Popular Posts

Saturday, March 3, 2018

ከሁሉ በፊት እርስ በርሳችሁ አጥብቃችሁ ተዋደዱ

ፍቅር የኃጢአትን ብዛት ይሸፍናልና ከሁሉ በፊት እርስ በርሳችሁ አጥብቃችሁ ተዋደዱ። 1ኛ ጴጥሮስ 4፡8
ከሁሉ በፊት አጥብቃችሁ ተዋደዱ፡፡ ከሁሉ በፊት ተዋደዱ፡፡ ከሁሉ በፊት፡፡  ከመስራታችን ከመናገራችን ከመሆናችን ከመስጠታችን ከማገልገላችን ሁሉ በፊት እንዋደድ፡፡ ከፍቅር ውጭ የሚደረግ መልካም ነገር ከንቱ ነው፡፡ ከፍቅር ውጭ የሚደረግ መስዋእትነት ምንም አይጠቅምም፡፡ ከፍቅር ውጭ የሚደረግ ሃይማኖዊ እንቅስቃሴ ሁሉ ከንቱ ነው፡፡ ካለ ፍቅር የተደረገ ነገር ብክነት ነው፡፡  
በሰዎችና በመላእክት ልሳን ብናገር ፍቅር ግን ከሌለኝ እንደሚጮኽ ናስ ወይም እንደሚንሽዋሽዋ ጸናጽል ሆኜአለሁ። ትንቢትም ቢኖረኝ ምሥጢርንም ሁሉና እውቀትን ሁሉ ባውቅ፥ ተራሮችንም እስካፈልስ ድረስ እምነት ሁሉ ቢኖረኝ ፍቅር ግን ከሌለኝ ከንቱ ነኝ። ድሆችንም ልመግብ ያለኝን ሁሉ ባካፍል፥ ሥጋዬንም ለእሳት መቃጠል አሳልፌ ብሰጥ ፍቅር ግን ከሌለኝ ምንም አይጠቅመኝም። 1ኛ  ቆሮንቶስ 13፡1-3
ስለዚህ ነው ኢየሱስ መስዋእት ልታደረግ ስትል ፍቅር እንደተበላሸ ካወቅክ መጀመሪያ አስተካክል፡፡ ከመባና ስጦታ በፊር ፍቅር ይቀድማል፡፡ መባ ሊዘገይ ይችላል ፍቅር ግን ሊዘገይ አይችልም፡፡ ስጦታ ቢዘገይ ይሻላል ፍቅር ከሚዘገይ፡፡ ምክኒያቱም ካለ ፍቅር የተደረገ መባ ይበላሻል፡፡ ካለፍቅር የተደረገ አገልግሎት በከንቱ ዘመንን ማባከን ነው፡፡
እንግዲህ መባህን በመሠዊያው ላይ ብታቀርብ፥ በዚያም ወንድምህ አንዳች በአንተ ላይ እንዳለው ብታስብ፥ በዚያ በመሠዊያው ፊት መባህን ትተህ ሂድ፥ አስቀድመህም ከወንድምህ ጋር ታረቅ፥ በኋላም መጥተህ መባህን አቅርብ። ማቴዎስ 5፡24
በተለያየ መልኩ በሰዎች እንበደላለን፡፡ በደል መሸፈን አለበት፡፡ በደል ካልተሸፈነ ሰላም አይመጣም፡፡ በደል ካልተሸፈነ አንድነት አይመጣም፡፡ በደል ይቅር ካልተባለ ሰላም የለም፡፡ በደል ካልታለፈ የትም አንደርስም፡፡
በደልን ሊሸፍን የሚችለው ፍቅር ብቻ ነው፡፡ ፍቅር በደለን የመሸፈን ታላቅ ሃይል አለው፡፡ ፍቅር በደልን አይቆጥርም፡፡
(ፍቅር ) የራሱንም አይፈልግም፥ አይበሳጭም፥ በደልን አይቆጥርም፤ 1ኛ ቆሮንቶስ 13፡5
ፍቅር ፈጥኖ በመተው እንጂ በደልን በመቁጠር ምንም እንደማይጠቀም ይረዳል፡፡ ፍቅር በመተው እንጂ በመያዝ እንደሚጎዳ ያውቃል፡፡ ፍቅር በመተውና በመርሳት እንጂ በደለን በመቁጠር አይደሰትም፡፡
ፍቅር የበደለን ብዛት ይሸፍናል፡፡ ፍቅር ያለው ሰው ከበደለው ሰው ጋር ለመኖር ይችላል፡፡ ፍቅር ያለው ሰው ከበደለው ሰው ጋር ለመስራት አይቸግረውም፡፡
በሰላም ለመኖር በደል መሸፈን አለበት፡፡ በደል እንዲሸፈን ምህረት የሚያደርግ ይቅርታ የሚያደርግ ሰው ይጠይቃል፡፡ ምህረትና ይቅርታ ለማድረግ ፍቅር ያስፈልጋል፡፡
ፍቅር አንድን በደል ብቻ ሳይሆን የበደለን ብዛት ይሸፍናል፡፡
ቁልፉ ያለው እናንተ ጋር ነው፡፡ እናንተን የሚያድናችሁ የሚበድል ሰው መታጣቱ አይደለም፡፡ እናንተን ነፃ የሚያደጋችሁ ሰው ሁሉ ለእናንተ መልካም መሆኑ አይደለም፡፡
ቁልፉ ያለው ሌላው ሰው ጋር ሳይሆን እናንተ ጋር ነው፡፡ እናንትን ነፃ የሚያደርጋችሁ ከልባችሁ መዋደዳችሁ ነው፡፡ መስራት ያለባችሁ በሌላው ሰው መልካምነት ሳይሆን በእናንተ ፍቅር ላይ ነው፡፡ ስለሌላው መልካምነት ሃላፊነት የለባችሁም፡፡ ስለ ራሳችሁ ከልብ መዋደድ ግን ሃላፊነት አለባችሁ፡፡  
ስለዚህ ከልባችሁ አጥብቃችሁ ተዋደዱ፡፡
ፍቅር የኃጢአትን ብዛት ይሸፍናልና ከሁሉ በፊት እርስ በርሳችሁ አጥብቃችሁ ተዋደዱ። 1 ጴጥሮስ 48
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes

#ኢየሱስ #ጌታ #ፍቅር #አጥብቃችሁተዋደዱ #ተዋደዱ #መውደድ #ሃጢያት #በደል #መንፈስ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ትጋት #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #ትዕግስት #መንፈስቅዱስ #ምስክር #ልብ #መሪ

No comments:

Post a Comment