Popular Posts

Friday, September 30, 2022

እግዚአብሄር ለምን ግድ ይለዋል ?

 

እግዚአብሄር የአላማ አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሄር የፈጠረን ለክብሩ ነው፡፡  የፈጠረን እግዚአብሄር በህይወታችን ምን እንደምንሰራ ግድ ይለዋል፡፡ እግዚአብሄር ምን እንደምንሰራ ግድ እንደሚለው ሁሉ ለምን ምክኒያት እንደምንሰራው ደግሞ ግድ ይለዋል፡፡

አንድን ነገር ለማድረግ ያነሳሳን ነገር በተለይም የተደበቀ ወይም ግልጽ ያልሆነ ምክንያት ተነሳሽነት /motive/ ይባላል። ታዲያ የምንሰራውን ነገር ከምንም የልብ መነሻ ሃሳብ ወይም ተነሳሽነት /motive/ እንደሆነ እግዚአብሄር ማወቅ ይፈልጋል፡፡

መፅሃፍ ቅዱስ ምንም መልካም ነገር ብናደርግ ከፍቅር መነሻ ሃሳብ ካላደረግነው ከንቱ እንደሆነ እና ምንም እንደማይጠቅመን ያስተምረናል፡፡ ልብን የሚመዝነው እግዚአብሄር የምናደርገውን ነገር ብቻ ሳይሆን በምን መነሻ ሃሳብ እንደምናደርገው ያያል፡፡ እግዚአብሄር እንድን መልካም ነገርን ስላደርግን ብቻ ጎሽ አይለንም ወይም ደስ አይሰኝም፡፡ በፍቅር ወይም በራስ ወዳድነት ለግል ስማችን ብለን ወይም በፉክክር ስሜት እንዳደረግነው የሰውን ልብ የሚመዝነው እግዚአብሄር ያውቃል፡፡

ትንቢትም ቢኖረኝ ምሥጢርንም ሁሉና እውቀትን ሁሉ ባውቅ፥ ተራሮችንም እስካፈልስ ድረስ እምነት ሁሉ ቢኖረኝ ፍቅር ግን ከሌለኝ ከንቱ ነኝ። ድሆችንም ልመግብ ያለኝን ሁሉ ባካፍል፥ ሥጋዬንም ለእሳት መቃጠል አሳልፌ ብሰጥ ፍቅር ግን ከሌለኝ ምንም አይጠቅመኝም። 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 13፡2-3

መልካሙን ነገር በፍቅር ካላደረግከው እና በጥላቻ ወይም በፉክክር ካደረግከው ተራሮችን በእምነት ስናፈልስ ወንድማችንን ለመጉዳት የወንድማችን መንገድ ለመዝጋት ልናደርገው እንችላለን፡፡

እንግዲህ ምጽዋት ስታደርግ፥ ግብዞች በሰው ዘንድ ሊከበሩ በምኩራብ በመንገድም እንደሚያደርጉ በፊትህ መለከት አታስነፋ፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋቸውን ተቀብለዋል። የማቴዎስ ወንጌል 6፡2

በምታደርገው ነገር ልትረካ ሰውንም ልታስደንቅ ትችላለን እግዚአብሄርን ግን በተበላሸ የልብ መነሻ ሃሳብ ባደረግከው ነገር ልታታልለው ወይም ልታስደንቀው አትችልም፡፡

ስትጸልዩም እንደ ግብዞች አትሁኑ፤ ለሰው ይታዩ ዘንድ በምኩራብና በመንገድ ማዕዘን ቆመው መጸለይን ይወዳሉና፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋቸውን ተቀብለዋል። የማቴዎስ ወንጌል 6፡5

ስለዚህ መልካምም ነገር ቢሆን እንኳን የምናደርገው ነገር በምን የልብ መነሻ ሃሳብ እንደምናደርገው ልባችንን መመርመር ከንቱ በሆነ እና በማይጠቅም ነገር ላይ ህይወታችንን ከማባከን ያድነናል፡፡  

አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa 


Thursday, September 29, 2022

ቅንነትና ንጽሕና እንዳይለወጥ

 


በእግዚአብሔር ቅንዓት እቀናላችኋለሁና፥ እንደ ንጽሕት ድንግል እናንተን ለክርስቶስ ላቀርብ ለአንድ ወንድ አጭቻችኋለሁና፤ ነገር ግን እባብ በተንኮሉ ሔዋንን እንዳሳታት፥ አሳባችሁ ተበላሽቶ ለክርስቶስ ከሚሆን ቅንነትና ንጽሕና ምናልባት እንዳይለወጥ ብዬ እፈራለሁ። 2 ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 11፡2-3

በምንም መልኩ ይሁን ንፅህና ደስ የሚያሰኝ ነገር ነው፡፡ በእግዚአብሄር መልክና አምሳል ስለተፈጠረን ንፅህናን እንወዳለን፡፡ ንፅህና ሲጎድል ደግሞ በእጅጉ ደስታችንን እናጣለን፡፡ ሰውነታችን ከቆሸሸ ከምግብ እና ከመኝታ አስቀድመን የምናደርገው ነገር በመታጠብ እንደገና ንፅህናችንን መጠበቅ ነው፡፡ ንፁህ ልብስ ያልለበስን ጊዜ የነበረን ድፍረታችን ሁሉ ይመታል፡፡ ቤታችን ሲመሰቃቀል እና ሲቆሽሽ መልሰን አስክናፀዳው እረፍት እናጣለን፡፡

ይህ ሁሉ ንፅህና በጣም ደስ የሚያሰኝ እና የሚበረታታ ነገር ነው፡፡ እነዚህ የቤት ፣ የገላ እና የልብፅ ንፅህና መጓደል በህይወታችነ ላይ የሚያሳድሩት አሉታዊ አስተዋፅኦ አለ፡፡ ነገር ግን የእነዚህ የንፅህና ጉድለት በህይወታችን ላይ ከሚያሳድረው አሉታዊ አስተዋእፆ በላይ የህይወት ወይም የልብ ንፅህና  መጓደል የሚያስከትለው ጥፋት እጅግ አስከፊ ነው፡፡

ሰው ለልብሱ ለገላው ለቤቱ ንፅህና ከሚጠፋው ጊዜ በላይ በህይወቱ ላይ በብዙ እጥፍ እጅግ ወሳኝ በሆነው በልቡ ንፅህና ላይ የሚያጠፋው ጊዜ እጅግ መብለጥ አለበት፡፡

ከአፍ የሚወጣ ግን ከልብ ይወጣል፥ ሰውንም የሚያረክሰው ነው። ከልብ ክፉ አሳብ፥ መግደል፥ ምንዝርነት፥ ዝሙት፥ መስረቅ፥ በውሸት መመስከር፥ ስድብ ይወጣልና። የማቴዎስ ወንጌል 15፡18-19

ንፅህና እጅግ ትጋትና ክትትል የሚፈልግ ነገር ነው፡፡ ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ አፀዳሁት የሚባል ነገር የለም፡፡ አፅድተህ ስትጨርስ ለሚቀጥለው ፅዳት አቅድ ማውጣት ግድ ይላል፡፡ እንደፀዳ የሚቆይ ነገር የለም፡፡ እንዲሁ ከተውከው ምንም ነገር ይቆሽሻል፡፡  

የልብም ንፅህና እንዲሁ ነው፡፡ የልብ ንፅህና በየጊዜው ራሳችንን ማየት መፈተሽ ይጠይቃል፡፡ ትላንት አፅድቼዋለሁ ብለን ብንሰንፍ ወይም ችላ ብንል ከንፅህና እንጎድላለን፡፡ መፅሃፍ ቅዱስ በየእለቱ ልባችንን እንድንመረምረ ልባችንን እንድንፈትሽ በራሳችን ላይ እንድንፈርድ እና ቶሎ እንድንመለስ የሚያስተምረን ስለዚህ ነው፡፡

