Popular Posts

Sunday, April 26, 2020

በምድር ያለነው


በተለያየ ጊዜ በህይወታችን የተለያዩ ተግዳሮቶች ይመጣሉ፡፡ ታዲያ ይህን አልፈው ይሆን ብለን የምናስብበት ውጥረት በህይወታችን ይመጣል፡፡ እንደዚህ አይነት ውጥረት በህይወታችን ሲገጥመን "በምድር ላይ ያለሁት ለምንድነው?" ብለን ይህን ጥያቄ ከልባችን እንጠይቃለን፡፡
በምድር ላይ ያለሁት ለምንድነው? የሚለው ጥያቄ ሁል ጊዜ መጠየቅና በትክክል መመለስ ያለበት ጥያቄ ነው፡፡
እውነት ግን በምድር ላይ ያለነው ለምንድነው?
የማንሞተው ለምንድነው ? ወይም መሞት የማንፈልገው ለምንድነው ?
በምድር ላይ ያለነው ስላልሞትን ነው ? ወይስ በምድር ላይ ስለመኖራችን ሌላ አለማ አለ?
እግዚአብሄር ሰውን የፈጠረው አስቦና አቅዶና በአላማ ነው፡፡
እግዚአብሔርም አለ፦ ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር፤ የባሕር ዓሦችንና የሰማይ ወፎችን፥ እንስሳትንና ምድርን ሁሉ፥ በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትንም ሁሉ ይግዙ። እግዚአብሔርም ሰውን በመልኩ ፈጠረ፤ በእግዚአብሔር መልክ ፈጠረው፤ ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው። ኦሪት ዘፍጥረት 1፡26-27
ወደምድር ከመምጣታችን በፊት ወደምድር የመጣንበት ልዩ አላማ ነበር፡፡
ማንም ሰው በድንገት ውይም በአጋጣሚ በምድር ላይ የተወለደ ሰው የለም፡፡ ሰው በምድር ላይ የመወለዱ ምልክት ከመወለዱ በፊት የተወለደበት ልዩ አላማ የመኖሩ ምልክት ነው፡፡
ለእናንተ የማስባትን አሳብ እኔ አውቃለሁ፤ ፍጻሜና ተስፋ እሰጣችሁ ዘንድ የሰላም አሳብ ነው እንጂ የክፉ ነገር አይደለም። ኤርሚያስ 29፡11
እኛ በምድር ላይ ለመኖር ከምንፈልገው በላይ እግዚአብሄር በምድር ላይ እንድንኖር ይፈልጋል፡፡ በምድር ላይ ለመኖር ካለን ፍላጎት በላይ በምድር ላይ እንድንኖር የተፈለገበት የእግዚአብሄር አላማ ይበልጣል፡፡
በሰው ልብ ብዙ አሳብ አለ፤ የእግዚአብሔር ምክር ግን እርሱ ይጸናል። ምሳሌ 19፡21
በመጀመሪያ መጨረሻውን፥ ከጥንትም ያልተደረገውን እነግራለሁ፤ ምክሬ ትጸናለች ፈቃዴንም ሁሉ እፈጽማለሁ እላለሁ። ኢሳያስ 46፡10
ይህን በህይወታችን ላይ ያለውን የእግዚአብሄርን አላማ ስንረዳ እናርፋለን፡፡
እግዚአብሄር እንዴት እንደሚወደን ስንረዳ እና በህይወት ለመኖራችን ልዩ አላማ እንዳለው ስንረዳ ከፍርሃት ነፃ እንወጣለን፡፡
እኛ ፍጥረቱ ነንና፤ እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ በክርስቶስ ኢየሱስ ተፈጠርን። ኤፌሶን 2፡10
ፍጹም ፍቅር ፍርሃትን አውጥቶ ይጥላል እንጂ በፍቅር ፍርሃት የለም፥ ፍርሃት ቅጣት አለውና፤ የሚፈራም ሰው ፍቅሩ ፍጹም አይደለም። እርሱ አስቀድሞ ወዶናልና እኛ እንወደዋለን። 1ኛ የዮሐንስ መልእክት 4፡18-19
ፍርሃት የእግዚአብሄርን ፍቅር የመረዳታችንን ደረጃ ያመለክታል፡፡ እግዚአብሄር በህይወታችን ያለውን የፍቅር አላማ በተረዳን መጠን ፍርሃት ከህይወታችን ቦታ እያጣ ይሄዳል፡፡  
የእግዚአብሄርን ፍቅር በተረዳን መጠን ከፍርሃት ነፃ እንወጣለን፡፡ እግዚአብሄር እንዴት በፍቅር እንደሚያየን በህይወታች ላይ ያለውን የእግዚአብሄርን የፍቅር አላማ እየተረዳን ስንመጣ በፍርሃት ሳይሆን በፍቅር እንንቀሳቀሳለን፡፡
የእግዚአብሄርን የፍቅር አለማ ስንረዳ የሚያንቃቅሰን ፍርሃት ሳይሆን ፍቅር ብቻ ይሆናል፡፡
በእኔ ላይ ያለው ዓላማውም ፍቅር ነው። መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን 2፡4
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.dinsa.37/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ኢየሱስ #ጌታ #ራእይ #እይታ #አላማ #ተስፋ #ፍፃሜ #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ተስፋ #ፍፃሜ #የእግዚአብሄርሃሳብ #የእግዚአብሄርእቅድ #የእግዚአብሄርፈቃድ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

