Popular Posts

Friday, July 19, 2019

መታዘዝ እንጂ መሥዋዕት እግዚአብሄርን ደስ አያሰኘውም



መሥዋዕትን ብትወድድስ በሰጠሁህ ነበር የሚቃጠለውም መሥዋዕት ደስ አያሰኝህም። የእግዚአብሔር መሥዋዕት የተሰበረ መንፈስ ነው፥ የተሰበርውንና የተዋረደውን ልብ እግዚአብሔር አይንቅም። መዝሙረ ዳዊት 51፡16-17
እውነተኛ አምልኮት በራስ ግምት እግዚአብሄርን ለማምለክ ከመሞከር ተስፋ መቁረጥ ነው፡፡ እውነተኛ አምልኮት በራስ መስዋእት ተስፋ ከመቁረጥ ይጀመራል፡፡ እውነተኛ አምልኮ መስዋእትን ማቅረብ ሳይሆን እግዚአብሄር የጠየቀንን ነገር ለመታዘዝ መስዋእት መሆን ነው፡፡
መሥዋዕትንና ቍርባንን አልወደድህም፤ ሥጋን አዘጋጀህልኝ፤ የሚቃጠለውንና ስለ ኃጢአት የሚቀርበውን መሥዋዕት አልሻህም። በዚያን ጊዜ አልሁ፦ እነሆ፥ መጣሁ፤ ስለ እኔ በመጽሐፍ ራስ ተጽፎአል፤ አምላኬ ሆይ፥ ፈቃድህን ለማድረግ ወደድሁ፥ ሕግህም በልቤ ውስጥ ነው። መዝሙረ ዳዊት 40፡6-8
እውነተኛ አምልኮ እግዚአብሄር ይህን ባቀርብለት መልካም ነው በማለት መስዋእትን ማቅረብ ሳይሆን እግዚአብሄር እንድናደርግ ያዘዘንን ያንን ብቻ መታዘዝ ነው፡፡ እውነተኛ አምልኮ የእግዚአብሄር ፈቃድ መሆኑን በልባችን የሰማነውን ነገር ማድረግ ነው፡፡
ሳሙኤልም፦ በውኑ የእግዚአብሔርን ቃል በመስማት ደስ እንደሚለው እግዚአብሔር በሚቃጠልና በሚታረድ መሥዋዕት ደስ ይለዋልን? እነሆ፥ መታዘዝ ከመሥዋዕት፥ ማዳመጥም የአውራ በግ ስብ ከማቅረብ ይበልጣል። መጽሐፈ ሳሙኤል ቀዳማዊ 15፡22
የአምልኮት መልክ ብቻ ያለው ሰው እግዚአብሄርን አያውቅም አይከተልም፡፡ የአምልኮት መልክ ብቻ ያለው ሰው ምህረትን አያውቅም አይከተልም፡፡ የአምልኮት መልክ ያለው ሰው እግዚአብሄርን መታዘዝን በራስ ግምት እግዚአብሄርን በስጦታ ለማስደሰት በመሞከር ይለውጠዋል፡፡ የአምልኮት መልክ የእውነተኛ መንፈሳዊነት ማስመሰያ ፌክ ነው፡፡
የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል፤ ከእነዚህ ደግሞ ራቅ። 2ኛ ወደ ጢሞቴዎስ 3፡5
የአምልኮት መልክ ብቻ ያለው ሰው የሃይማኖት ወጎችንና ስርአቶችን አይፈፅምም ማለት አይደለም፡፡ የአምልኮት መልክ ብቻ ያለው ሰው እንደ ማንኛውም አምላኪ የሃይማኖት ወጎችንና ስርአቶችን ይፈፅማል፡፡ የአምልኮት መልክ ብቻ ያለው ሰው በራሱ ግምት እግዚአብሄር ይሄን ሊፈልግ ይችላል እያለ በግምት መስዋእትን ያቀርባል፡፡ የአምልኮት መልክ ብቻ ያለው ሰው የእግዚአብሄርን ትእዛዝ ከማድረግ ውጭ ሃይማኖታዊ ወጎችንና ስርአቶችን ሁሉ ይፈፅማል፡፡
ከመሥዋዕት ይልቅ ምሕረትን፥ ከሚቃጠልም መሥዋዕት ይልቅ እግዚአብሔርን ማወቅ እወድዳለሁና። ትንቢተ ሆሴዕ 6፡6
የአምልኮት መልክ ብቻ ያለው ሰው መንገዱ በፊቱ የቀናች ትመስለዋለች፡፡ የአምልኮት መልክ ብቻ ያለው ሰው እግዚአብሄርን እያገለገለ ይመስለዋል፡፡ የአምልኮት መልክ ብቻ ያለው ሰው ስርአትና ወግ ስለፈፀመ ብቻ እግዚአብሄርን የሚያስደስት ይመስለዋል፡፡
እግዚአብሄር ግን ሰው እግዚአብሄርን አስደስትበታለሁ ብሎ  በሚገምተው የግምት መስዋእት አይደሰትም፡፡
የሰው መንገድ ሁሉ በዓይኑ ፊት የቀናች ትመስለዋለች፤ እግዚአብሔር ግን ልብን ይመዝናል። እግዚአብሔር ከመሥዋዕት ይልቅ ጽድቅንና ቅን ነገርን ማድረግ ይወድዳል። መጽሐፈ ምሳሌ 21፡2-3
እግዚአብሄር የሚፈልገውን ያውቃል፡፡ እግዚአብሄር ከሰው የሚፈልገው ከእግዚአብሄር ጋር መቆምን እግዚአብሄርን በቃሉ መታዘዝን ነው፡፡ እግዚአብሄር እውነተኛ መስዋእት የሚለው እርሱን ሰምቶ መታዘዝን እንጂ መልካም የሚመስልን ነገር ለእግዚአብሄር ማድረግን አይደለም፡፡ ለእግዚአብሄር ከምናደርግለት ብዙ መስዋእት ይልቅ ድምፁን በመታዘዛችን ይደሰታል፡፡
መሥዋዕትንና ቍርባንን አልወደድህም፤ ሥጋን አዘጋጀህልኝ፤ የሚቃጠለውንና ስለ ኃጢአት የሚቀርበውን መሥዋዕት አልሻህም። በዚያን ጊዜ አልሁ፦ እነሆ፥ መጣሁ፤ ስለ እኔ በመጽሐፍ ራስ ተጽፎአል፤ አምላኬ ሆይ፥ ፈቃድህን ለማድረግ ወደድሁ፥ ሕግህም በልቤ ውስጥ ነው። መዝሙረ ዳዊት 40፡6-8
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiydinsa7/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#የእግዚአብሄርምክር #የእግዚአብሔርፈቃድ #እግዚአብሔር #እንደተፃፈ #ማታዘዝ #መባ #መሥዋዕት ##እምነት #የሰውአሳብ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ህይወት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ 

የሰው መጠቀሚያ የመሆን ስሜት



እውነትም እያንዳንዳችን አንዳንዴ ሌላው ሰው ካላግባብ እንደተጠቀመብን ይሰማናል::
ከሰው ጋር እየኖረና እየሰራ ይህ አይነት ስሜት በየጊዜው የማይሰማው ሰው አይገኝም:: አንዳንዴ መሪው ተመሪው እንደተጠቀመበት ይሰማዋል:: ተመሪው  መሪው እንደተጠቀመበት ይሰማዋል:: አንዳንዴ ፓስተሩ ምእመኑ እንደተጠቀመበት ይሰማዋል:: ምእመኑ ፓስተሩ እንደተጠቀመበት ይሰማዋል:: አንዳንዴ አሰሪው ሰራትኛው እንደተጠቀመበት ይሰማዋል:: ሰራተኛው አሰሪው እንደተጠቀመበት ይሰማዋል::
አንዳንዴ እጅግ ቅርብ በሆኑት በባልና በሚስት ላይ እንኳን እንደዚህ አይነት ሌላው ተጠቀመበኝ ስሜት ይንፀባረቃል:: አንዳንዴ ሚስት ባልዋ እንደተጠቀመባት ይሰማታል:: ባል ሚስቱ እንደተጠቀምችበት ይሰማዋል::
እንዳንዴ ሌላው ተጠቀምብኝ የሚለውን ሁሉ ስንሰማ ይህ ሁሉ ጥቅም የት ገባ ብለን እንጠይቃለን::
እውነት ነው ድንበራችንን ካላወቅንና ካላሳወቅ ድንበራቸውን የማያውቁ እና ካላግባብ ሊጠቀሙብን የሚፈልጉ ሰዎች ይኖራሉ:: ነገር ግን ሌላው ሰው ተጠቀመብን የሚለውን ስሜታችንን ሁሉ ካመንነው ደግሞ ሰላማችንን እናጣለን::
ሌላው ተጠቀመብን የሚለው ስሜት ሁሌም ባይሆንም አንዳንዴ ከራስ ወዳድነትና ከስስት ይመጣል፡፡ እኛ ይበልጥ እንደለፋን ስናስብ መነጫነጭ እንጀምራለን፡፡ በማንኛውም አጋርነት አንተ ሃምሳ በመቶ እኔ ሃምሳ በመቶ እናዋጣለን ተብሎ የሚሰመርበት ሁኔታ የለም፡፡ በቃል ደረጃ እንለዋለን እንጂ አንዱ አንዳንድ ጊዜ ሰባ በመቶ የሚያዋጣበት ለዔላው ሃምሳ በመቶ የሚያዋጣበት ሁኔተ ይፈጠራል፡፡ በሌላ ጊዜ ድግሞ ሰላሳ በመቶ ያዋጣው ስልሳ በመቶ የሚያዋጣበትና ሌላው አርበና በመቲ የሚያዋጣበት ሁኔታ ደግሞ ይፈጠራል፡፡
የሰው ብድራት ያለው በእግዚአብሄር ዘንድ እንደሆነ የሚያምን ሰው ብዙ በማዋጣቱ እንደተጠቀመ ደስ እያለው ይሄዳል እንጂ አይነጫነጭም፡፡
ባሪያ ቢሆን ወይም ጨዋ ሰው፥ እያንዳንዱ የሚያደርገውን መልካም ነገር ሁሉ ከጌታ በብድራት እንዲቀበለው ታውቃላችሁና። ወደ ኤፌሶን ሰዎች 6፡8
ሰዎች ቢጠቀሙብን ብንበደል እንኳን የሚክሰን እግዚአብሄር አለ፡፡ ከመበደል መበደል ይሻላል፡፡
እንግዲህ ፈጽሞ የእርስ በርስ ሙግት እንዳለባችሁ በእናንተ ጉድለት ነው። ብትበደሉ አይሻልምን? ብትታለሉስ አይሻልምን? 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 6፡7
የሚያፅናናን ነገር ግን ሰው ሊጠቀምብን የሚፈልገው ጠቃሚ ስለሆንን ነው:: ከሌላ ሰው ጥቅም ያልፈለገው ሰው ከእኛ ጥቅም ቢፈልግ ሰውን መጥቀም መቻላችን በራሱ ክብራችን ነው፡፡
እንዲሁ እናንተ ደግሞ የታዘዛችሁትን ሁሉ ባደረጋችሁ ጊዜ፡የማንጠቅም ባሪያዎች ነን፥ ልናደርገው የሚገባንን አድርገናል፡ በሉ። የሉቃስ ወንጌል 17:10
ሰው ሊጠቀምብን የሚፈልገውም እንዳንጠቀምበት ፈርቶ ከስጋት ከመነጨ ስሜት ሊሆን ይችላል:: እንዳልተጠቀምንበት ስጋቱን የምንቀንሰው ገፋ አድርገን እንዲጠቀምብን ስንፈቅድለት ነው::
ማንም ሰው አንድ ምዕራፍ ትሄድ ዘንድ ቢያስገድድህ ሁለተኛውን ከእርሱ ጋር ሂድ። የማቴዎስ ወንጌል 5፡41
እግዚአብሄር በሰጠን ፀጋ ከሌላው ሰው እንደተሻልን የምናሳየውና በእግዚአብሄር የሚያስችል ሃይል የምንኩራራው ተጨማሪውን ምእራፍ በራሳችን ፈቃድ ስንሄድ ነው፡፡
የሆነ ሆኖ ተጠቀምክበትና ተጠቀመብህ የሚለው ጥያቄና ስሜት ቀላል መልስ ያለው  ጥያቄ አይደለም:: ሰውን እናንተ እንዳልተጠቀማችሁበት ወይም ሌላው እንደተጠቀመባቹ በንግግር ከማሳመን ይልቅ ክርክር ያስነሳውን ጥቅማችሁ የተባለውን ነገር መተው ይቀላል::
መፍቀድ የሌለባችሁ ግልፅ የሆነ አላግባበ መጠቀም ካልሆነ በስተቀር አግባብና አላግባብ የሆነውን መጠቀም ለመለየት ቀላል አይደለም፡፡ ስለዚህ ሰውን እናንተ እንዳልተጠቀማችሁበት ወይም ሌላው እንዳልተጠቀምባቹ በንግግር ከማሳመን ይልቅ ክርክር ያስነሳውን ጥቅማችሁ የተባለውን ነገር መተው ውጥረት ይቀንሳል ሰላምን ይሰጣል::
ቢቻላችሁስ በእናንተ በኩል ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ። ወደ ሮሜ 12:18
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.dinsa37/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ኢየሱስ #ጌታ #መሪ #ፀጋ #የሚያስችልሃይል #እውቀት #ምስጋና #ትህትና #ልብ #እምነት #ፀሎት #ማማጠን #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ትጋት #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

Thursday, July 18, 2019

የእግዚአብሔርን ባለጠግነት የምንካፈልበት ስልት



እግዚአብሄር ባለጠጋ አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሄር ሁሉ በእጁ ሁሉ በደጁ የሆነ የሚጎድለው የሌለ ባለጠጋ አምላክ ነው፡
እርሱ ባጠጋ ሆኖ ልጆቹ እንዲያጡና እንዲጎድላቸው የሚፈልግ አባት እንደሌለ ሁሉ እግዚአብሄር ልጆቹም ያጡትንና የጎደላቸውን ነገር ይው እንዲልምኑት ይፈልጋል፡፡ ልጆቹ ከእርሱ ባለጠግነት ሙሉ ለሙሉ ተጠቃሚ እንዲሆኑ እንደሚፈልግ አባት ሁሉ እግዚአብሄርም በፀሎት ከእግዚአብሄር ባለጠግነት ተካፋይ እንዲሆኑ ይፈልጋል፡፡
ልጆቹ ከእርሱ ባለጠግነት እንዲካፈሉ የሚፈልግ ጌታ የሰው ልጆች እንዲፀልዩ በብዙ ቦታዎች ያበረታታል፡፡ መፅሃፍ ቅዱስ እግዚአብሄርን ያየው አንዳች እንኳን የለም በእቅፉ ያለው አንድ ልጁ ተረከው እንደሚል ኢየሱስ የእግዚአብሄርን ልብ ሲተርከው ሰዎች መፀለይ እንዳለባቸው በብዙ ቦታዎች በምሳና ካለ ምሳሌ በተደጋጋሚ ሲያስተምር እንመለከታለን፡፡  
በእኔ ብትኖሩ ቃሎቼም በእናንተ ቢኖሩ የምትወዱትን ሁሉ ለምኑ ይሆንላችሁማል። የዮሐንስ ወንጌል 15፡7
ሳይታክቱም ዘወትር ሊጸልዩ እንዲገባቸው የሚል ምሳሌን ነገራቸው፥ እግዚአብሔር እንኪያስ ቀንና ሌሊት ወደ እርሱ ለሚጮኹ ለሚታገሣቸውም ምርጦቹ አይፈርድላቸውምን? እላችኋለሁ፥ ፈጥኖ ይፈርድላቸዋል። ነገር ግን የሰው ልጅ በመጣ ጊዜ በምድር እምነትን ያገኝ ይሆንን? የሉቃስ ወንጌል 18፡1፣7-8
እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብ በስሜ የምትለምኑትን ሁሉ ይሰጣችኋል። እስከ አሁን በስሜ ምንም አልለመናችሁም፤ ደስታችሁ ፍጹም እንዲሆን ለምኑ ትቀበሉማላችሁ። የዮሐንስ ወንጌል 16፡23-24
ኢየሱስ ስለፀሎት ያስተማረበትን ስንመለከት እግዚአብሄር ለልጆቹ ያልውን ቅናት እንመለከታለን፡፡ ልጆቹ ምን የመሰለ አባት በሰማይ እያላቸው ባለመለመናቸው ብቻ ከእግዚአብሄር ባለጠግነት ተካፋዮች አለመሆናቸውን አይቶ ይቀናል፡፡ ኢየሱስ ስለፀሎት ያስተማረውን ስንመለከት ልጆቹ ቶሎ ስለፀሎት ተረድተው እንዲፀልዩና ከእግዚአብሄር ባለጠግነት ተካፋይ እንዲሆኑ የቀናላቸውን የእግዚአብሄርን ቅናት እናስተውላለን፡፡
እስከ አሁን በስሜ ምንም አልለመናችሁም፤ የዮሐንስ ወንጌል 16፡24
እንደ እውነቱ ከሆነ መፀለይና መቀበል የሚገባንን ያህል አልተቀበልንም፡፡ የእግዚአብሄር ግምጃ ቤት ሙሉ ነው፡፡  
ለምኑ፥ ይሰጣችሁማል፤ ፈልጉ፥ ታገኙማላችሁ፤ መዝጊያን አንኳኩ፥ ይከፈትላችሁማል። የሚለምነው ሁሉ ይቀበላልና፥ የሚፈልገውም ያገኛል፥ መዝጊያንም ለሚያንኳኳ ይከፈትለታል። የማቴዎስ ወንጌል 7፡7-8
ብዙ ክርስትያኖች እግዚአብሄር አባታቸው ባለጠጋ ሆኖ እነርሱ ግን በጉድለት የሚኖሩበት ምክኒያት ለመፀለይ በመጀመሪያ ራሳቸውን ስለሚያዩ ነው፡፡ እግዚአብሄር በቃሉ እንደ ደሞዛችሁ መጠል ለምኑ ፣ እንደ ገቢያቹ መጠን ለምኑ ፣ እንደ ባንክ ሂሳባችሁ መጠን ለምኑ ያለ ይመስላቸዋል፡፡
እግዚአብሄር ግን ያው ለምኑ ነው፡፡ እግዚአብሄር የሚያበረታን ካለምንም ቅድመ ሁኔታ እንድንለምን ነው፡፡
ሲጀመር የሚለምን ሰው የሚለመነው ነገር ያለው ሰው አይደለም፡፡ የሚለምን ሰው የጎደለው የሌለው ሰው ነው፡፡ የሚለምን ሰው እንዲኖረው የሚፈልግ እንጂ ያለው ሰው አይደለም፡፡  
ያለመቀበላችን ምክኒያት አለመለመናችን ነው፡፡
ነገር ግን አትለምኑምና ለእናንተ አይሆንም፤ የያዕቆብ መልእክት 4፡2
ለምኑ፥ ይሰጣችሁማል፤ ፈልጉ፥ ታገኙማላችሁ፤ መዝጊያን አንኳኩ፥ ይከፈትላችሁማል። የሚለምነው ሁሉ ይቀበላልና፥ የሚፈልገውም ያገኛል፥ መዝጊያንም ለሚያንኳኳ ይከፈትለታል። የማቴዎስ ወንጌል 7፡7-8
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.dinsa.37/notes
#ኢየሱስ #ጌታ #እግዚአብሔር #ለምኑ #ፈልጉ #አንኳኩ #ይቀበላል #ያገኛል #ይከፈትለታል #ቃል #ብልፅግና #ሃብት #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #የእግዚአብሄርቃል  #የእግዚአብሔርፈቃድ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

Wednesday, July 17, 2019

በጣም የጓጓንለት ነገር ያሳፍረናል


ለአንድ ነገር በጣም መጓጓት ለነገሩ ያለንን የእውቀት ማነስ ሊያሳይ ይችላል:: ለአንድ ነገር ያለን መጓጓት ግምት አሰጣጣችን መዛባቱን ከማሳየቱም በላይ ይፍጠንም ይዘግይም እንደሚያሳዝነን እርግጥ ነው::

ከሰማይ በታች የሚያጓጓ ነገር የለም:: ከሰማይ በታች አዲስ ነገር የለም:: አዲሱ ነገር ጌታ ኢየሱስ ብቻ ነው:: አዲሱ ነገር በፍቅር መኖር ነው:: አዲሱ ነገር ጌታንና ሰውን መውደድ ነው:: አዲሱ ነገር ጌታን መከተልና ማምለክ ነው::
ከጌታ ውጭ በጣም የሚያጓጓ ምንም ነገር የለም::
የሆነው ነገር እርሱ የሚሆን ነው፥ የተደረገውም ነገር እርሱ የሚደረግ ነው፤ ከፀሐይም በታች አዲስ ነገር የለም። መጽሐፈ መክብብ 1:9
ሰው ሰውን የማገልገል ሀላፊነቱን ከተረዳው ስለ ስልጣን በጣም አይጓጓም::
ሰው ከዝነኝነት ጋር ተያይዞ የሚመጣው ሀላፊነትተረዳ የዝነኝነት ጥቅም ያን ያህል አያጓጓውም::
ሰው ሀይሉን በሚገባው ቦታ ላይ ብቻ የማዋል ከፍተኛ ሀላፊነት እንደተጫነበት የሚርዳ ሰው ሃይል እና ስልጣን  ለማግኘት አይቸኩልም:: ስልጣን ጥቅም ብቻ ሳይሆን የማገልገል ሃላፊነትም እንደሆነ የተረዳ ሰው ስልጣንን ያን ያህል አይመኝም፡፡
የትዳርን ጥቅሙን ብቻ ሳይሆን ሃላፊነቱንም በሚገባ የተረዳ ሰው ተግዳሮቱን እንዳልተረዳው ሰው የብቸኝነት ጊዜውን ሳያጣጥል አክብሮ በሚገባ ይጠቀምበታል::
ከሚጠብቀው ነገር ውስጥ ጥቅም ብቻ የሚጠብቅና ሃላፊነቱን የማይረዳ ሰው በራሱ ይሰናከላል:: እያንዳንዱ ጥቅም ከሃላፊነት ጋር ይመጣል::
እያንዳንዱ አገር የራሱ ተግዳሮቶች እንዳሉት የማይረዳ ሰው አገርመለውጥ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከተግዳሮት ለማረፍ እጅግ ይጓጓል::
ለነገ ከመጠን በላይ የሚጓጓው እያንዳንዱ ቀን ከራሱ ጭንቀት ጋር አብሮ እንደሚመጣ የማያውቅ ሰው ብቻ::
ነገ ለራሱ ይጨነቃልና ለነገ አትጨነቁ፤ ለቀኑ ክፋቱ ይበቃዋል። የማቴዎስ ወንጌል 6:34
ከእግዚአብሄር ውጭ ሙሉ ትኩረታችንን ሊወስድ የሚገባው ምንም ነገር ሊኖር አይገባውም፡፡ ከእግዚአብሄር ውጭ በጣም የምንጓጓለት ነገር ከመጠን በላይ ስላጋነንነው ያስቀይመናል፡፡  
ለእግዚአብሄር ብቻ መስጠት ያለብንን ትኩረትሌላ ለምንም ነገር በመስጠት እግዚአብሄርን አንስቀናው ::
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.dinsa.37/notes
#ኢየሱስ #ጌታ #ዘላለማዊ #አዲስ #ልብ #ሰማይ #ዘላለም #ጌታ #ከፀሐይበታች #ያልፋሉ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #ወንጌል #መናገር #ፅናት #ትግስት #መሪ

Sunday, July 14, 2019

ዛሬ ካልሆነ መቼ?


ህይወት ደስ ይላል፡፡ ህይወት ምን ያህል እንደሚጣፍጥ የምናውቅው ልናጣው ስንል ነው፡፡ የህይወትን ክብር ይበልጥ የምንረዳው ከሞላ ጎደል አጥተነው ስናገኘው ነው፡፡
እግዚአብሄርን አሁን ካላመሰገነው መቼ እናመሰግነዋለን፡፡
ሲኦል አያመሰግንህምና፥ ሞትም አያከብርህምና፤ ወደ ጕድጓዱ የሚወርዱ እውነትህን ተስፋ አያደርጉም። እኔ ዛሬ አንደማደርግ ሕያዋን እነርሱ ያመሰግኑሃል፤ አባት ለልጆች እውነትህን ያስታውቃል። ትንቢተ ኢሳይያስ 38፡18-19
አንድ የእግዚአብሄር ሰው ሲናገር ለስኬት የሚያስፈልገው ቤት ብቻ ነው ይላል፡፡ ሲቀጥልም ለስኬት የሚያስፈልገው በስጋ ውስጥ መኖር ህያው መሆን በህይወት መኖር ብቻ ነው፡፡ በህይወት የሚኖር ሰው ለስኬት ተስፋ አለው፡፡ ሰው በምድር ላይ ለስኬት ተስፋው የሚያከትመው ከስጋ ከወጣ ብቻ ነው፡፡
አቤቱ፥ ሙታን የሚያመሰግኑህ አይደሉም፥ ወደ ሲኦልም የሚወርዱ ሁሉ፤ እኛ ሕያዋን ግን ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘላለም እግዚአብሔርን እንባርካለን፡፡ ሃሌ ሉያ። መዝሙረ ዳዊት 115፡17-18
እግዚአብሄርን ለማመስገን የሚያስፈልጉት ነገሮች ህያው መሆንና ህያው መሆን ብቻ ናቸው፡፡
ሃሌ ሉያ። እግዚአብሔርን በመቅደሱ አመስግኑት፤ በኃይሉ ጠፈር አመስግኑት። በችሎቱ አመስግኑት፤ በታላቅነቱ ብዛት አመስግኑት። በመለከት ድምፅ አመስግኑት፤ በበገናና በመሰንቆ አመስግኑት። በከበሮና በዘፈን አመስግኑት፤ በአውታርና በእምቢልታ አመስግኑት። ድምፁ መልካም በሆነ ጸናጽል አመስግኑት፤ እልልታ ባለው ጸናጽል አመስግኑት። እስትንፋስ ያለው ሁሉ እግዚአብሔርን ያመስግን፦ ሃሌ ሉያ። መዝሙረ ዳዊት 150፡1-6
እግዚአብሄርን ለማመስገን ቀን መቅጠር አያስፈልግም፡፡ እግዚአብሄርን ለማመስገን ምንም አይነት ቅድመ ሁኔታዎችን ማስቀመጥ አያስፈልግም፡፡ እግዚአብሄርን ለማመስገን አንዱና ብቸኛው ቅድመ ሁኔታ ህያው መሆን በህይወት መኖር ነው፡፡ እስትንፋስ ያለው ሁሉ እግዚአብሔርን ያመስግን፦ ሃሌ ሉያ።
ነገ ያንተ አይደለም፡፡ ዛሬን በህይወት የጠበቀህን ነገን ሊሰጥህ የሚችለውን እስትንፋስህን በእጁ የያዘውን እግዚአብሄርን ዛሬ አመስግን፡፡
አሁንም፦ ዛሬ ወይም ነገ ወደዚህ ከተማ እንሄዳለን በዚያም ዓመት እንኖራለን እንነግድማለን እናተርፍማለን የምትሉ እናንተ፥ ተመልከቱ፥ ነገ የሚሆነውን አታውቁምና። ሕይወታችሁ ምንድር ነው? ጥቂት ጊዜ ታይቶ ኋላ እንደሚጠፋ እንፍዋለት ናችሁና። በዚህ ፈንታ። ጌታ ቢፈቅድ ብንኖርም ይህን ወይም ያን እናደርጋለን ማለት ይገባችኋል። አሁን ግን በትዕቢታችሁ ትመካላችሁ፤ እንደዚህ ያለ ትምክህት ሁሉ ክፉ ነው። የያዕቆብ መልእክት 4፡13-16
እንግዲህ ዘወትር ለእግዚአብሔር የምስጋናን መሥዋዕት፥ ማለት ለስሙ የሚመሰክሩ የከንፈሮችን ፍሬ፥ በእርሱ እናቅርብለት። ዕብራውያን 13፡15
እስትንፋስ ያለው ሁሉ እግዚአብሔርን ያመስግን፦ ሃሌ ሉያ። መዝሙረ ዳዊት 150፡6
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ኢየሱስ #ጌታ #አመስግኑ #መልካም #እምነት #ቃልኪዳን #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #የዘላለምህይወት #ቸር #መንፈስ #መንፈስቅዱስ

Thursday, July 11, 2019

መንገዴ ከእግዚአብሔር ተሰውራለች


ያዕቆብ ሆይ፥ እስራኤልም ሆይ፦ መንገዴ ከእግዚአብሔር ተሰውራለች ፍርዴም ከአምላኬ አልፋለች ለምን ትላለህ? ለምንስ እንዲህ ትናገራለህ? አላወቅህምን? አልሰማህምን? እግዚአብሔር የዘላለም አምላክ፥ የምድርም ዳርቻ ፈጣሪ ነው፤ አይደክምም፥ አይታክትም፥ ማስተዋሉም አይመረመርም። ትንቢተ ኢሳይያስ 40፡27-28
እስራኤል ህይወቱ ቅርፅ አልባ ስለሆነበት መንገዴ ከእግዚአብሄር ተሰውራለች ሲል እንመለከተዋለን፡፡ እስራኤል ህይወቱ የተበታተነ እና የተወሳሰበ ስለሆነ ከዚህ ቅርፅ አልባ ህይወቱ ሊወጣ እንደማይችል አስቧል፡፡ እስራኤል ጥያቄው ውስብስብ በመሆኑ ሊፈታ እንደማይችል ተስፋ ቆርጧል፡፡ እስራኤል በህይወቱ ካሉ መልሶች ይልቅ ጥያቄዎቹ በዝተዋል፡፡
አሁንም እያንዳንዳችን አንዳንዴ ህይወታችን እንደተበታተነ ቅርፅ አልባ እንደሆነና የህይወታችንን መንገድ ማንበብ እንደማንችእል ይሰማናል፡፡ አንዳንዴ የህይወታችን ክር እንደተበተበና ውሉ እንደጠፋ እንደተወሳሰበ ይሰማናል፡፡
አንዳንዴ የህይወታችንን መንገድ ጫፉ እንደማይያዝ መጀመሪያውና መጨረሻው እንደማይታወቅ ይሆናል፡፡ የህይወታችንን እንቆቅልሽ መጀመሪያውንና መጨረሻ ማገናኘት ያቅተናል፡፡
ይህ ስሜት መርገም አይደለም፡፡ ይህ ስሜት ለእርዳታ እግዚአብሄርን እንድንፈልግ ትሁት የሚያደርግን ተፈጥሮአዊ ስሜት ነው፡፡ ይህ ስሜት ህይወታችንን በራሳችን እንደማንወጣው የሚያስታውሰን ስሜት ነው፡፡ ይህ ስሜት ህይወታችን በእግዚአብሄር እንጂ በእኛ እንዳልተያዝ የሚያስታውስን ስሜት ነው፡፡
የሕያዋን ሁሉ ነፍስ የሰውም ሁሉ መንፈስ በእጁ ናት። መጽሐፈ ኢዮብ 12፡10
ትንፋሽህንና መንገድህን ሁሉ በእጁ የያዘውን አምላክ አላከበርኸውም። ትንቢተ ዳንኤል 5፡23
ህይወታችንን ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ማወቅ የለብንም፡፡ የምናውቃቸው ነገሮች አሉ የማናውቃቸው ነገሮች አሉ፡፡ ሁሉንም ካወቅን እግዚአብሄር እንጂ ሰው ልንሆን አንችልም፡፡ ሁሉንም ነገር ካወቅን በእግዚአብሄር ላይ መታመን አያስፈልግም፡፡ ሁሉንም ነገር ማድረግ ከቻልን የእግዚአብሄር እርዳታ አያስፈልግም፡፡
ምሥጢሩ ለአምላካችን ለእግዚአብሔር ነው፤ የተገለጠው ግን የዚህን ሕግ ቃሎች ሁሉ እናደርግ ዘንድ ለእኛ ለዘላለምም ለልጆቻችን ነው። ኦሪት ዘዳግም 29፡29
ሁሉን በሚያውቅ በእግዚአብሄር ላይ መደገፍ ያለብን እኛ እውቀት ሁሉ ስለሌለን ነው፡፡
የእግዚአብሄር አምላካዊ መልስ ግን እንዲህ ይላል፡፡
እግዚአብሔር የዘላለም አምላክ፥ የምድርም ዳርቻ ፈጣሪ ነው፤ አይደክምም፥ አይታክትም፥ ማስተዋሉም አይመረመርም። ትንቢተ ኢሳይያስ 40፡27-28
አንተ አላወቅክም ማለት እግዚአብሄር አላወቀም ማለት አይደለም፡፡ አንተ የህይወትህ ንድፍ ዲዛይን የለህም ማለት እርሱ የለውም ማለት አይደለም፡፡  
አንተ የሚያስፈልግህ አንድ ነገር በምታውቅው እርምጃ እየወሰድክ በማታውቅው በሚያውቀውና ማስተዋሉ በማይመረመረው እግዚአብሄር ላይ መደገፍ ነው፡፡ እንደ እርሱ እንድትበረታ ፣ እንደ እርሱ እንድታስተውል ፣ እንደ እርሱ እንድታውቅና እንደ እርሱ እንድትራመድ የሚያስፈልግህ እርሱን በመተማመን መጠበቅ ብቻ ነው፡፡  
እግዚአብሔርን በመተማመን የሚጠባበቁ ግን ኃይላቸውን ያድሳሉ፤ እንደ ንስር በክንፍ ይወጣሉ፤ ይሮጣሉ፥ አይታክቱም፤ ይሄዳሉ፥ አይደክሙም። ትንቢተ ኢሳይያስ 40፡31
እግዚአብሄር እንዲህ ይላል፡፡
እኔ አምላክህ እግዚአብሔር፦ አትፍራ፥ እረዳሃለሁ ብዬ ቀኝህን እይዛለሁና። ትንቢተ ኢሳይያስ 41፡13
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ኢየሱስ #ጌታ #ራእይ #እይታ #መጠበት #መተማመን #እምነት #ያድሳሉ #ይወጣሉ #አይደክሙም #አይታክቱም #እግዚአብሔር #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ቃል #አሸናፊ #አማልክት #የእግዚአብሄርእቅድ #የእግዚአብሄርፈቃድ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