Popular Posts

Monday, December 24, 2018

የምስጋና ምስክርነት


በሃጢያት ጨለማ በጠፋሁ ጊዜ ፈልጎ ያገኘኝን የክርስቶስን እውቀት ብርሃን በልቤ ያበራን እግዚአብሄርን ማመስገን አለብኝ፡፡ ሳላውቀው ሳልረዳው ስለሃጢያቴ የሞተልኝን እግዚአብሄርን የማመስገን ግዴታ አለብኝ፡፡ ከልጅነቴ ጀምሮ በጤና እና በህይወት የጠበቀኝ እግዚአብሄር ይመስገን፡፡ በመልካም የፍቅር ቤት ውስጥ እንዳድግ ከወላጆቼ ታማኝነት ፣ ትጋትንና መስዋእትነትን ከህይወት ምሳሌነታቸው እንድማር ያደረገኝን እግዚአብሄርን አመሰግነዋለሁ፡፡ ከወጣትነቴ ጀምሮ የመራኝን እግዚአብሄርን ከፍ ከፍ አደርገዋለሁ፡፡
ይህን አልችለውም ብዬ በራሴ ተስፋ በቆረጥኩ ጊዜ ትችለዋለህ ብሎ ያመነብኝ በውስጤ ባስቀመጠው የሚያስችል ፀጋ የተማመነብኝ ከምችለው በላይ እንድፈተን ያልፈቀደ እግዚአብሄር ይመስገን፡፡   
በብዙ ከፍታና ዝቅታ ውስጥ ሳልፍ ከጎኔ የሆነውን ያበረታኝን ሳዝን ያፅናናኝን ስደክም ያበረታኝን እግዚአብሄርን አመሰግነዋለሁ፡፡
አብሬያቸው ይህን ድንቅ ጌታ እንዳመልክ የምወዳቸውንና የሚወዱኝን ወንድሞችና እህቶች የሰጠኝን እግዚአብሄርን አመሰግነዋለሁ፡፡
በእግዚአብሄር መንግስት ውስጥ ያለኝን ድርሻ ያሳየኝን እግዚአብሄርን አመሰግነዋለሁ፡፡ እግዚአብሄር ለምንድነው የጠራኝ ብዬ እንዳላወላውል ልቤን በፈቃዱ ያፀናውን እግዚአብሄርን አመሰግነዋለሁ፡፡ እግዚአብሄር ለምን እንደጠራኝ ጥርት አድርጎ ያሳየኝን እግዚአብሄርን አመሰግነዋለሁ፡፡
ሰዎች የከበረውን ከተዋረደው መለየት አቅቷቸው በህይወት ሲንከታተቱ የከበረውን ከተዋረደው እንድለይ ያደረገኝን እግዚአብሄርን አመሰግነዋለሁ፡፡
በእያንዳንዱ ነገሬ እየመራኝ ያለውን እግዚአብሄርን አመሰግነዋለሁ፡፡ መልካሙ እረኛዬ እግዚአብሄር እኔን በትጋት እንደሚመራኝ ከማወቄ የተነሳ የሌለኝ ነገር ሁሉ የሌለኝ ስለማያስፈልገኝ እንደሆነ እስከምረዳ ድረስ በትጋት የሚመራኝን እግዚአብሄርን አመሰግነዋለሁ፡፡ ልቤ ሙሉ ነው የጎደለኝ ነገር እንዳለ አይሰማኝም፡፡
እንደገና መኖር ቢኖርብኝ አሁን የምኖረውን ኑሮ ደግሜ መኖር እስከምፈልግ ድረስ በህይወቴ ደስተኛ ነኝ፡፡ እኔ ከሰው ሁሉ በላይ ደስተኛ ነኝ ባልልም ነገር ግን ከእኔ በላይ ደስተኛ ሰው ያለ አይመስለኝም፡፡
በክርስቶስ ያገኘሁትን ሰላም አልፎ ሊገባ የሚችል ምንም ሁኔታ በህይወቴ የለም፡፡
እግዚአብሄር በሰዎች ፊት ሞገስ ሰጥቶኛል፡፡ ሰዎች ይወዱኛል ያከብሩኛል ስለዚህ ደግሞ በሰዎች ፊት ተቀባይነትን የሰጠኝን እግዚአብሄርን አመሰግናለሁ፡፡
ስኬት የእግዚአብሄርን አላማ መፈፀም ነው፡፡ በህይወቴ የእግዚአብሄር አላማ በህይወቴ በመፈፀም የተሳካልኝ እንደሆንኩ አውቃለሁ፡፡
ከእኔ በላይ ተከናወነለት ብዬ የምቀናበት ሰው የለም፡፡ ሙሉ ለሙሉ እንደተከናወነለት ሰው ልቤ ሙሉ ነው፡፡ እግዚአብሄር በምሰራው ስራ ሁሉ ድል በድል የምሄድ ሰው አድርጎኛል፡፡  
እኔ ራሴን መንከባከብ ከምችለው በላይ እርሱ ሲንከባከበኝ አይቻለሁ፡፡ ጌታዬን ከተከተልኩ ጀምሮ እግዚአብሄር የሚያስገፈልገኝን ሁሉ ሲያሟላ ስላየሁት እግዚአብሄር ምን ያደርግልኛል የሚለው ጭንቀት ከህይወቴ ስለሞተ እግዚአብሄርን አመሰግነዋለሁ፡፡ አሁን ሁል ጊዜ የሚያሳስበኝ ምን ላድርግለት ፣ እንዴት ልኑርለት ፣ ምኔን ልስጠው ፣ እንዴት ላገልግለው የሚለው ሃሳብ ብቻ ነው፡፡
ጌታን እንዳወቅኩ ህልሜ እግዚአብሄር በሃይል እንዲጠቀምብኝ ነበር፡፡ አሁን ህልሜን እየኖርኩት ነው፡፡ በአገልግሎቴ ሰዎች ሲባረኩ ሲጠቀሙ ሳይ እግዚአብሄርን ከማመስገን ውጭ ሌላ ምንም ቃላት የለኝም፡፡ እግዚአብሄር በቃልህ ተጠቅሞ  ካለሁበት ነገር አወጣኝ የሚል ምስክርነት በመስማት ህልሜን እየኖርኩት ነው፡፡
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa  
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ገና #በዓል #ፍቅር #ተስፋ #ደስታ #መስዋእት #ምስክርነት #መዳን #ምስጋና #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #ብርሃን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ህይወት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ  #ኢየሱስ #ጌታ

