Popular Posts

Thursday, May 31, 2018

በሚያጠፋውም እንደ ጠፉ አታንጐርጕሩ

ከእነርሱም አንዳንዶቹ እንዳንጎራጎሩ በሚያጠፋውም እንደ ጠፉ አታንጐርጕሩ። 1ኛ ቆሮንቶስ 10፡10
የእስራኤል ህዝብ በእግዚአብሄር መሪነት ደስተኛ አልነበሩም፡፡ የእስራኤል ህዝብ እግዚአብሄር እንደዚህ አድርጎ ሊይዘን አይገባም ነበር የሚል ጥያቄ ነበራቸው፡፡ የእስራኤል ህዝብ እግዚአብሄር ከዚህ በላይ ሊያደርግልን ይገባል የሚል ቅሬታ ነበራቸው፡፡ የእስራኤል ህዝብ እግዚአብሄ ጠላቶቻችንን እንደዚህ ነበር ማድረግ የነበረበት የሚል የተለየ ሃሳብ አላቸው፡፡ የእስራኤልክ ህዝብ እግዚአብሄር እንደሚገባን አልተንከባከበንም የሚል ጥያቄ ነበራቸው፡፡ ሰው የሚያንጎራጉረው በመሪው ላይ ጥያቄ ሲኖረው ነው፡፡  
ሰው በሚስቴ በባሌ ደስተኛ እይደለሁም ሲል አልገረምም፡፡ ሰው በፍፁሙ በእግዚአብሄር መሪነት ላይ ጥያቄ ካለው ሚስት በባልዋ መሪነት ላይ ጥያቄ ባይኖራት ይገርማል እንጂ የማይገባት ነገር ስላለ አያስገርምም፡፡ ሰው በእግዚአብሄር መሪነት ላይ አቃቂር የሚያወጣ ሰው በሰው መሪነት ላይ አቃቂር ቢያወጣ አያስገርምም፡፡ ሁላችንም በምናውቃቸው ሰዎች መሪነት ላይ አቃቂር ማውጣት እንችላለን፡፡  
የሚያንጎራጉር ሰው በህይወቱ ለሰይጣን በር እየከፈተ ይሄዳል፡፡ የሚያንጎራጉር ሰው የእግዚአብሄርን መንፈስ እያሳዘነ ይሄዳል፡፡ የሚያንጎራጉር ሰው እደከመ መቋቋም እያቃተው ይሄዳል፡፡ ስለዚህጅ ነው መፅሃፍ ቅዱስ በግልፅ አታንጎራጉሩ የሚለው፡፡
ማንጎራጎር ተስፋ መቁረጥ ነው
ማንጎራጎር ተስፋን አለማየት ነው፡፡ ማንጎራጎር ጨለማ ነው፡፡ ማንጎራጎር ተስፋ ቢስነት ነው፡፡
እኔ ግን ሁልጊዜ ተስፋ አደርጋለሁ፥ በምስጋናህም ሁሉ ላይ እጨምራለሁ። መዝሙር 71፡14
ማንጎራጎር እግዚአብሄር እውነተኛ ዳኛ መሆኑን መርሳት ነው
ማንጎራጎር እግዚአብሄር በወቅቱ እንደማየፈርድ መጠራጠር ነው፡፡ ማንጎራጎር አግዚአብሄር ለመፍረድ የሆነ ነገር እንደጎደለው ማሰብ ነው፡፡  
ሕግን የሚሰጥና የሚፈርድ አንድ ነው፤ እርሱም ሊያድን ሊያጠፋም የሚችል ነው፤ በሌላው ግን የምትፈርድ አንተ ማን ነህ? ያዕቆብ 4፡12
ማንጎራጎር እግዚአብሄርን አለማመስገን ነው
የሚያንጎራጉር ሰው የእግዚአብሄር ምስጋና ያነሰበት ሰው ነው፡፡ የሚያንጎራጉር ሰው የእግዚአብሄርን መልካምነት ያልተረዳ ሰው ነው፡፡ የሚያንጎራጉር ሰው የእግዚአብሄርን አሰራር የማያውቅ ሰው ነው፡፡ የሚያንጎራጉር ሰው የእግዚአብሄርን እርምጃ ያልተረዳ ሰው ነው፡፡  
በሁሉ አመስግኑ፤ ይህ የእግዚአብሔር ፈቃድ በክርስቶስ ኢየሱስ ወደ እናንተ ነውና። 1ኛ ተሰሎንቄ 5፡17-18
ማንጎራጎር በእግዚአብሄር ደስ አለመሰኘት ነው
በእግዚአብሄር ደስ የተሰኘ ሰው ጥያቄውን ዋጥ ያደርገዋል እንጂ ለማንጎራጎር አፉን ለመክፈት አይደፍርም፡፡
ማንጎራጎር በሰው ቁጣ የእግዚአብሄርን ፅድቅ የመስራት ከንቱ ሙከራ ነው፡፡
ማንጎራጎር በእግዚአብሄር መታመን አይደለም፡፡ ማንጎራጎር በራስ ችሎታ መታመን ነው፡፡ ማንጎራጎር የስጋ ክንፍ ነው፡፡  
ስለዚህ፥ የተወደዳችሁ ወንድሞቼ ሆይ፥ ሰው ሁሉ ለመስማት የፈጠነ ለመናገርም የዘገየ ለቍጣም የዘገየ ይሁን፤ የሰው ቍጣ የእግዚአብሔርን ጽድቅ አይሠራምና። ያእቆብ 1፡19-20
ማንጎራጎር የእግዚአብሄርን መሪነት ጥያቄ ውስጥ መክተት ነው
ምድርን እና ሞላዋን ለራሱ ክብር የፈጠረና እያስተዳደር ያለ ባለቤት እያለ የሚያንጎራጉር ሰው እግዚአብሄር መምራት በትክክል አልቻለም እያለ ነው፡፡ የሚያንጎራጉር ሰው መሪነቱን ከእግዚአብሄር ተቀብሎ በተሻለ ለማምራት እየተፈተነ ነው፡፡
ማንጎራጎር ባለን ነገር ላይ ሳይሆን በጎደለን ነገር ላይ ማተኮር ነው
እግዚአብሄር በህይወታችን ያደረጋቸው ከቁጥር የበዙ ታእምራቶች እያሉ አልሆነልኝም በምንለው ነገር ላይ ማተኮር ማጉረምረምን ያመጣል፡፡
የማይመረመረውን ታላላቅ ነገር፥ የማይቈጠረውንም ተአምራት ያደርጋል። ኢዮብ 9፡10
ማንጎራጎር እኔ አውቃለሁ ባይነት ነው
የሚያንጎራጉር ሰው ከእርግዚአብሄር በላይ እንደሚያውቅ የተሰማው ሰው ነው፡፡ የሚያንጎራጉር ሰው እግዚአብሄርን ሊመክርው የሚዳዳው ሰው ነው፡፡ የሚያንጎራጉር ሰው በእግዚአብሄር ያልተረዳውነ አንድ ነገር ያገኘ የመሰለው ሰው ነው፡፡
ማንም አንዳች የሚያውቅ ቢመስለው ሊያውቅ እንደሚገባው ገና አላወቀም፤ 1ኛ ቆሮንቶስ 8፡2
በፊቱ ሙግቴን አዘጋጅ ነበር፥ አፌንም በማስረጃ እሞላው ነበር። የሚመልስልኝም ቃል ምን እንደ ሆነ አውቅ ነበር፥ የሚለኝንም አስተውል ነበር። ኢዮብ 23፡4-5
ማንጎራጎር ትእቢት ነው
ማንጎራጎር ሰው ከሚገባው በላይ በትእቢት ማሰብ ነው፡፡   
ለጣዖት ስለ ተሠዋ ሥጋም፥ ሁላችን እውቀት እንዳለን እናውቃለን። እውቀት ያስታብያል ፍቅር ግን ያንጻል። 1ኛ ቆሮንቶስ 8፡1
ማንጎራጎር እግዚአብሄርን አለመፍራት ነው፡፡
እግዚአብሄርን በትክክል የማያውቀው ሰው ይዳፈረዋል፡፡ እግዚአብሄርን የሚዳፈር ሰው ለማንጎራጎር ቅርብ ነው፡፡ እግዚአብሄርን የሚፈራ ሰው ላለማንጎራጎር የሚጠይቀውን ሁሉ ያደርጋል፡፡
ሰው ዝም ብሎ የእግዚአብሔርን ማዳን ተስፋ ቢያደርግ መልካም ነው። ሰቆቃው ኤርምያስ  3፥29
ተስፋ የሆነው እንደ ሆነ አፉን በአፈር ውስጥ ያኑር።  ሰቆቃው ኤርምያስ 3፥26
ያዕቆብ ሆይ፥ እስራኤልም ሆይ፦ መንገዴ ከእግዚአብሔር ተሰውራለች ፍርዴም ከአምላኬ አልፋለች ለምን ትላለህ? ለምንስ እንዲህ ትናገራለህ? አላወቅህምን? አልሰማህምን? እግዚአብሔር የዘላለም አምላክ፥ የምድርም ዳርቻ ፈጣሪ ነው፤ አይደክምም፥ አይታክትም፥ ማስተዋሉም አይመረመርም። ኢሳያስ 40፡27-28
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ማካፈል share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ኢየሱስ #ጌታ #አመስግኑ #መልካም #እምነት #አታንጎራጉሩ #አታጉረምርሙ #ቃልኪዳን #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #የዘላለምህይወት #ቸር #መንፈስ #መንፈስቅዱስ

No comments:

Post a Comment