ወንድሞች ሆይ፥ ምናልባት ሕያው እግዚአብሔርን የሚያስክዳችሁ ክፉና የማያምን ልብ ከእናንተ በአንዳችሁ እንዳይኖር ተጠንቀቁ፤ ነገር ግን ከእናንተ ማንም በኃጢአት መታለል እልከኛ እንዳይሆን፥ ዛሬ ተብሎ ሲጠራ ሳለ፥ በእያንዳንዱ ቀን እርስ በርሳችሁ ተመካከሩ፤ ወደ ዕብራውያን 3፡12-13

ልባቸው እግዚአብሄርን ወደመካድ እና ወደአለማመን የተለወጡ ሰዎች በአንድ ጊዜ እግዚአብሄርን የሚያምኑ መልካም ልብ የነበራቸው ሰዎች ነበሩ፡፡ ነገር ግን የልባቸውን ንፅህና ለመጠበቅ ቸልተኛ በመሆናቸው በእኔ ላይ አይደርስም ብለው በትእቢት ስላሰቡ ወድቀዋል፡፡

ሄዋን መልካም ሴት ነበረች፡፡ ሃሳብዋ ቅን ልብዋም ንፁህ ነበር፡፡ ነገር ግን ይህን ቅንነትና ንፅህናዋን የሚጠብቅላትን የእግዚአብሄርን ቃል ከምሰማት ይልቅ የሰይጣንን ቃል ሰማች፡፡ የምትሰማውን ማንኛውም ተቃራኒ ቃል በእግዚአብሄር ቃል ፈትና ከመጣል ይልቅ ታስተናግደው ጀመረች፡፡ የልብንም ስሜትና አሳብ ለሚመረምረው ለእግዚአብሄር ቃል ራስዋን ሙሉ በሙሉ ስላልሰጠች ወደቀች፡፡  

የእግዚአብሔር ቃል ሕያው ነውና፥ የሚሠራም፥ ሁለትም አፍ ካለው ሰይፍ ሁሉ ይልቅ የተሳለ ነው፥ ነፍስንና መንፈስንም ጅማትንና ቅልጥምንም እስኪለይ ድረስ ይወጋል፥ የልብንም ስሜትና አሳብ ይመረምራል፤ እኛን በሚቆጣጠር በእርሱ ዓይኖቹ ፊት ሁሉ ነገር የተራቆተና የተገለጠ ነው እንጂ፥ በእርሱ ፊት የተሰወረ ፍጥረት የለም።ወደ ዕብራውያን 4፡12-13

የምናስበው ሃሳብ እንደእግዚአብሄር ሃሳብ እንደሆነ ልናደርግ ያሰብነው ነገር በመልካም ልብ አነሳሽነት /motive/ እንደሆነ የልባችንን ንፅህና በትጋት መከታተል ቀዳሚው ሃላፊነታችን ነው፡፡ ቃሉ በሃሳባችን በልባችን መነሻ ሃሳብ ላይ ብርሃን በማብራት ከእርሱ ወይስ ከጠላት እንደሆነ እውነተኛ ማንነቱን ያሳየናል፡፡

ስለዚህ ርኵሰትን ሁሉ የክፋትንም ትርፍ አስወግዳችሁ፥ ነፍሳችሁን ማዳን የሚችለውን በውስጣችሁም የተተከለውን ቃል በየዋህነት ተቀበሉ። የያዕቆብ መልእክት 1፡21

በኑሮዋችን በስራችን በአገልግሎታቸን እግዚአብሄርን ማየት ከፈለግን በትጋት ልባችንን መጠበቅ የእኛ የዘወትር ግዴታ ነው፡፡

ልበ ንጹሖች ብፁዓን ናቸው፥ እግዚአብሔርን ያዩታልና። የማቴዎስ ወንጌል 5፡8

አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa