሔር አምላክ ከፈጠረው ከምድር አውሬ ሁሉ ይልቅ ተንኰለኛ ነበረ። ሴቲቱንም፦ በውኑ እግዚአብሔር ከገነት ዛፍ ሁሉ እንዳትበሉ አዝዞአልን? አላት። ሴቲቱም ለእባቡ አለችው፦ በገነት ካለው ከዛፍ ፍሬ እንበላለን፤ ነገር ግን በገነት መካከል ካለው ከዛፉ ፍሬ፥ እግዚአብሔር አለ፦ እንዳትሞቱ ከእርሱ አትብሉ አትንኩትም። ዘፍጥረት 3፡1-3
እግዚአብሄር ሰውን የፈጠረው ለህብረት ነው፡፡ ይህ ህብረቱ እንዳይበላሽ ሰው ሌላን ማንንም መስማት አልነበረበትም፡፡ ይህ የእግዚአብሄርና የሰው ህብረት እንዳይበላሽ ሰው አትብላ የተባለውን ክፉውንና ደጉን የሚያሳውቀውን የዛፍ ፍሬ መብላት አልነበረበትም፡፡
ሰው ከዛፉ ፍሬ መብላቱ ብቻ ነው ክፉና ደጉን እንዲያውቅ የሚያደርገው፡፡ ሰው የዛፉን ፍሬ መንካቱ ክፉና ደጉን እንዲያውቅ አያደርገውም፡፡ ስለዚህ ነው እግዚአብሄር በግልጥ አትብሉ ያለው፡፡
ሰው የታዘዘው ከዛፉ ፍሬ እንዳይበላ ነው፡፡ ሰው የታዘዘው ብቻ መብላት ነበረበት፡፡ ሰው ያልታዘዘውን መብላት አልነበረበትም፡፡ የተከለከለው መብላትን ነው፡፡ የተከለከለው መንካትን አይደለም፡
እባቡ ግን ሄዋንን ሲጠይቃት አትብሉ ብሎዋል ብቻ ሳይሆን አትንኩትም የሚል ቃል ጨመረችበት፡፡ አትብሉ ብሎዋል ብትል እኮ በቂ ነበር፡፡ እርሱዋ ግን አትንኩትም የሚል ጨመረችበት፡፡
የወግ ሃይማኖት በሰው መንገድ እግዚአብሄር ማምለክ ነው፡፡ የወግ ሃይማኖት ወደ እግዚአብሄር ለመድረስ የሰው ፈጠራ ነው፡፡ እውነተኛው ሃይማኖት ግን በእግዚአብሄር መንገድ እግዚአብሄርን ማምለክ ነው፡፡  እውነተኛው ሃይማኖት ሰው ወደ እግግዚአብሄር የሚደርስበት የእግዚአብሄር ምሪት ነው፡፡
ሰው እግዚአብሄር ያዘዘውን ብቻ ሰምቶ ማድረግ አይደፈልግም፡፡ ሰው እግዚአብሄርን እንኳን ሊያሻሽለው ያምረዋል፡፡ ሰው ከእግዚአብሄር በላይ ፃዲቅ ሊሆን ይፈልጋል፡፡ ሰው ለእግዚአብሄር ይጨምርለታል፡፡ ሰው የእግዚአብሄርን ቃል በራሱ ሊያጠናክረው ይጥራል፡፡
የእግዚአብሄር ቃል ግን ራሱ ጠንካራ ነው፡፡ የእግዚአብሄር ቃል ለመፅናት የማንንም ሰው ድጋፍ አይፈልግም፡፡
የእግዚአብሄርን ቃል አናሳምረውም ያመረ ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል አናጣፍጠውም ጣፋጭ ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል አናፀናውም የፀና ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል አናጠናክረውም የጠነከረ ነው፡፡
እንዲያውም የእግዚአብሄርን ቃል ልናጠናክረው በሞከርን ቁጥር እናዳክመዋለን፡፡ የእግዚአብሄር ቃል ላይ ጉልበታችንን በጨመርንበት መጠን እናዳክመዋለን፡፡
የሰው ቍጣ የእግዚአብሔርን ጽድቅ አይሠራምና። ያዕቆብ 1፡20
የእግዚአብሄር ቃል ለማፅናት ወጋችንን በጨመርነበት መጠን እንሽረዋለን፡፡
ባስተላለፋችሁትም ወግ የእግዚአብሔርን ቃል ትሽራላችሁ፤ እንደዚሁም ይህን የሚመስል ብዙ ነገር ታደርጋላችሁ። ማርቆስ 7፡13
መፅሃፍ ቅዱስ አትስከር ሲል አትጠጣ ብለን አንጨምርበት፡፡ አትስከር ያለው ህሊናችንን እንዳትስት ፣ ለስጋህ አርነት እንዳትሰጥ ፣ ራሳችንን መግዛት እንዳይሳነን ነው፡፡ አትጠጣ ስንል ግን ለምን እግዚአብሄር አትጠጣ እንዳለ ማስረዳት ስለሚያቅተን የቃሉን ሃይል እንሽረዋለን፡፡ በቃሉ ላይ ስለምጨምር እግዚአብሄር ያልሰጠንን ሸክም ጨምረን ሰለምንሸከም እግዚአብሄርን ይበልጥ ያስደሰትን ይመስለናል ነገር ግን እናሳዝነዋለን፡፡ ያላለንን ጨምረን ስንል ቅድስና ይመስልሃል ነገር ግን ከስጋ ነው፡፡ ክርስትና ይመስለናል ነገር ግን የሰው ወግ ነው፡፡   
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #አትያዝ #አትቅመስ #አትንካ #አለማዊ #ስርአት #መጀመሪያ #ፅድቅ ሰላም #መንፈስቅዱስ #ደስታ #መብል #መጠጥ #አትስከር #አትጠጣ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ልብ #አለም #ድምፅ #ቅባት #ደስታ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #መሪ

No comments:

Post a Comment