ለእናንተ የማስባትን አሳብ እኔ አውቃለሁ፤ ፍጻሜና ተስፋ እሰጣችሁ ዘንድ የሰላም አሳብ ነው እንጂ የክፉ ነገር አይደለም። ትንቢተ ኤርምያስ 29፡11


Thursday, April 23, 2020

እንዲህም ይሆናል፤ የአምላክህን የእግዚአብሔርን ቃል ብትሰማ፥ ዛሬም ያዘዝሁህን ትእዛዙን ሁሉ ብታደርግ ብትጠብቅም፥ አምላክህ እግዚአብሔር ከምድር አሕዛብ ሁሉ ላይ ከፍ ከፍ ያደርግሃል። የአምላክህንም የእግዚአብሔርን ቃል ብትሰማ እነዚህ በረከቶች ሁሉ ይመጡልሃል ያገኙህማል። አንተ በከተማ ቡሩክ ትሆናለህ፥ በእርሻም ቡሩክ ትሆናለህ። የሆድህ ፍሬ፥ የምድርህም ፍሬ፥ የከብትህም ፍሬ፥ የላምህም ርቢ፥ የበግህም ርቢ ቡሩክ ይሆናል። እንቅብህና ቡሃቃህ ቡሩክ ይሆናል። አንተም በመግባትህ ቡሩክ ትሆናለህ፥ በመውጣትህም ቡሩክ ትሆናለህ። እግዚአብሔርም በላይህ የሚቆሙትን ጠላቶችህን በፊትህ የተመቱ ያደርጋቸዋል፤ በአንድ መንገድ ይመጡብሃል፥ በሰባትም መንገድ ከፊትህ ይሸሻሉ። እግዚአብሔር በረከቱ በአንተ ላይ በጐተራህ በእጅህም ሥራ ሁሉ እንዲወርድ ያዝዛል፤ አምላክህ እግዚአብሔር በሚሰጥህም ምድር ይባርክሃል። የአምላክህን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ብትጠብቅ፥ በመንገዱም ብትሄድ፥ እግዚአብሔር እንደ ማለልህ ለእርሱ የተቀደሰ ሕዝብ አድርጎ ያቆምሃል። የምድር አሕዛብም ሁሉ የእግዚአብሔር ስም በአንተ ላይ እንደ ተጠራ አይተው ይፈሩሃል። እግዚአብሔርም እርስዋን ይሰጥህ ዘንድ ለአባቶችህ በማለላቸው በምድርህ ላይ፥ በሆድህ ፍሬ፥ በከብትህ ፍሬ፥ በእርሻህም ፍሬ፥ እግዚአብሔር በጎነቱን በላይህ ያበዛል። እግዚአብሔርም ለምድርህ በወራቱ ዝናብ ይሰጥ ዘንድ፥ የእጅህንም ሥራ ሁሉ ይባርክ ዘንድ መልካሙን መዝገብ ሰማዩን ይከፍትልሃል፤ ለብዙ አሕዝብም ታበድራለህ፥ አንተ ግን ከማንም አትበደርም። ዛሬም ያዘዝሁህን የአምላክህን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ሰምተህ ብትጠብቃት ብታደርጋትም፥ ዛሬም ካዘዝሁህ ከእነዚህ ቃሎች ወደ ቀኝ ወደ ግራም ፈቀቅ ባትል፥ ታመልካቸውም ዘንድ ሌሎችን አማልክት ባትከተል፥ እግዚአብሔር ራስ ያደርግሃል እንጂ ጅራት አያደርግህም፤ ሁልጊዜም በላይ እንጂ በታች አትሆንም። ኦሪት ዘዳግም 28፡1-14


Tuesday, April 14, 2020

በሰው ከመታመን ይልቅ በእግዚአብሔር መታመን ይሻላል። መዝሙረ ዳዊት 118:8

በሰው ከመታመን ይልቅ በእግዚአብሔር መታመን ይሻላል። መዝሙረ ዳዊት 118:8

Saturday, April 4, 2020

ያየውን ወንድሙን የማይወድ ያላየውን እግዚአብሔርን ሊወደው እንዴት ይችላል?


ማንም፦ እግዚአብሔርን እወዳለሁ እያለ ወንድሙን ቢጠላ ሐሰተኛ ነው፤ ያየውን ወንድሙን የማይወድ ያላየውን እግዚአብሔርን ሊወደው እንዴት ይችላል? 1 የዮሐንስ መልእክት 4:20
ፍቅር ረቂቅ ሃሳብ ነው፡፡ ሰው እግዚአብሄርን እወደዋለሁ ቢል እግዚአብሄርን አትወድም ብለን መከራከር አንችልም፡፡ ሰው እግዚአብሄርን እወዳለሁ ሲል እውነተኝነቱን በቀጥታ ለማረጋገጥ ቀላል አይደለም፡፡ ምክኒያቱም ፍቅር የልብ ስለሆነና የሰው ልብ ደግሞ ተከፍቶ ስለማይታይና ስለማይታወቅ ነው፡፡
ፍቅር የልብ መሰጠት ስለሆነ ሰው እግዚአብሄርን መውደዱ የሚረጋገጥበት ቀጥተኛ መንገድ የለም፡፡ ሰው እግዚአብሄርን መውደዱንና አለመውደዱን በቀጥታ ሳይሆን በተዘዋዋሪ የሚያመለክቱ ነገሮች ግን አሉ፡፡ እኛም እግዚአብሄርን እንዴት እንድምንወድ የምንፈትንባቸው ሌሎች መንገዶች አሉ፡፡
ሰው እግዚአብሄርን መውደዱ መለኪያው ሰውን መውደዱ ነው፡
ሰውን የመውደድ ጥቂቱን መመዘኛ የማያማላ ሰው እግዚአብሄርን እወዳለሁ ቢል ውሸቱን ነው፡፡ ሰው የሚያየውን ሰው ካልወደደ የማያየውን እግዚአብሄርን እንደማይወድ በቂ ማረጋገጫ ነው፡፡
ለሰው ቅርቡ የሚያየውን ሰውን መውደድ ነው፡፡ ለሰው የሚቀለው ለሚያየው ሰው መልካምን ማድረግ ነው፡፡ ለሰው የሚቀለው የሚያየውን ሰውን በርህራሄ ማየት ነው፡፡ ለሰው የሚቀለው የሚያየውን የሚዳስሰውን ሰውን መቀበል ነው፡፡ ለሰው የሚቀለው የሚያየውን ሰውን መታገስ ነው፡፡ ለሰው የሚቀለው ከሚያየውን ሰው ጋር በትህትና መኖር ነው፡፡
ሰው እግዚአብሄርን እወዳለሁ እግዚአብሄርን አከብራለሁ የሚለው ለእግዚአብሄር ያለን አክብሮት ለሰው እንዳለን አክብሮት በቀጥታ የማይታይ ስለሆነ ይሆናል፡፡ ሰው ለእግዚአብሄር ፍቅር አለኝ የሚለው ስለማይታይ ይሆናል፡፡ ሰው በእግዚአብሄር ፊት ትሁት ነኝ የሚለው በቀጥታ ትህትናው በቀጥታ ስለማይለካ ይሆናል፡፡
ሰው ለሚያየው ሰው መልካምን ካላደረገ ለእግዚአብሄር መልካም ያደርጋል ማለት ዘበት ነው፡፡ ሰው የሚያየውን ሰውን ካልተቀበለ የማያየውን እግዚአብሄርን ይቀበላል ማለት ውሸት ነው፡፡ ሰው የሚያየውን ሰውን በርህራሄ ካላየ የማያየውን እግዚአብሄርን ይወዳል ማለት ከንቱ ነው፡፡ ሰው የሚያየውን ሰው ካልታገሰ እግዚአብሄርን እታገሳለሁ ማለቱ ከእውነት የራቀ ነው፡፡ ሰው ከሚያየው ከሰው ጋር በትህትና መኖር ካልቻለ እኔ በእግዚአብሄር ፊት ትሁት ነኝ ቢል ተታልሎዋል፡፡
ማንም፦ እግዚአብሔርን እወዳለሁ እያለ ወንድሙን ቢጠላ ሐሰተኛ ነው፤ ያየውን ወንድሙን የማይወድ ያላየውን እግዚአብሔርን ሊወደው እንዴት ይችላል? 1ኛ የዮሐንስ መልእክት 4:20
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.dinsa37/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ኢየሱስ #ጌታ #ሰላም #እምነት #ሃሳብ #ጥበብ #ማስተዋል #ፍቅር #ትህትና #ርህራሄ #መልካም #ጠብ #መልካም #ፍርድ #እውቅና #ፍፁም #ችግር #መፍትሄ #አላማ #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ  #እምነት #ቃል  #ማደስ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