Friday, December 21, 2018

ለእነዚህ 11 ነገሮች ጊዜ የለንም


1.      ለጭንቀት
የእግዚአብሄር ፅድቅና መንግስቱን ለመፈለግ በቀን 24 ሰአት 7 በሳምንት ሰባት ቀን አለን፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሄርን ፅድቅና መንግስቱን ከመፈለግ የሚተርፍ እና ለጭንቀት የሚሆን አንድ ደቂቃም የለንም፡፡ 
እርሱ ስለእናንት ያስባልና የሚያስጨንቃችሁን በእርሱ ላይ ጣሉት የተባለለት ሁሉ በእጁ ሁሉ በደጁ የሆነ አባት እያለን በጭንቀት የምናባክንው ምንም ጉልበት የለም፡፡
እንግዲህ፦ ምን እንበላለን? ምንስ እንጠጣለን? ምንስ እንለብሳለን? ብላችሁ አትጨነቁ፤ ይህንስ ሁሉ አሕዛብ ይፈልጋሉ፤ ይህ ሁሉ እንዲያስፈልጋችሁ የሰማዩ አባታችሁ ያውቃልና። የማቴዎስ ወንጌል 6፡31-32
ጭንቀት ፍሬ እንዳናፈራ የሚያደርግ የመንፈሳዊ ፍሬ ጠላት ስለሆነ በጭንቀት ለማባከን የምንፈልገው ምንም ፍሬ የለንም፡፡
በእሾህ መካከል የተዘራውም ይህ ቃሉን የሚሰማ ነው፥ የዚህም ዓለም አሳብና የባለጠግነት መታለል ቃሉን ያንቃል፥ የማያፈራም ይሆናል። የማቴዎስ ወንጌል 13፡22
2.     ለውድድር
እግዚአብሄር የሰጠን በቂ የህይወት ሃላፊነት አለን፡፡ እግዚአብሄር በምድር ላይ ሰርተን እንድናከብረው የሰጠን የህይወት አላማ አለን፡፡ እግዚአብሄር የጠራን ለተለየ አላማ ነው፡፡ ከእኛ የተለየ የህይወት አላማ ካለው ሰው ጋር አንፎካከርም፡፡ እኛ የምንወዳደረው እግዚአብሄር ከሰጠን ስራ ጋር ነው፡፡ እግዚአብሄር የሰጠኝን ስራ ምን ያህሉን ሰርቼያለሁ ብለን በመጠየቅ     የተሰጠንን ሃላፊነት ከራሳችን የስራ አፈፃፀም ጋር እናስተያያለን፡፡  
ራሳቸውን ከሚያመሰግኑ ከአንዳንዶች ጋር ራሳችንን ልንቆጥር ወይም ራሳችንን ልናስተያይ አንደፍርምና፤ ነገር ግን እነርሱ ራሳቸውን ከራሳቸው ጋር ሲያመዛዝኑ፥ ራሳቸውንም ከራሳቸው ጋር ሲያስተያዩ፥ አያስተውሉም። 2ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 10፡12
3.     ለስንፍና
ነገ ይመጣሉ ብለን ስለምናስባቸው ስለ ትልልቅ ነገሮች አንመካም፡፡ ያለን አሁን ነው፡፡ አሁንን በሚገባ እንጠቀምበታለን፡፡ አሁን እንተጋለን፡፡ ለነገ ብለን የምንቆጥበው ጉልበት የለንም፡፡ የጉልበት የቁጠባ ባንክ የለም፡፡ ዛሬ ካልተጋንበት ጉልበታችን ይባክናል እንጂ አይጠራቀምም፡፡ ታማኝነታችንን ለማሳየት ታላላቅ ነገሮችን አንጠብቅም፡፡ አሁን ባለን ነገር ታማኝነታችንን እናሳያለን፡፡ በመቃብር የስራና የትጋት እድል የለም፡፡ 
አንተ በምትሄድበት በሲኦል ሥራና አሳብ እውቀትና ጥበብ አይገኙምና እጅህ ለማድረግ የምታገኘውን ሁሉ እንደ ኃይልህ አድርግ። መጽሐፈ መክብብ 9፡10
4.     ለቅንጦት
እግዚአብሄር የሚያስፈልገንን ሁሉ እንደሚያሟላ ቃል ገብቷል፡፡ ነገር ግን ቅንጦታችንን እንደሚያሟላ ቃል የገባበት አንድም ቦታ አይገኝም፡፡ ለቅንጦት የምንጠቀመው ገንዘብ ሁሉ ከመሰረታዊ ፍላታቸን ላይ የተቀነሰ ነው፡፡ ለቅንጦት የምንጠቀመው የመሰረታዊ ፍላጎታችን በጀት ነው፡፡ በቅንጦት ላይ ያዋልነው ሁሉ መሰረታዊ ፍላጎት ይቀንሳል፡፡ ለመሰረታዊ ፍላጎት ማዋል ያለብንን ነው በቅንጦት ላይ የምናቃጥለው፡፡ ስለዚህ ከመሰረታዊ ፍላጎት ውጭ በቅንጦት ላይ የምናጠፋው አንድም ገንዘብ የለንም፡፡
ትለምናላችሁ፥ በምቾቶቻችሁም ትከፍሉ ዘንድ በክፉ ትለምናላችሁና አትቀበሉም። የያዕቆብ መልእክት 4፡3
አንዳችንም ልንወስድ አይቻለንም፤ ምግብና ልብስ ከኖረን ግን፥ እርሱ ይበቃናል። ዳሩ ግን ባለ ጠጎች ሊሆኑ የሚፈልጉ በጥፋትና በመፍረስ ሰዎችን በሚያሰጥምና በሚያሰንፍ በሚጎዳም በብዙ ምኞትና በፈተና በወጥመድም ይወድቃሉ። 1ኛ ወደ ጢሞቴዎስ 6፡8-9
5.     ለጥላቻ
ስንሰራ የተነደፍነው ለፍቅር ነው፡፡ ስንወድ ያምርብናል፡፡ ስንወድ እንሳካለን፡፡ ስንወድ እንከናወናለን፡፡ ለጥላቻ ግን አልተሰራንም፡፡ ለምሬትና ይቅር ላለማለት ግን አልተፈጠንም፡፡ እግዚአብሄር ፍቅር ነው፡፡ ጥላቻ ከእግዚአብሄር አይደለም፡፡
ጥላቻ ያለበት ሰው ሰይጣንን እንጂ እግዚአብሄርን ማገልገል አይችልም፡፡ ጥላቻ ለሰይጣን እንደፈለገ ዘርቶ ብዙ ፍሬ የሚያጭድበት ለም መሬቱ ነው፡፡ ስለዚህ ለፍቅር እንጂ ለጥላቻ የምናውለው ምንም ጊዜ የለንም፡፡
መራርነትና ንዴት ቁጣም ጩኸትም መሳደብም ሁሉ ከክፋት ሁሉ ጋር ከእናንተ ዘንድ ይወገድ። እርስ በርሳችሁም ቸሮችና ርኅሩኆች ሁኑ፥ እግዚአብሔርም ደግሞ በክርስቶስ ይቅር እንዳላችሁ ይቅር ተባባሉ። ወደ ኤፌሶን ሰዎች 4፡31-32
6.     ሰውን ለማስደሰት
የተጠራነው እግዚአብሄርን ለማስደሰት ነው፡፡ ሰው የምናስደስተው እግዚአብሄርን በማሰደሰት ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄርን ባለመታዘዝ ሰውን አናስደስትም፡፡ እግዚአብሄር የጠራንን ነገር ማድረግ ትተን ሰውን ለማስደሰት ጊዜውም ጉልበቱም የለንም፡፡
ሰውን ወይስ እግዚአብሔርን አሁን እሺ አሰኛለሁን? ወይም ሰውን ደስ ላሰኝ እፈልጋለሁን? አሁን ሰውን ደስ ባሰኝ የክርስቶስ ባሪያ ባልሆንሁም። ወደ ገላትያ ሰዎች 1፡10
ጴጥሮስና ዮሐንስ ግን መልሰው፦ እግዚአብሔርን ከመስማት ይልቅ እናንተን እንሰማ ዘንድ በእግዚአብሔር ፊት የሚገባ እንደ ሆነ ቍረጡ፤ እኛስ ያየነውንና የሰማነውን ከመናገር ዝም ማለት አንችልም አሉአቸው። የሐዋርያት ሥራ 4፡19-20
7.     ለምኞት
የእግዚአብሄርን አላማ ለመፈፀም ወደምድር መጥተናል፡፡ የራሳችንን ፍላጎት ለመፈፀም የሚያስችል ጊዜውም ጉልበቱም የለንም፡፡ ለአላማችን የሚበቃ የእግዚአብሄር ፀጋ በእኛ ላይ አለ፡፡ ከዚያ የተረፈ እንደፈለግን ለመኖር እና የራሳችንነ ፍላጎት ለመፈፀም የሚበቃ ትርፍ አቅርቦት የለንም፡፡ ለወንንጌል የከበረ አላማ ተጠርተናል፡፡ ይህንን የከበረ አላማ ትተል ወንጌሉን የልጅነት ምኞታችንን ለማሳካት ህሊናችን አይፈቅድልንም፡፡
እንዲህ ያሉት ለገዛ ሆዳቸው እንጂ ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ አይገዙምና፥ በመልካምና በሚያቆላምጥ ንግግርም ተንኮል የሌለባቸውን ሰዎች ልብ ያታልላሉ። ወደ ሮሜ ሰዎች 16፡18
እንደ እርሱ ያለ፥ ስለ ኑሮአችሁ በቅንነት የሚጨነቅ፥ ማንም የለኝምና፤ ሁሉ የራሳቸውን ይፈልጋሉና፥ የክርስቶስ ኢየሱስን አይደለም። ወደ ፊልጵስዩስ ሰዎች 2፡20-21
እንደ ኢየሱስ ክርስቶስ በጎ ወታደር ሆነህ፥ አብረኸኝ መከራ ተቀበል። የሚዘምተው ሁሉ ለጦር ያስከተተውን ደስ ያሰኝ ዘንድ ትዳር በሚገኝበት ንግድ ራሱን አያጠላልፍም። 2 ወደ ጢሞቴዎስ 2፡4
8.     ለግምት እና ለሙከራ
እግዚአብሄር በትጋት ይመራናል፡፡ እግዚአብሄር የሚመራንን ምሪት እንከተላለን እንጂ እግዚአብሄር ይህን ይፈልግ ይሆን እያልን በግምት ለመመራት የሚበቃ አቅምም ጉልበትም የለንም፡፡ ህይወታችንን በሙከራ ለማሳለፍ የሚተርፍ ጊዜውም አቅሙም የለንም፡፡ እግዚአብሄር ካላለን ስፍራችንን አንለቅም፡፡ እግዚአብሄር ሳይለን በራሳችን አነሳሽነት ለእግዚአብሄር ለማድረግ የምናባክነው ትርፍ ጉልበትና ጊዜ የለንም፡፡ 
በእግዚአብሔር መንፈስ የሚመሩ ሁሉ እነዚህ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸውና። ወደ ሮሜ ሰዎች 8፡14
9.     ለሰው አስተያየት
እግዚአብሄር ብዙ ጊዜ በሰዎች ሲመክረንና ሲመልሰን አይተናል፡፡ በህይወታችን በሰዎች የሚጠቀመውን የእግዚአብሄርን ምሪት እንከተላለን፡፡ ነገር ግን የሰውን አስተያየት ሁሉ በማድረግ በሰዎች አስተያየት ህይወታችንን አንገነባም፡፡ በእግዚአብሄር ምሪት እንጂ በሰዎች አስተያየት ህይወታችንን ለመገንባት የሚበቃ ጊዜ የለንም፡፡ የሰዎች ፍላጎት ስለሆነ ብቻ እግዚአብሄርን ያለንን ለማድረግ የሚያስችል አንድም ትርፍ ቀን በህይወታችን የለንም፡፡
ነገር ግን በእናንተ ዘንድ ወይም በሌላ ሰው ዘንድ ብፈረድ ለእኔ ምንም አይደለም፤ እኔም በራሴ እንኳ አልፈርድም፤ 1 ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 4፡3
10.    ለፍርሃት
የፍርሃት አላማ እኛን እግዚአብሄር ከሰጠን የህይወት ሃላፊነት ማስቆም ነው፡፡ ፍርሃትን ለማስተናገድ ጊዜ የለንም፡፡ ፍርሃት ስሜት አይመጣመ ማለት አይደለም፡፡ እግዚአብሄርን ከመታዘዛችን በፊት ይፍርሃት ስሜቱ መቆም የለበትም፡፡ የፍርሃት ስሜቱ እያለም ቢሆን የእግዚአብሄር ፈቃድ እናደርገዋልን፡፡
አንተ ታናሽ መንጋ፥ መንግሥትን ሊሰጣችሁ የአባታችሁ በጎ ፈቃድ ነውና አትፍሩ። የሉቃስ ወንጌል 12፡32
11.     ለማጉረምረም
እግዚአብሄርን በሁሉ እናመሰግናለን፡፡ ነገር ግን በማጉረምረም እግዚአብሄርን ለማማት ጊዜ የለንም፡፡ ባይገባንም እንኳን ሁለ በሚያውቅና ለእኛ በሚጠነቀቅ በእግዚአብሄር ላይ እንደገፋለን እንጂ በማጉረምረም አባታችንን እግዚአብሄርን ለማስቆጣት ፍላጎቱም ጊዜውም የለንም፡፡
በመጥፎና በጠማማ ትውልድ መካከል ያለ ነቀፋ የዋሆችም ነውርም የሌለባቸው የእግዚአብሔር ልጆች እንድትሆኑ ሳታንጐራጉሩ ክፉም ሳታስቡ ሁሉን አድርጉ፤ ወደ ፊልጵስዩስ ሰዎች 2፡14-15
ሳታቋርጡ ጸልዩ፤ በሁሉ አመስግኑ፤ ይህ የእግዚአብሔር ፈቃድ በክርስቶስ ኢየሱስ ወደ እናንተ ነውና። 1ኛ ወደ ተሰሎንቄ ሰዎች 5፡17-18
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ክብር #አገልግሎት #ግምት #ምኞት #አላማ #ምሪት #ማጉረምረም #አስተያየት #ጥላቻ #ቅንጦት #ስንፍና #ጭንቀት #መዋረድ #መርካት #ፀጋ #እውቀት #ኢየሱስንተመልክተን #ፍርሃት #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ብፅእና #እምነት #ታላቅነት #ማገልገል #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

Thursday, December 20, 2018

በሚዛን ተመዘንህ፥ ቀልለህም ተገኘህ ፣ እግዚአብሔር መንግሥትህን ቈጠረው ፈጸመውም


የተጻፈውም ጽሕፈት፦ ማኔ ቴቄል ፋሬስ ይላል። የነገሩም ፍቺ ይህ ነው፤ ማኔ ማለት፥ እግዚአብሔር መንግሥትህን ቈጠረው ፈጸመውም ማለት ነው። ቴቄል ማለት፥ በሚዛን ተመዘንህ፥ ቀልለህም ተገኘህ ማለት ነው። ፋሬስ ማለት፥ መንግሥትህ ተከፈለ፥ ለሜዶንና ለፋርስ ሰዎችም ተሰጠ ማለት ነው። ትንቢተ ዳንኤል 5፡25-28
ይህ ፅሁፍ የተፃበት ሰው ንጉስ የነበረና ንግስናውን ካለአግባብ በመጠቀም ህዝቡን ሲያጎሳቁል ስለነበረ ነው፡፡ ነው ይህ ጽሁፍ የተፃፈው እግዚአብሄርን ስላልፈራና ስለተዳፈረ ንጉስ ነው፡፡
እግዚአብሄርን አለመፍራትና ማን አለብኝነት ሰይጣንን መከተል ነው፡፡ በየትኛውም ቦታ በቤተሰብ በቤተክርስትያን በአገር ትእቢት ሰውን ያዋርዳል፡፡ ትእቢት ውድቀትን ይቀድማል፡፡ ሰው የሚሰነብተው በትህትና እንጂ ትእቢት ከመጣ ውድቀት ይመጣል፡፡
ትዕቢት ጥፋትን፥ ኵሩ መንፈስም ውድቀትን ይቀድማል። መጽሐፈ ምሳሌ 16፡18
እግዚአብሄር ንጉስ ነው፡፡ እግዚአብሄር በቤተክርስትያን ብቻ ሳይሆን በአገር ውስጥ በፍጥረቶቹ ላይ ስለሚሆነው ነገር ሁሉ ግድ ይለዋል፡፡
ምድር የግለሰቦች አይደለችም፡፡ ምድር የእግዚአብሄር ነች፡፡ በምድር ላይ እግዚአብሄር ለሰዎች ስልጣንን በአደራ ይሰጣል፡፡ ከእግዚአብሔር ካልተገኘ በቀር ሥልጣን የለም፡፡ 
ከእግዚአብሔር ካልተገኘ በቀር ሥልጣን የለምና፤ ያሉትም ባለ ሥልጣኖች በእግዚአብሔር የተሾሙ ናቸው። ወደ ሮሜ ሰዎች 13፡1
እግዚአብሄር ሰዎችን ስለሚወድ ሰዎችን እንዲያገለግሉና በመልካም እንዲያስተዳድሯቸው እግዚአብሄር ለሰው ልጆች ስልጣንን ይሰጣል፡፡
አትታበዩ፥ በኩራትም አትናገሩ፤ እግዚአብሔር አዋቂ ነውና፥ እግዚአብሔርም ሥራውን የሚመዝን ነውና፥ ከአፋችሁ የኵራት ነገር አይውጣ። የኃያላንን ቀስት ሰብሮአል፥ ደካሞችንም በኃይል ታጥቀዋል። ጠግበው የነበሩ እንጀራ አጡ፤ ተርበው የነበሩ ከራብ ዐርፈዋል፤ መካኒቱ ሰባት ወልዳለችና፥ ብዙም የወለደችው ደክማለች። እግዚአብሔር ይገድላል ያድናልም፤ ወደ ሲኦል ያወርዳል፥ ያወጣል። እግዚአብሔር ድሀ ያደርጋል፥ ባለጠጋም ያደርጋል፤ ያዋርዳል፥ ደግሞም ከፍ ከፍ ያደርጋል። ከሕዝቡ መኳንንት ጋር ያስቀምጣቸው ዘንድ፥ የክብርንም ዙፋን ያወርሳቸው ዘንድ፥ ችግረኛውን ከመሬት ያስነሣል፥ ምስኪኑንም ከጉድፍ ያስነሣል፤ የምድር መሠረቶች የእግዚአብሔር ናቸውና፥ በእነርሱ ላይም ዓለምን አደረገ። መጽሐፈ ሳሙኤል ቀዳማዊ 2፡3-8
መሪን የሚሾመው እግዚአብሄር ነው፡፡ እግዚአብሄር ህቡን ወደ ብልፅግና እንዲመሩና መሪዎችን ይሾማል፡፡
ምድርና ሞላዋ የእግዚአብሄር ነች፡፡ ስልጣን የእግዚአብሄር ነው፡፡ እግዚአብሄር ስልጣንን ለሰዎች በአደራ ይሰጣል፡፡ ስልጣን በሰው ቤት ላይ እንደተሾመ ሰው በአደራ የሚሰጥ ሃላፊነት ነው፡ 
ስልጣን ተጠቃሚነት አይደለም፡፡ ስልጣን ሃላፊነት ነው፡፡ ስልጣንን ከእግዚአብሄር በአደራ እንደተሰጠ ጊዜያዊ ሃላፊነት የማያይ ሰው ስልጣኑን አላግባብ ይጠቀማል፡፡ ስልጣኑን የሰጠው አምላክ እንደሚጠይቀው የማያውቅ ሰው በስልጣኑ ይባልጋል፡፡ ስልጣኑን የሰጠው አምላክ ስራውን እንደሚከታተለውና እንደሚመዝነው የማውቅ ሰው እንዲያገለግለው የተሰጠውን ህዝብ ያጎሳቁላል፡፡ ስልጣኑን በአደራ ለሰጠው አምላክ ሃላፊነት እንዳለበትና እንደሚጠየቅ የማያውቅ ሰው እንደ ባለአደራ ሳይሆን እንደግል ቤቱ ያስተዳደራል፡፡
እግዚአብሄር መሪን ይመዝናል፡፡ እግዚአብሄር ትእቢተኛን መሪን ይሽራል፡፡ እግዚአብሄር ስልጣንን ለወደደው ይሰጣል፡፡
ልዑሉ በሰዎች መንግሥት ላይ እንዲሠለጥን፥ ለወደደውም እንዲሰጠው፥ ከሰውም የተዋረደውን እንዲሾምበት ሕያዋን ያውቁ ዘንድ ይህ ነገር የጠባቂዎች ትእዛዝ፥ ይህም ፍርድ የቅዱሳን ቃል ነው። ትንቢተ ዳንኤል 4፡17
እግዚአብሄር በሌላው ላይ የሰጣቸውን ድል በሃያልነታቸው እንዳገኙት የሚያስቡ ሰዎች ንስሃ ሊገቡ ይገባል፡፡ እግዚአብሄር የሰጣቸውን ህዝብን የማስተዳደር ስልጣን በራሳቸው ሃያልነትና ቅልጥፍና እንዳገኙት የሚያስቡ ሰዎች ሊያዝኑና ሊፀፀቱ ይገባል፡፡ የጦርነት ድል የሚገኘው በሃያልነት ሳይሆን በእግዚአብሄር ፈቃድ ብቻ ነው፡፡
እኔም ተመለስሁ፥ ከፀሐይ በታችም ሩጫ ለፈጣኖች፥ ሰልፍም ለኃያላን፥ እንጀራም ለጠቢባን፥ ባለጠግነትም ለአስተዋዮች፥ ሞገስም ለአዋቂዎች እንዳልሆነ አየሁ፤ ጊዜና እድል ግን ሁሉን ይገናኛቸዋል። መጽሐፈ መክብብ 9፡11
እግዚአብሄር የሰጣቸውን ህዝብን የማስተዳደር ስልጣን በራሳቸው ሃያልነትና ቅልጥፍና እንዳገኙት ቆጥረው እግዚአብሄርን ባለመፍራት የኖሩ ሰዎች ሊያዝኑበትና ሊያፍሩበት ይገባል፡፡ እግዚአብሄር የሰጣቸውን ህዝብን የመምራት እድል በሚገባ ያልተጠቀሙ ሰዎች ሊያዝኑና ንስሃ ሊገቡ ይገባል፡፡ እግዚአብሄር በእጃቸው የሰጣቸውን ህዝብ ያጎሳቆሉ ሁሉ ንስሃ ሊገቡ ይገባል፡፡ እግዚአብሄር በእጃቸው የሰጣቸውን ህዝብ የዘረፉ ሁሉ በሌብነታቸው ሊያፍሩ ይገባል፡፡ እግዚአብሄር በአደራ የሰጣቸውን ህዝብ ሃብትና ንብረት በስግብግብነት ሁሉ ወደ ግል ይዞታነት ያሸጋገሩ ሁሉ ሊያፍሩ ይገባል፡፡ እግዚአብሄር የሰጣቸውን ሃላፊነት ሳይወጡ የራሳቸውን የግል ጥቅም ሲያሳድዱ የኖሩ ሁሉ ሊፀፀቱ ይገባል፡፡ እግዚአብሄር እንዲመሩትት እና ወደብልፅግና እንዲያደርሱት የሰጣቸውን ህዝብ አስፈራርተው የነጠቁትና የበዘበዙት ሁሉ ሊያፍሩበት ይገባል፡፡ እግዚአብሄር በአደራ የሰጣቸውን ህዝብ በማን አለብኝነት የገረፉ ፣ ያሰቃዩና የገደሉ ሁሉ በትእቢት መቀጠል ሳይሆን ከእግዚአብሄር ምህረትን መጠየቅ አለባቸው፡፡  
አሁን እግዚአብሄር በሰጣቸው ጊዜ ሊመለሱና እግዚአብሄር በሰጣቸው ስልጣን ህዝቡን በቅንነት ለማገልገል ሊወስኑ ይገባል፡፡
አሁንም በትእቢት የሚመላለሱ ሰዎች ከመፀፀት ይልቅ ወቀሳውንና ጥፋተኝነቱን ወደሌላ ሰው የሚያስተላለፉ ሰዎች እግዚአብሄር ይፈርድባቸዋል፡፡ የእግዚአብሄርን ስራ የማይቀበሉ አገሪቱ ላይ የመጣውን ለውጥ የሰው የእጅ ስራ የሚያደርጉ ሰዎች እግዚአብሄርን ደስ አያሰኙትም፡፡ በአገሪቱ ላይ የመጣው ለውጥ የእግዚአብሄር እጅ እንደሌለበት የሚያስቡ ሰዎች እንደገና ሊያስቡበት ይገባል፡፡
እግዚአብሄር እድልን ይሰጣል፡፡ እግዚአብሄር መዝኖ ቀለህ ተገኘህ ብሎ የጣለውን ሰው ሊያነሳው የሚችል ማንም ሰው የለም፡፡ እግዚአብሄር መዝኖ የጣለውን ሰው የተባበሩት መንግስታት አያነሳውም፡፡ በእግዚአብሄር ፊት ተመዝኖ የተጣለን ሰው ሃያሉ የአሜሪካ መንግስት አያስጥለውም፡፡
ባለስልጣኖች ስልጣን የእግዚአብሄር መሆኑን የመረዳት ሃላፊነት አለባቸው፡፡ ስልጣን የእግዚአብሄር እንደሆነ እግዚአብሄርን በመፍራት ህዝብን ለማገልገል ለህዝብ ጥቅም የሚሰጥ እንደሆነ የማይረዱ ባለስልጣት እግዚአብሄር ይፈርድባቸዋል፡፡ የእግዚአብሄርን ስርአት የሚቃወመው እግዚአብሄርን ይቃወማል፡፡ እግዚአብሄር በፈጠረው ምድር ላይ እግዚአብሄርን ተቃውሞ የሚሳካለት ሰው የለም፡፡  
ከእግዚአብሔር ጋር የሚጣሉ ይደቅቃሉ፤ በሰማይም ያንጐደጕድባቸዋል፤ እግዚአብሔር እስከ ምድር ዳርቻ ይፈርዳል፤ ለንጉሡም ኃይል ይሰጣል፤ የመሲሑንም ቀንድ ከፍ ከፍ ያደርጋል። መጽሐፈ ሳሙኤል ቀዳማዊ 2፡10
እግዚአብሄር የማንንም ውድቀት አይፈልግም፡፡ እግዚአብሄር ሃያል ነው ማንንም አይንቅም፡፡ ራሱን የሚያዋርደውን ማንኛውንም ሰው እግዚአብሄር ይቅር ይላል ያነሳዋል፡፡ ራሱን የሚያዋርደውን ሰው ልብ እግዚአብሄር አይንቅም፡፡ ራሱን የሚያዋርደውን ሰው እግዚአብሄር ህዝቡን የሚያገለግልበትን ሌላ እድል ይሰጠዋል፡፡
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ  Abiy Wakuma Dinsa
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes

#ኢየሱስ #ጌታ #ባለስልጣን #ፀሎት #ወታደር #ኢየሱስ #ጌታ #መበለት #ድሃአደግ #ድሃ #ጭቆና #ፍትህ #ፍርድ #ቀራጭ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #ወንጌል #መናገር #ፅናት #ትግስት #መሪ

Tuesday, December 18, 2018

የአገልግሎት ስድስቱ ቅድመ ሁኔታዎች

እግዚአብሄርን እንደ ማገልገል የከበረ ነገር የለም፡፡ እግዚአብሄርን ማገልገል ደግሞ በጣት ለሚቆጠሩ ጥቂት ሰዎች የተሰጠ እድል ሳይሆን ለሁሉም ሰው የተሰጠ እድል ነው፡፡ እግዚአብሄር ንጉስ ነው፡፡ እግዚአብሄርን እርሱ በሚፈልገው እንጂ እኛ በፈለግነው ሁኔታ አናገለግለውም፡፡ እግዚአብሄርን በማገልገል ፍሬያማ ለመሆን ከእኛ የሚጠይቀው ነገር አለ፡፡ እግዚአብሄርን ማገልገል በእግዚአብሄር ቃል ስርአት እንደሚገባ መሄድን ይጠይቃል፡፡ ስለዚህ ነው ብዙ ሰዎች እግዚአብሄርን ያገለግላሉ ነገር ግን ሁሉም እግዚአብሄርን በማገልግል ፍሬያማ አይሆኑም፡፡ እግዚአብሄርን በማገልግል ውጤያማ የሚያደርጉትን ነገሮች ከእግዚአብሄር ቃል እንመልከት፡፡  
1.      ቅንነት
እግዚአብሄርን ለማገልገል ቅንነት ወሳኝ ነገር ነው፡፡ ቅንንት ሳይኖራቸው እግዚአብሄርን ለማገልገል የሚሞክሩ ሰዎች እግዚአብሄርንም ራሳቸውን ለማገልገል ሲመክሩ ይወድቃሉ፡፡ እግዚአብሄርን ለማገለገል ለእግዚአብሄር ቃል የዋህ መሆን ይጠይቃ፡፡ እግዚአብሄርን ለማገልገል ለእግዚአብሄር ሃሳብ ሞኝ መሆን ይጠይቃል፡
እግዚአበሄርን ካላመንነው እግዚአብሀርን ማገልግል የማይታሰብ ነገር ነው፡፡ እንደው በከንቱ እንወጣለን እንወርዳለን እንጂ እግዚአብሄን ማገልግል የምንችለው እግዚአብሄርን ባመንንነት መጠን ብቻ ነው ፡፡
እግዚአብሄር አገልግሉኝ የሚለው ለእኛው ጥቅም እንደሆነ በቅንነት መረዳት ይጠይቃል፡፡ እግዚአብሄርን መልካምነት በመጠራጠርና ለእግዚአብሄር ራሳችንን ሙሉ በሙሉ ባለመስጠት የምናገለግለው አገልግሎት ፍሬያማ አይሆንም፡፡
አንድ መክሊትም የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ፦ ጌታ ሆይ፥ ካልዘራህባት የምታጭድ ካልበተንህባትም የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መሆንህን አውቃለሁ፤ ፈራሁም ሄጄም መክሊትህን በምድር ቀበርሁት፤ እነሆ፥ መክሊትህ አለህ አለ። የማቴዎስ ወንጌል 25፡24-25
2.     ትህትና
እግዚአብሄርን ማገልገል በእግዚአብሄር ፊት ትሁት መሆን ይጠይቃል፡፡ የእግዚአብሄር መንገድና የእኛ መንገድ ሊለያየ ይችላል፡፡ እግዚአብሄርን የምናገለግለው በራሳችን መንገድ አይደለም፡፡ እግዚአብሄርን የምናገለግለው በእርሱ መንገድ ነው፡፡ ከእግዚአብሄር ጋር ለመኖር እና እርሱ በሚመርጠው መንግድ እርሱን ለማገልግል ትህትና ይጠይቃል፡፡
እርሱም ብቻ አይደለም ሰውን ለማገልገል ትህትና ይጠይቃል፡፡ የምናገለግለውን ሰው እኛ አንመርጥም፡፡ እግዚአብሄር የሰጠንን ሰው ነው የምናገለግለው፡፡ የምናገለግላቸው ሰዎች ከእኛ የተለዩ ሰዎች ናቸው፡፡ የምናገለግላቸው ሰዎች እንደእኛ መረዳት የሌላቸው ሰዎች ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ሰውን በማገልገል እግዚአብሄርን ለማገልገል ዝቅ ማለትና ትህትና ይጠይቃል፡፡ እግዚአብሄርን ለማገልገል ሌላውን ሰው ከእኛ እንደሚሻል መቁጠርን ይጠይቃል፡፡ ሁሉም ሰው በትህትና አድጎ ጨርሶ ማገልገል አይጀምርም፡፡ እያገለገልንም በትህትና እናድጋለን፡፡ ነገር ግን ትሁት በሆንንበት መጠን ብቻ ነው ጌታን ማገልገል የምንችለው፡፡ 
ለወገኔ ይጠቅማል በማለት ወይም በከንቱ ውዳሴ ምክንያት አንድ እንኳ አታድርጉ፥ ነገር ግን እያንዳንዱ ባልንጀራው ከራሱ ይልቅ እንዲሻል በትሕትና ይቍጠር፤ በክርስቶስ ኢየሱስ የነበረ ይህ አሳብ በእናንተ ዘንድ ደግሞ ይሁን።
ወደ ፊልጵስዩስ ሰዎች 2፡3፣5
3.     ተገኝነት   
ተገኝነት ወይም ራስን መስጠት ለአገልግሎት ወሳኝ ነገር ነው፡፡ ሰው ምንም ያህል ስጦታ ቢኖረው ራሱን ካልሰጥ ምንም ስጦታ እንደሌለው ይቆጠራል፡፡ ሰው ስጦታውን አውጥቶ ለእግዚአብሄር ህዝብ ጥቅም ማዋል የሚችለው ራሱን ለሚያገለግልው ህዝብ ሲሰጥ ብቻ ነው፡፡ ሰው ራሱን ላለመስጠትም ሰስቶ እግዚአብሄርን ለማገልገልም ፈልጎ ሁለት ወዶ አይሆንም፡፡ ሰው ራሱን ሲሰጥ ብቻ ነው እግዚአብሄር በውስጡ ያስቀመጠውን ፀጋ አውጥቶ ህዝቡን የሚጠቅመው እንዲሁም ስጦታውን የሚያሳድገው፡፡ ሰው በውስጡ ያለውን ፀጋ የሚያሳድገውና በአገልግሎቱ የሚያድገው ራሱን ከሰጠ ብቻ ነው፡፡ ብዙ ፀጋ ኖሮት ራሱን ካልሰጠው ሰው ይልቅ ያነሰ ፀጋ ኖሮት ራሱን የሰጠው ሰው እግዚአብሄር በሃይል ይጨቀምበታል በአግልግሎቱ  ያሳድገውማል፡፡ ራሱን የያልሰጠን ሰው እግዚአብሄር ሊጠቀምበትና በአገልግሎትም ሊያሳድገው አይችልም፡፡
የጌታንም ድምፅ፦ ማንን እልካለሁ? ማንስ ይሄድልናል? ሲል ሰማሁ። እኔም፦ እነሆኝ፥ እኔን ላከኝ አልሁ። ትንቢተ ኢሳይያስ 6፡8
በሠራተኞች እጅ ለሚሠራው ሥራ ሁሉ ለወርቁ ዕቃ ወርቁን፥ ለብሩም ዕቃ ብሩን ሰጥቻለሁ። ዛሬ በፈቃዱ ራሱን ለእግዚአብሔር የሚቀድስ ማነው? መጽሐፈ ዜና መዋዕል ቀዳማዊ 29፡5
4.     ታማኝነት
ሰው አገልጋይ እንዲሆን ታማኝነት ይጠበቅበታል፡፡ አግዚአብሄር በሰጠው በትንሽ ነገር የማይታመን ሰው እግዚአብሄርን አገልግላለሁ ቢል ውሸቱን ነው፡፡ እግዚአብሄር የሰው አገልግሎቱ የሚፈተነው በትንኙ ነው፡፡ የሰው አገልግሎቱ የሚለካው በጥቃቅን ነገር ላይ ባለው ታማኝነት ነው፡፡ አንዴ የጀመረውን ነገር እንስከሚጨርሰው ድርስ የሚያመን ሰው ለሚያገልግለው ሰው በረከት ይሆናል እርሱንም በአገልግሎቱ እያደገና ለታላላቅ ሃላፊነት እየተሾመ ይሄዳል፡፡
ከሁሉ በሚያንስ የታመነ በብዙ ደግሞ የታመነ ነው፥ ከሁሉ በሚያንስም የሚያምፅ በብዙ ደግሞ ዓመፀኛ ነው። የሉቃስ ወንጌል 16፡10
5.     እረፍት
አገልግሎት የሚጀምረው ከእረፍት ነው፡፡ በእግዚአብሄር ላይ ያላረፈ ሰው እግዚአብሄርን አገልግላለሁ ማለት ከንቱ ነው፡፡ እግዚአብሄር ያላሳረፈው ሰውን ሊያሳርፍ አይችልም፡፡ በእግዚአብሄር አገልግሎት ያልረካ ሰውን ሊያረካ አይችልም፡፡ ሰው እግዚአብሄር ለእርሱ መልካም እንደሆነ በማወቅ ማረፍ አለበት፡፡ ሰው ከማገልገሉ በፊት እግዚአብሄር ለእርሱ ግድ እንደሚለውና የሚያስፈልገውን ነገር ሁሉ እንደሚያሟላለት ማወቅ አለበት፡፡ ሰው እግዚአብሄር እረኛው እንደሆነና የሚያሳጣው እንደሌለ በእግዚአብሄር እረኝነት ማረፍ አለበት፡፡ ሰው የእግዚአብሄርን ስራ ሲሰራ እግዚአብሄር የእርሱን ስራ እንደሚሰራለት ያላመነ እና ስለኑሮው የሚጨነቅ ሰው እግዚአብሄርን ማገልገል አይችልም፡፡ ሰው እግዚአብሄርን የሚያገለግለው ከጭንቀት ባረፈበት መጠን ብቻ ነው፡፡
እንግዲህ፦ ምን እንበላለን? ምንስ እንጠጣለን? ምንስ እንለብሳለን? ብላችሁ አትጨነቁ፤ ነገር ግን አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፥ ይህም ሁሉ ይጨመርላችኋል። የማቴዎስ ወንጌል 6፡31፣33
6.     ፍቅር
እግዚአብሄር ለማገልገል እግዚአብሄርን መውደድ ግዴታ ነው፡፡ አገልግሎት ከፍቅር ይመነጫል፡፡ የማንወደውን ሰው ልናገለግለው አንችልም፡፡ የምንወደውን ሰው እንኖርለታለን እናገለግለዋለን፡፡ እግዚአብሄርን ማገልገል ሰውን መውደድ ይጠይቃል፡፡ እግዚአብሄርንም ማገልገል የማይወዱንንና የማይቀበሉንን ሰዎች ጭምር በእኩልነት መውደድ ይጠይቃል፡፡
ጠቦቶቼን ጠብቅ አለው። ሦስተኛ ጊዜ፦ የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ፥ ትወደኛለህን? አለው። ሦስተኛ፦ ትወደኛለህን? ስላለው ጴጥሮስ አዘነና፦ ጌታ ሆይ፥ አንተ ሁሉን ታውቃለህ፤ እንድወድህ አንተ ታውቃለህ አለው። ኢየሱስም፦ በጎቼን አሰማራ። የዮሐንስ ወንጌል 21፡17
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ክርስቶስ #ጌታ #ፍቅር #ታማኝነት #ቅንነት #ተገኝነት #ትህትና #እምነት #እረፍት #ቅድሚያ #እምነት #እውቀት #መደገፍ #ሰንበት #በመንፈሴ #በሃይል #በብርታት #ፀጥታ #መመለስ #ማረፍ #ፅድቁን #ኢየሱስ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #ፀጥታ #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #መታመን #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

Saturday, December 15, 2018

ሀገሪቱን የሚጎዱ ሁለቱ ፅንፍ አስተሳሰቦች


ሰብአዊ መብት ማንም ለማንም የሚሰጠው ችሮታ አይደለም፡፡ ሰው በእግዚአብሄር ሲፈጠር የተሰጠው ጥቅም ነው፡፡ ሰብአዊ መብት በማንም መልካም ፈቃደ የሚሰጥ መብት አይደለም፡፡ በነፃነት የማሰብ እና የመናገር መብት በብአዊ መብት በመወለድ ብቻ የሚገኝ መብት ነው፡፡ ሰው ማድረግ የሚችለው ትልቁ ነገር የሰውን ሰብአዊ መብት ማክበር ነው፡፡
ሰሞኑን እየሰማናቸው ያሉት የሰብአዊ መብት ገፈፋዎች እጅግ የሚያሰቅቁ አንገትን የሚያስደፉ ናቸው፡፡ ማንኛውም ሰው ሰብአዊ መብቱ ሲገፈፍ እንደ ህዝብ ያዋርደናል፡፡ በማንኛውም ሰው ላይ የተደረገ ስቃይ እንደ ህዝብ ዝቅ ዝቅ ያደርገናል፡፡ በእኛ አይነት ፍጡር በሰው ላይ የተደረገ ስቃይ ሁላችንም ያሳንሰናል፡፡  
ግፍን ያደረግ ሰው መጀመሪያ የናቀው በመልኩና በአምሳሉ ሰውን የፈጠረውን እግዚአብሄርን ነው፡፡ ይህን ግፍና ስቃይ በሰው ላይ ያደረጉ ሰዎች ሰውን ከመናቃቸው በፊት የናቁት ሁሉን የሚያየውን እግዚአብሄርን ነው፡፡ ይህን ግፍና መከራ እርዳታ በሌለው ሰው ላይ ያደረጉ ሰዎች መጀመሪያ ያልፈሩትና የተዳፈሩት እግዚአብሄርን እንጂ ሰውን አይደለም፡፡  
ይህንን ግፍና መከራ ያደረጉ ሰዎች በእግዚአብሄር ፊት ማዘን ንስሃ መግባት ይኖርባቸዋል፡፡ እነዚህ ሰዎች የፍትህ አካላት ተከታትለው ባይደርሱባቸውም እንኳን ራሳቸውን አሳልፈው መስጠት አለባቸው፡፡ ሰዎች ከሰው ፍርድ ማምለጥ ቢችሉም ከእግዚአብሄር ፍርድ ግን ማምለጥ አይችሉም፡፡ በእግዚአብሄር እጅ ከመውደቅ በሰው እጅ መውደቅ ይሻላል፡፡
እነዚህ ግፍን ያደሬጉ ሰዎች ንስሃ እስካልገቡና ከእግዚአብሄርና ከሰው ንቀታቸው እስካልተመለሱ ድረስ ከሰው ፍርድ ቢያመልጡ ከእግዚአብሄር ፍርድ ግን አያመልጡም፡፡ እነዚህ ሰዎች ሊደግፍ የሚፈልግ ማንኛውም ሰው ከእግዚአብሄርና ከሰው የንቀት አስተሳሰባቸውና ስራቸው ስራቸው ጋር በመተባበር የእግዚአብሄርን ፍርድ ለራሱ ያከማቻል፡፡ ግፍን ለሰራው ሰውም ይሁን ሊደብቃቸው ለሚሞክረው ሰው ያለው ብቸኛ አማራጭ ሰዎቹን አሳልፉ በመስጠት ከእግዚአብሄር ቁጣ መዳን እና ማዳን ነው፡፡
እውነት አትለወጥም፡፡ ፍትህ አይለወጥም፡፡ እውነትን እንደምናከብርና ፍትህን እንደምንወድ የምናሳየው ፍትህ ያጓደለው ማንም ይሁን ማን አሳልፈን በመስጠት ነው፡፡ ነገር ግን ፍትህ የምንለው ሌላ ሌላው ሰው ላይ ሲሆን ከሆነና እኛ ላይ ሲደርስ ግን ፍትህ የማይሰራ ከሆነ ውሸተኞች ነን፡፡ በወገንተኝነት ስሜት አላግባብ የምናደርገው ነገር የሚጎዳው ራስን ነው፡፡ ዛሬ በጭካኔ በሌላ ላይ ክፉ የሰራው ሰው ነገ በእኛ ላይ አይሰራውም ብለን ማሰብ ሞኝነት ነው፡፡ በወገንተኝነት ስሜት ፍትህን ማጨለም ከእግዚአብሄ ጋር መጣላት ነው፡፡
ለወገኔ ይጠቅማል በማለት ወይም በከንቱ ውዳሴ ምክንያት አንድ እንኳ አታድርጉ፥ ነገር ግን እያንዳንዱ ባልንጀራው ከራሱ ይልቅ እንዲሻል በትሕትና ይቍጠር፤ ወደ ፊልጵስዩስ ሰዎች 2፡3
እነዚህ ግንፍን ያደረጉ ሰዎች ማንም ይሁን ማንም ካልተመለሱ ግፍ የሚሰራ ጥሩ መንገድ ስለሚመስላቸው ነገ እና ከነገ ወዲያ በሌላው ሰው ላይ እንደማያደርጉት ማንም እርግጠኛ ሊሆን አይችልም፡፡ በእግዚአብሄር እጅ መውደቅ እጅግ አስፈሪ ነገር ነው፡፡ እግዚአብሄር እንዳያዋርደው የሚፈልግ ሰው ቀድሞ ራሱን ማዋረድ አለበት፡፡
በሌላ መልኩ ደግሞ እነዚህ ስልጣናቸውን አላግባብ ተጠቅመው ግፍን ፈፅመዋል ብለው የሚጠረጠሩት በአብዛኛው ከአንድ ብሄር የተውጣጡ በመሆናቸው ያንን ብሄር ሁሉ እንደ ግፈኛ ማየት ሌላው ፅንፍ አስተሳሰብ ነው፡፡ ሚዛናዊነትን መጠበቅ እንጂ ሁለት ስህተት ትክክልን አይሰራም፡፡ ስህተት የሚስተካከል በትክክል እንጂ በስህተት አይደለም፡፡ ብዙ እግዚአብሄርን የሚፈሩ ከግፍ የራቁ ህሊናቸውን ጠብቀው የሚኖሩ የተባረኩ ሰዎች ከሁሉም ብሄር አሉ፡፡ ጥቂቶች ባደረጉት ግፍ ብሄር ሁሉ እንዳደረገው አድርጎ ማቅረብ በብሄሩ ላይ የማይገባ ስጋትን ስለሚጭር ከግፈኞቹ ጋር አላግባብ እንዲተባበር ይፈትነዋል፡፡  
ጥቂት ሰዎች ያደረጉት ግፍ ምክኒያት በሚሊዮኖች የሚቆጠርን ሰው አውጥቶ መጣል ብልህነት አይደለም፡፡ በጥቂት ክፉ ሰዎች ድርጊት በሚሊዮን የሚቆጠርን ህዝብ እንደ ክፉ ህዝብ መፈረጅ በአንድ ብሄር ላይ ስጋትን ከመጨመር ውጭ ለማንም አይጠቅምም፡፡
እንዲሁም ሰዎች በወንጀል ተጠረጠሩ ማለት ወንጀለኞች ናቸው ማለት እንዳይደለ መታወቅ አለበት፡፡ የህግ የበላይነት በሰፈነበት ስርአት ሰው በነፃ ፍርድ ቤት ጉዳዩ ታይቶ ጥፋተኛ እስካልተባለ ድረስ ንፁህ ሰው ነው፡፡ ሰው ተጠረጠረ ማለት ተፈረደበት ማለት አይደለም፡፡
ሰው ለምን ተጠረጠረ ማለት አግባብ አይደለም፡፡ ሰው እንዲፈረድበት ንፁሁም ሰው ይሁን ጥፋተኛም ሰው ሊጠረጠር ይገባዋል፡፡  
እነዚህም ግፍን ያደረጉ እና ንስሃ ያልገቡ ሰዎች መሸሸግ የሚፈልጉት በዚህ ሁለት ፅንፍ አስተሳሳብ ውስጥ ነው፡፡ እነዚህ ግፍን የፈፀሙ ሰዎች ለፍርድ ሲፈለጉ አንድ ብሄር ላይ የተነጣጠረ ጥቃት እንደተፈፀመባቸው ለማስመሰል የማይፈነቅሉት ድንጋይ የለም፡፡ እነዚህ ግፍ የፈፀመሙ ሰዎች ድል ሰው ግፍ ባደረገው ግለሰብ ላይ ማተኮርን ትቶ አለአግባብ በህዝብ ላይ እንዲያተኩር ማድረግ ነው፡፡
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ፖለቲካ #ፍትህ #ፅንፍ #ስጋት #ፀሎት #ፍርድቤት #ህግአውጪ #ህግአስፈፃሚ #ምክርቤት #ፖሊስ #ዲሞክራሲ #ህግተርጉዋሚ #ተቃውሞ #ሃዘን #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