Popular Posts

Sunday, February 18, 2018

እንደ ሙሉ ደስታ ቍጠሩት

ወንድሞቼ ሆይ፥ የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ አውቃችሁ፥ ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ እንደ ሙሉ ደስታ ቍጠሩት ትዕግሥትም ምንም የሚጎድላችሁ ሳይኖር ፍጹማንና ምሉዓን ትሆኑ ዘንድ ሥራውን ይፈጽም። ያዕቆብ 1፡2-4
በምድር ላይ ኢየሱስን ስንከተል ልዩ ልዩ ፈተና ይገጥመናል፡፡ በተለያየ ጊዜ ልዩ ልዩ ፈተና ይመጣል፡፡ ፈተናው ዘርፈ ብዙ ነው፡፡ ፈተናው በሁሉም የህይወታችን አቅጣጫ ነው፡፡ አንዴ በቤተሰብ ፣ ሌላ ጊዜ በስራ ፣ ሌላ ጊዜ በአገልግሎት ፣ ሌላ ጊዜ በቤተክርስትያን ሌላ ጊዜ በጓደኝነት ፣ ሌላ ጊዜ በዘመድ ፈተናዎች ይመጣሉ፡፡
አንዳንዴ በገንዘብ ፣ ሌላ ጊዜ በጊዜ ፣ ሌላ ጊዜ በልጆች ፣ ሌላ ጊዜ በጤንነት ፣ ሌላ ጊዜ በግንኙነት እንፈተናለን፡፡  
ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ ፈተናውን የምትቀበሉበት አቀባበል የፈተናውን አላማ ግብ መምታት ወይም አለመምታት ይወስነዋል፡፡
ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ ራሳችሁን ዝቅ አድርጋችሁ የምትመለከቱ ከሆነ እንደሙሉ ደስታ መቁጠር ያቅታችኋል፡፡ ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስበናችሁ እንዳውም ይህን ፈተና ያልፈዋል ብሎ በተማመነብን በእግዚአብሄር ደስ ሊለን ይገባል፡፡ ከምንችለው በላይ እንድንፈተን የማይፈቅድ እግዚአብሄር የታመነ ነውና፡፡
. . . ነገር ግን ከሚቻላችሁ መጠን ይልቅ ትፈተኑ ዘንድ የማይፈቅድ እግዚአብሔር የታመነ ነው፥ . . . 1ኛ ቆሮንቶስ 10፡13
ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ ደስ ሊላችሁ የሚገባው እግዚአብሄር ይህን ፈተና እንድታልፉት አድርጎ እንዳሳደጋችሁ ስታስቡ ነው፡፡ ለእናንተ የሚያስጨንቅ ነው እግዚአብሄር ግን ከታገሱ በድል ይወጡታል ብሎ አምኖዋል፡፡ የፈተናው ግዙፍነት የእናንተን እድገት ስለሚያሳይ ደስ ይበላችሁ፡፡ የፈተናው ትልቅነት እናንት እንኳን ስለማታውቁት ስለውስጥ እድገታችሁ ይመሰክራል፡፡
ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ እናንት ላይ ብቻ እንደመጣ ፣ የተሳሳታችሁት ነገር እንዳለ ፣ እንደሳታችሁና ያልገባችሁነገር እንዳለ ማሰብ ፈተናውን እንደሙሉ ደስታ እንዳትቆጥሩት ያደርጋል፡፡ መልኩ ይለያይ ፣ ደረጃው ይለያይ ፣ ጊዜው ይለያይ እንጂ ሁሉም ሰው ይፈተናል፡፡ ከትልቅ እስከ ትንሽ ይፈተናል፡፡ ለአንዱ ፈተና የሆነው ለሌላው ፈተና ላይሆን ይችላል፡፡ እያንዳንዱ ግን የራሱ የፈተና ድርሻ አለው፡፡ መፈተናችሁ የእውቀት ማነስ ወይም የሃጢያት ምልክት ሳይሆን በአለም የምትኖሩ ወንድሞች የመሆናችሁ ምልክት ነው፡፡
በዓለም ያሉት ወንድሞቻችሁ ያን መከራ በሙሉ እንዲቀበሉ እያወቃችሁ በእምነት ጸንታችሁ ተቃወሙት። 1ኛ ጴጥሮስ 5፡9
ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ ጥቅሙን አለማወቅ በፈተናው ውስጥ ደስ እንዳይላችሁ እንደሙሉ ደስታ እንዳትጥሩት ያደርጋችኋል፡፡ ሁላችንም ለእግዚአብሄር መኖር እንፈልጋለን፡፡ ሁላችንም እግዚአብሄርን ማስደሰት እንፈልጋለን፡፡ ሁላችንም ፍፁም መሆን እንፈልጋለን፡፡ ፈተና የሚያደርገው ነገር ደግሞ ያንኑ ነው፡፡ ፈተናን መታገሳችሁ ምንም ሳይጎድላቸሁ ምሉአንና ፍፁማን እንድትሆኑ ያደርጋችሁዋል፡፡  
ትዕግሥትም ምንም የሚጎድላችሁ ሳይኖር ፍጹማንና ምሉዓን ትሆኑ ዘንድ ሥራውን ይፈጽም። ያዕቆብ 1፡4
ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስብን እንደሙሉ ደስታ ለመቁጠር ፈተና የራሱ ስራ እንዳለው ማወቅ ይጠይቃል፡፡ የፈተና አላማና ስራ እኛን ማጥፋት እንዳይደለ መረዳት እንደሙሉ ደስታ እንድንቆጥረው ያስችለናል፡፡ ፈተና ሲደርስብን እንደሙሉ ደስታ ለመቁጠር ፈተና እኛን እንደማያገኘን ነገር ግን በህወታችን የማያስፈልግን ነገርን እንደሚያራገፍ ገለባውን እንደሚበላ መረዳት ይጠይቃል፡፡ በመከራ በመታገስ መታዘዝን እንማራለን፡፡
ምንም ልጅ ቢሆን፥ ከተቀበለው መከራ መታዘዝን ተማረ፤ ዕብራውያን 5፡8
ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ እንደ ሙሉ ደስታ መቁጠር ያለብን ምክኒያት ፈተና ምንም መውጫ የሌለው ቢመስልም ሁሌ መውጫ መንገድ እንዳለው ማወቅ ነው፡፡ መፍትሄ የሌለው ነገር የለም፡፡ ፈተና ምንም መውጫ የሌለው ቢመስልም የጊዜ ጉዳይ ነው፡፡ ፈተናን ከታገስን ሁሌ መውጫ አለው፡፡ መውጫ የሌለው ፈተና ኖሮ አያውቅም ወደፊትም አይኖርምም፡፡ እንደሙሉ ደስታ እንድትቆጥሩትና እንድትታገሱት እግዚአብሄር ሁሌ መውጫውን ያዘጋጃል፡፡ በደስታ እና በተስፋ እንድታልፉነት መውጫው አስቀድሞ ተዘጋጅቶዋል፡
. . . እግዚአብሔር የታመነ ነው፥ ትታገሡም ዘንድ እንድትችሉ ከፈተናው ጋር መውጫውን ደግሞ ያደርግላችኋል። 1 ቆሮንቶስ 101
ወንድሞቼ ሆይ፥ የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ አውቃችሁ፥ ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ እንደ ሙሉ ደስታ ቍጠሩት ትዕግሥትም ምንም የሚጎድላችሁ ሳይኖር ፍጹማንና ምሉዓን ትሆኑ ዘንድ ሥራውን ይፈጽም። ያዕቆብ 12-4
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ክብር #መዋረድ #መከራ #ፈተና #መፅናት #መታገስ #መውጫ #ትግስት #ፍጹማን #ምሉዓን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ብፅእና #እምነት #አንድነት #ፀጋ  #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment