Popular Posts

Saturday, March 3, 2018

ለህይወትህ ዋጋ ስጥ

ክፉን በክፉ ፈንታ ወይም ስድብን በስድብ ፈንታ አትመልሱ በዚህ ፈንታ ባርኩ እንጂ፥ በረከትን ልትወርሱ ለዚህ ተጠርታችኋልና። ሕይወትን ሊወድ መልካሞችንም ቀኖች ሊያይ የሚፈልግ ሰው፥ መላሱን ከክፉ ከንፈሮቹንም ተንኰልን ከመናገር ይከልክል፤ ከክፉ ፈቀቅ ይበል፥ መልካምንም ያድርግ፥ ሰላምን ይሻ ይከተለውም፤ 1ኛ ጴጥሮስ 3፡9-11
ህይወት ውድ ስጦታ ነው፡፡ በህይወትህ ለመልካም ነገር እንጂ ለክፉ ነገር እንዳትሰራ ተጠንቀቅ፡፡ የህይወትህ ፍፃሜ በረከት መሆን ሲገባው በክፋት ለበረከት እንቅፋት አትሁን፡፡ በረከትን መውረስ ሲገባህ በክፋት ህይወትህን አታጎሳቁል፡፡ በበረከት ልትታወቅ ሲገባህ በህይወትህ ያለውን በረከት በክፋት አታጥፋው፡፡ ክፋት ውስጥ በመግባት የጠራህለትን የበረከት ህይወት አታጉድፍ፡፡  
ለህይወቱ ዋጋ የሚሰጥ ሰው ህይወትን ከሚበክል ነገር ይጠነቀቃል፡፡ ህይወቱን የሚወድ ሰው ከህይወት ከሚያጎድል ነገር ይሸሻል፡፡
የተጠራችሁት ለበረከት ነው፡፡ የተጠራችሁት ለማበብ ለመውጣት ለማሸነፍ ነው፡፡ ለተጠራችሁበት  መጠራት እንደሚገባ ተመላለሱ፡፡
1.      ክፉን በክፉ ፋንታ አትመልሱ ስድብን በስድብ ፋንታ
ክፉን በክፉ መመለስ ከደረጃችን ያወርደናል፡፡ ደረጃችን በመባረክ መባረክ ነው፡፡ ስድብን በስድን ፋንታ መመለስ እግዚአብሄር ልጅነት ክብር አይፈቅድልንም፡፡
እኔ ግን እላችኋለሁ፥ በሰማያት ላለ አባታችሁ ልጆች ትሆኑ ዘንድ ጠላቶቻችሁን ውደዱ፥ የሚረግሙአችሁንም መርቁ፥ ለሚጠሉአችሁም መልካም አድርጉ፥ ስለሚያሳድዱአችሁም ጸልዩ፤ ማቴዎስ 5፡44-45
2.     ክፉ በመናገርና በስድብ ፋንታ ባርኩ እንጂ
ክፉ የሚያደርግባችሁን ሰው ባርኩ፡፡ ክፉ ለሚያደርግላችሁ ሰው መልካም አድርጉ፡፡ ክፉ ለሚያደርግባችሁ ሰው ፀልዩ፡፡
የሚያሳድዱአችሁን መርቁ፥ መርቁ እንጂ አትርገሙ። ሮሜ 12፡14
3.     መላሱን ከክፉ ከንፈሮቹንም ተንኰልን ከመናገር ይከልክል
አንደበት የልማትም የጥፋትም ታላቅ ሃይል አለው፡፡ አንደበታችሁን ለጥፋት አታውሉ፡፡ አንደበታችሁን ሰውን ለመስረቅ ለማረድና ለማጥፋት በመጠቀም ከሰይጣን ጋር አትተባበሩ፡፡ በአንደበታችሁ የሰይጣን መጠቀሚያ አትሁኑ፡፡
እንዲሁም አንደበት ደግሞ ትንሽ ብልት ሆኖ በታላላቅ ነገር ይመካል። እነሆ፥ ትንሽ እሳት እንዴት ያለ ትልቅ ጫካ ያቃጥላል። ያዕቆብ 3፡5
4.     ከክፉ ፈቀቅ ይበል፥ መልካምንም ያድርግ
ክፉ ማድረግ የትልቅነት ስሜት ሊሰጣችሁ ይችላል፡፡ አዎ ጉልበተኛ ናችሁ ክፉም ማድረግ ትችላላችሁ፡፡ ነገር ግን ክፋት ከህይወትና ከበረከት ያጎድላችኋል፡፡ ክፉ ማድረግን አውቃችሁ ተውት፡፡ ክፉ ለማድርግ ስትፈተን መልካምን አድርግ፡፡ ክፋት ማድረግ ሌላውን ብቻ ሳይሆን እኛንም ነው የሚጎዳው፡፡
ብትበደሉ አይሻልምን? ብትታለሉስ አይሻልምን? ነገር ግን እናንተ ትበድላላችሁ ታታልሉማላችሁ፥ ያውም ወንድሞቻችሁን። 1ኛ ቆሮንቶስ 6፡7-8
5.     ሰላምን ይሻ ይከተለውም፤
ሰላም እንደ ድንገት አይመጣም፡፡ ሰላም ትህትናን ይጠይቃል፡፡ ሰላም ትጋትን ይጠይቃል፡፡ ሰላም ራስን ማዋረድን ይጠይቃል፡፡
የሚያስተራርቁ ብፁዓን ናቸው፥ የእግዚአብሔር ልጆች ይባላሉና። ማቴዎስ 5፡9
በሰላም ማሰሪያ የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ትጉ።  ኤፌሶን 4፡3
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ባርኩ #ክፉ #መልካም #በረከት #ልትወርሱ #ትህትና #መልካምነት #መከባበር #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ብፅእና  #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #አንደበት #ከንፈር #ስድብ

No comments:

Post a Comment