Popular Posts

Saturday, March 31, 2018

በዋጋ ተገዝታችኋልና ለራሳችሁ አይደላችሁም

በዋጋ ተገዝታችኋልና ለራሳችሁ አይደላችሁም፤ 1ኛ ቆሮንቶስ 6፡19-20
በሰው ህይወት የባለቤትነት ጥያቄ ሲመለስ ብዙ ጥያቄዎች ይመለሳሉ፡፡ የባለቤትነት ጥያቄ ሲመለስ የተለያዩ የመብት ጥያቄዎች  ይመለሳሉ፡፡
አንድ ነገር የማን ነው የሚለው ጥያቄ ሲመለስ ማን መብት አለው የሚለውም ጠያቄ አብሮ ይመለሳል፡፡ አንድ ነገር ባለቤቱ ማን አንደሆነ ጥርት ያለ ነገር ከሌለ በነገሩ ላይ ማን ምን መብት አለው የሚለው ጥያቄ ሊመለስ አይችልም፡፡
እግዚአብሄር እኛን የፈጠረን ለክብሩ ነው፡፡ እግዚአብሄር እኛን የፈጠረን ለራሱ ነው፡፡ እግዚአብሄር የፈጠረን ለእኛ ለራሳችን አይደለም፡፡ ይህን እውነት ካልተረዳን ሌላ ምንም እውነት ልንረዳ አንችልም፡፡ በዚህ ካልተግባባን በሌላ በምንም ልንግባባ አንችልም፡፡ እኛ ፈጣሪዎች አይደለንም፡፡ እኛ የእግዚአብሄር የፈጠረን ፍጡሮች ነን፡፡ የህይወታችን ባለቤት እግዚአብሄር ብቻ ነው፡፡
እርሱ አምላካችን ነውና፥ እኛ የማሰማርያው ሕዝብ የእጁም በጎች ነንና። መዝሙር 95፡7
እግዚአብሄር ለክብሩ ፈጥሮናል፡፡ እኛ የእርሱ ነን፡፡ እኛ የራሳችን አይደለንም፡፡
በስሜ የተጠራውን ለክብሬም የፈጠርሁትን፥ የሠራሁትንና ያደረግሁትን ሁሉ አምጣ እለዋለሁ። ኢሳያስ 43፡6-7
እግዚአብሄር በእኛ ላይ ሙሉ ባለመብት ነው፡፡ እኛ በራሳችን ላይ መብት የለንም፡፡
እንደ ሸክላ ሠሪ ጭቃ የምትቈጠሩ አይደላችሁምን? በውኑ ሥራ ሠሪውን፦ አልሠራኸኝም ይለዋልን? ወይስ የተደረገው አድራጊውን፦ አታስተውልም ይለዋልን? ኢሳያስ 29፡16
ከሠሪው ጋር ለሚታገል ወዮለት! በምድር ሸክላዎች መካከል ያለ ሸክላ ነው። ጭቃ ሠሪውን፦ ምን ትሠራለህ? ወይስ ሥራህ፦ እጅ የለውም ይላልን? ኢሳያስ 459
ሰው እግዚአብሄር አታድርግ ያለውን ነገር በማድረግ በማመፁ ለሃጢያትና ለሰይጣን ተሽጦ ነበር፡፡ እግዚአብሄር ልጁን ኢየሱስን በመስቀል ላይ መስዋእት እንዲሆንልን በማድረግ እኛን በደሙ መልሶ ገዛን፡፡
በውድ ልጁም፥ እንደ ጸጋው ባለ ጠግነት መጠን፥ በደሙ የተደረገ ቤዛነታችንን አገኘን እርሱም የበደላችን ስርየት። ኤፌሶን 1፡7
አሁን ደግሞ በክርስቶስ ኢየሱስ አዳኝነት ያመንን ሁላችን  በክርስቶስ ኢየሱስ ደም በከበረ ዋጋ ተገዝተናል፡፡
ከአባቶቻችሁ ከወረሳችሁት ከከንቱ ኑሮአችሁ በሚያልፍ ነገር በብር ወይም በወርቅ ሳይሆን፥ ነውርና እድፍ እንደ ሌለው እንደ በግ ደም በክቡር የክርስቶስ ደም እንደ ተዋጃችሁ ታውቃላችሁ። 1ኛ ጴጥሮስ 1፡18-19
በዋጋ ተገዝታችኋልና ለራሳችሁ አይደላችሁም፤ 1ኛ ቆሮንቶስ 6፡19-20
ከአሁን በኋላ ለራሳችን በመሞት ህይወት ለሰጠን ለእርሱ እንኖራለን፡፡
ስለዚህ የራሳችን አይደለንም፡፡ ኢየሱስ የሞተው ለራሳችን እንድንሞት ነው፡፡ ኢየሱስ የሞተው ለሞተልን ለእርሱ እንድንኖር ነው እንጂ ወደፊት ለራሳችን እንዳንኖር ነው፡፡
ይህን ስለቆረጥን የክርስቶስ ፍቅር ግድ ይለናልና፤ አንዱ ስለ ሁሉ ሞተ፤ እንግዲያስ ሁሉ ሞቱ፤ በሕይወትም ያሉት ስለ እነርሱ ለሞተውና ለተነሣው እንጂ ወደ ፊት ለራሳቸው እንዳይኖሩ ስለ ሁሉ ሞተ። 2ኛ ቆሮንቶስ 5፡14-15
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ባለቤት #ዋጋ #መዋጀት #ብር #ወርቅ #ደም #ክብር #ራእይ #አላማ #ግብ #ውሳኔ #ኢየሱስ #ክርስቶስ #ጌታ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #ብርሃን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #መንገድ #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ  

No comments:

Post a Comment