Popular Posts

Saturday, March 10, 2018

የአንደኝነት ሃላፊነት

ብዙ ሰዎች አንደኛ መሆን ይፈልጋሉ፡፡ አንደኛ መሆን ምንም ጥፋተኛ የለበትም፡፡ ኢየሱስ ፊተኛ መሆን የሚፈልግህ ንስሃ ይግባ አይደለም ያለው፡፡ ፊተኛ የሚሆንበትን መንገዱን ነው እንጂ ያሳየው በፍፁም አልገሰፀም፡፡ አንደኛ መሆን መልካም ነው፡፡
ከእናንተም ማንም ፊተኛ ሊሆን የሚወድ የእናንተ ባሪያ ይሁን፤ ማቴዎስ 20፡27
እነርሱ ግን በመንገድ፦ ከሁሉ የሚበልጥ ማን ይሆን? ተባብለው ነበርና ዝም አሉ። ተቀምጦም አሥራ ሁለቱን ጠርቶ፦ ሰው ፊተኛ ሊሆን ቢወድ ከሁሉ በኋላ የሁሉም አገልጋይ ይሁን አላቸው። ማርቆስ 9፡34-35
ስለቤተክርስትያን መሪነት ሲናገር ማንም ኤጲስ ቆጶስነትን ቢፈልግ መልካምን ሥራ ይመኛል የሚለው ቃል የታመነ ነው። (1ኛ ጢሞቴዎስ 3፡1) ይለናል፡፡
ግን ኤጲስ ቆጶስነትን የሚፈልግ እንዲህ ሊሆን ይገባዋል እያለ የኤጲስ ቆጶስነትን ሃላፊነት ይዘረዝርልናል፡፡ 1ኛ ጢሞቴዎስ 3፡2-7
ኢየሱስ ማንም አንደኛ መሆን የሚፈልግ ጥፋት አጥፍቶዋል ንስሃ ይግባ አላለም፡፡ እንዲያውም በትክክለኛው መንገድ እንድንሽቀዳደም ቃሉ ያበራታታናል፡፡
እርስ በርሳችሁ ለመከባበርም ተሽቀዳደሙ (አዲሱ መደበኛው ትርጉም) ሮሜ 12:10
ኢየሱስ የሚያስጠነቅቀንምን አንደኛ መሆንን ሳይሆን አንደኛ የምንሆንበትን መንገድና አንደኛ የምንሆንበትን ምክኒያት ነው፡፡
አንዳንድ ሰው ለአንደኝነት ያለውን እጅግ መጓጓት ስታዩ አንደኝነት ሃላፊነት እንደሆነ እንዳልገባቸው ትመለከታላችሁ፡፡
በአለም ያሉ ሰዎች አንደኛ የሚሆኑት በተከታዮቻቸው ለመጠቀምና ለመክበር ነው፡፡ በትክክለኛው መንገድ አንደኛ መሆን ግን ለማገልገል ፣ ለመጥቀምና ለማክበር ነው፡፡  
አንደኛው ሰው ሁሉም የሚያገለግሉት ሳይሆን የሁሉ አገልጋይ ነው፡፡
አንደኛው ሰው ሁሉም የሚችሉት ሳይሆን ሁሉንም የሚችል ቻይ ሰው ነው፡፡ አንደኛ ሰው ሁሉም የሚሸከሙት ሳይሆን ሁሉንም የሚሸከም ልበ ሰፊ ሰው ነው፡፡ አንደኛ ሰው ሁሉም የሚመርጡት ሳይሆን ማንንም የማይጥል ሁሉንም የሚመርጥ ሰው ነው፡፡
አንደኛ ሰው ሁሉምን ስራ የሚሰራ ነው
አንደኛ ሰው የስራው አለመሳካትን ወቀሳ የሚቀበል ነው፡፡ ሰዎች ሌሎችን ሰዎችን ይወቅሳሉ፡፡ አንደኛ የሆነ ሰው ግን ለወቀሳ ሃላፊነትን ይወስዳል፡፡ አንደኛ ሰው እኔ ካለሳረሁት ማንም አይደጨሰራውም ይላል፡፡ አነደኛ ሰው ማነመ ያልሰራውን ስራ ይሰራል፡፡ አንደኛ ሰው ማንም መስራት ያልፈለገውን የተመናቀውን ስራ ይሰራል፡፡
ዋና ሠራተኛ ሁሉን ነገር ይሠራል፤ ምሳሌ 2610
አንደኛ መሆን ለሌሎች ምሳሌ መሆን ነው
አንደኛ ስትሆን ሰዎች ሁዑ ለምሪት አንተን ይመለከታሉ፡፡ አንደኛ ስትሆን የብዙዎች ምሳሌ ስለሆንክ የፈለግከውን መናገር አትችልም፡፡ አንደኛ ስትሆን የፈለግከውንም ማድረግ አትችልም፡፡ አንደኛ ስትሆን የሚከተሉህ ሰዎች ሸክም በልብህ ይኖራል፡፡ አንደኛ ስትሆን ያንተን ብቻ ሳይሆን የሌሎችን ህይወት ትኖራለህ፡፡
የእግዚአብሔርን ቃል የተናገሩአችሁን ዋኖቻችሁን አስቡ፥ የኑሮአቸውንም ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነታቸው ምሰሉአቸው። ዕብራውያን 13፡7
አንደኛ መሆን ለሌሎች ጥላ መሆን ነው
ለምሳሌ በገንዘብ አንደኛ ከሆንክ ባንተ ኩባንያ ውስጥ ለሚሰሩ ሰዎች ጥላ ትሆናለህ፡፡ ሰዎች የራሳቸውን ስራ መፍጠር ሳያስፈልጋቸው በከፈትከው ኩባንያ ውስጥ በመስራት መሰረታዊ ፍላጎታቸውን ያሟላሉ ልጆቻቸውን ያስትምራሉ፡፡ ገቢያ ቀንሰ ጨመረ በማለት እንዳንተ ሳይጨነቁ ባንተ እውቀት ጥላ ስር ሰላማዊ ኑሮን ይኖራሉ፡፡ አንተ ኩባንያ ውስጥ የሚጠበቅባቸውን ሃላፊነት ብቻ በመወጣት እንደ አንት ስለኩባንያው አጠቃላይ ሃላፊነትን ሳይወስዱ ኑሮዋቸውን ይኖራሉ፡፡
አንደኛ ስትሆን ፍትሃዊ መሆን ነው
አንደኛ ስትሆን ወሳኝ ስትሆን ውሳኔህ የብዙዎችን ህይወት የሚነካ ሲሆን አንደኝነት ሃላፊነት እንጂ ጥቅም እንዳይደለ ትረዳለህ፡፡
የንጉሥ ቃል ኃይለኛ ነውና፤ ይህንስ ለምን ታደርጋለህ? ማን ይለዋል? መክብብ 8፡4
አንደኛ የሆነ ሰው ሃያል ሰው ሃይሉን በምን አቅጣጫ እንደሚያፈሰው ትልቅ ሃላፊነት ተጥሎበታል፡፡
አንደኛ ሰው ሃይሉን ለክፋት እንዳይጠቀምበት ትልቅ ሃላፊነት አለበት፡፡ አንደኛ የሆነ ሰው ሃይሉን ለመልካም ከመጠቀም እንዳይከለክል ትልቅ ሃላፊነት አለበት፡፡
ወደ ሞት የሚነዱትን ታደግ፤ ሊታረዱ የተወሰኑትን አድን። እነሆ፥ ይህን አላወቀውም ብትል፥ ልቦችን የሚመረምር እርሱ አያስተውልምን? ነፍስህንም የሚመለከት እርሱ አያውቅምን? ለሰውስ ሁሉ እንደ ሥራው አይመልስለትምን? ምሳሌ 24፡11-12
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #አገልጋይ #ባሪያ #አንደኛ #ፍትህ #ጥላ #ትህትና #መልካምነት #መከባበር #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ብፅእና  #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #ውድድር #ፉክክር #ዋጋ

No comments:

Post a Comment