Popular Posts

Friday, March 16, 2018

ይብቃችሁ!!

ያላችሁ ይብቃችሁ፣ ጌታ ራሱ አልተውህም ፡ ከቶ አልለቅህም ብሏልና ዕብራዊያን 13÷5
እግዚአብሄር የፈጠረን ለክብሩ ነው፡፡ ኢየሱስን እንደአዳኝ ለተቀበለን ለሁላችን እግዚአብሄር አባታችን ነው፡፡
እኛ የእግዚአብሄርን መንግስትና ፅድቅ ስንፈልግ እርሱ የእኛን ፍላጎት እንደሚያሟላ ደጋግሞ አስረግጦ ነግሮናል፡፡
እንግዲህ፦ ምን እንበላለን? ምንስ እንጠጣለን? ምንስ እንለብሳለን? ብላችሁ አትጨነቁ፤ ይህንስ ሁሉ አሕዛብ ይፈልጋሉ፤ ይህ ሁሉ እንዲያስፈልጋችሁ የሰማዩ አባታችሁ ያውቃልና። ነገር ግን አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፥ ይህም ሁሉ ይጨመርላችኋል። ማቴዎስ 6፡31-33
ኢየሱስ ሲናገር ለገንዘብና ለጌታ ለሁለት ጌቶች መገዛት እንደማንችል አስተምሮናል፡፡ ገንዘብን ከተከተልን ጌታን መከተል እንደማንችል አስተምሮናል፡፡
ለሁለት ጌቶች መገዛት የሚቻለው ማንም የለም፤ ወይም አንዱን ይጠላል ሁለተኛውንም ይወዳል፤ ወይም ወደ አንዱ ይጠጋል ሁለተኛውንም ይንቃል፤ ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አትችሉም። ማቴዎስ 6፡24
የእብራዊያን ፀሃፊ ደግሞ አካሄዳችን ገንዘብን ያለ መውደድ እያስጠነቀቀን ነው፡፡
አካሄዳችሁ ገንዘብን ያለ መውደድ ይሁን፥ ያላችሁም ይብቃችሁ፤ እርሱ ራሱ፦ አልለቅህም ከቶም አልተውህም ብሎአልና፤ ዕብራዊያን 13፡5
እግዚአብሄር ራሱ መሰረታዊ ፍላጎታችንን ለማሟላት ቃል ሰለገባ አካሄዳችን ገንዘንብን በመውደድ መሆን እንደሌለበት ያስተምረናል፡፡ እርሱ ራሱ ስለእኛ ፍላጎት መሟላት ሃላፊነት ስለወሰደ ገንዘብን የመውደድ አካሄድ እንደማይጠቅመን አስተምሮናለ፡፡ አልጥልህም አልተውህም እያለ ገንዘብን መውደድ ከጥቅሙ ጉዳቱ እንደሚያመዝን ይነግረናል፡፡ ራሱ እግዚአብሄር እኛ ቢጎድልብን ተጠያቂ እንደሚሆንና ሃላፊነት እንደወሰደ አስረግጦ ይነግረናል፡፡
የፈጠረንና የሰራን እርሱ እግዚአብሄር ነው፡፡ እግዚአብሄር ራሱ በግል ያለህ ይብቃሃል ካለ እኛ ማን ነን ያለን አይበቃንም የምንለው፡፡ እግዚአብሄር እያንዳንዱ ፍጥረትህን ያውቃል፡፡ ምን እንደሚያስፈልገን ከእኛ በላይ ከእኛ ቀድሞ እግዚአብሄር ያውቃል፡፡
ሳትለምኑት አባታችሁ የሚያስፈልጋችሁን ያውቃልና። ማቴዎስ 6፡8
ያላችሁ ይብቃችሁ የሚለውን መታዘዝ ትህትና ነው፡፡ ያላችሁ ይብቃችሁ የሚለውን መጠራጠር ከእግዚአብሄር በላይ አውቃለሁ ማለት ትእቢት ነው፡፡
አንተ የጠየቅከው ከሆነ እንደ ፈቃዱ ካልሆነ ላይመለስ ይችላል፡፡ በዚህ ጉዳይ ግን እርሱ ራሱ ነው አልጥልህም አልተውህም የሚለው፡፡
ምክኒያቱም ገንዘብን መውደድ የክፋት ሁሉ ስር ነው፡፡ ገንዘብን የሚወድ ሰው እግዚአብሄርን አይወድም ገንዘብም የሚወድ ሰው ሰውን አይወድም፡፡ ሰው እግዚአብሄርንና ሰውን ካልወደደ ምንም ክፋት ሊሰራ ይችላል፡፡ ገንዘብን ለሚወድ ሰው መዋሸት ፣ ማታለል ፣ ማጭበርበር ፣ ሙስና መጥላትና መግደል የህይወት አካሄዱ ነው፡፡
ገንዘብን የሚወድ ሰው በአካሄዱ ይታወቃል፡፡ እግዚአብሄንና ሰውን የሚወድ ሰውም አንዲሁ በአካሄዱ ይታወቃል፡፡
አካሄዳችሁ ገንዘብን ያለ መውደድ ይሁን፥ ያላችሁም ይብቃችሁ፤ እርሱ ራሱ፦ አልለቅህም ከቶም አልተውህም ብሎአልና፤ ዕብራዊያን 13፡5

#ኢየሱስ #ጌታ #ጭንቀት #ልጅነት #ይብቃችሁ #አልጥልህም #አልተውህም #ብርሃን #ጨው #ምስክርነት #ጌታክርስቶስ #ርስት #ብድራት #ስራ #የኑሮሃሳብ #የእለትእንጀራ #የባለጠግነትምቾት #አቅርቦት #መሰረታዊፍላጎት #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #መናገር #ፅናት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment