Popular Posts

Monday, February 12, 2018

ካለ ምክኒያት ወደህ በምክንያት አትጠላም

እግዚአብሔርም ከሩቅ ተገለጠልኝ እንዲህም አለኝ፦ በዘላለም ፍቅር ወድጄሻለሁ ስለዚህ በቸርነት ሳብሁሽ። ኤርምያስ 31፡3
እግዚአብሄር ፍቅር ነው ፡፡ እግዚአብሄር ሰውን ይወዳል፡፡ እግዚአብሄር ሰውን የሚወደው ደግሞ እየመረጠ በምክኒያት አይደለም፡፡ እግዚአብሄር የሚወደን የምንወደድ መልካም ሰዎች ስለሆንን አይደለም፡፡
እግዚአብሄር የሚወደን ካለ ምክንያት ነው፡፡ ምኔን ነው የወደድከው? ምኔ ነው የሳበህ? የቱ ነገሬ ነው ደስ ያለህ እና የወደድከኝ? ተብሎ እግዚአብሄር ቢጠየቅ በዚህ ነው ብሎ የሚመልሰው ምንም ነገር የለም፡፡ ለምን ወደድከኝ ሲባል እንዲሁ ወደድኩህ ነው የሚለው፡፡
በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና። ዮሃንስ 3፡16
እግዚአብሄር የወደደን በማንወደድበት ጊዜ ነው፡፡ እግዚአብሄር የወደደን በንፅህናችንና በቅድስናችን አይደለም፡፡ እግዚአብሄር የወደደን ጠንካሮች ሆነን አይደለም፡፡ እግዚአብሄር የወደደን ደካሞች ሳለን ነው፡፡ እግዚአብሄር የወደደን ሃጢያተኞች ሆነን ነው፡፡
ገና ደካሞች ሳለን ክርስቶስ ዘመኑ ሲደርስ ስለ ኃጢአተኞች ሞቶአልና። ሮሜ 5፡6
እግዚአብሄር የወደደን ጠላቶች ሆንነ ነው፡፡ እግዚአብሄር የወደደን እግዚአብሄርን የማንፈልግ ተሳዳቢዎች ሆነን ነው፡፡ (ሮሜ 3፡10-19)
ነገር ግን ገና ኃጢአተኞች ሳለን ክርስቶስ ስለ እኛ ሞቶአልና እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን የራሱን ፍቅር ያስረዳል። ሮሜ 5፡8
ግዚአብሄር ምንም የሚወደድ ነገር ሳይኖረን ካልጠላን እና ከወደደን አሁንም እኛን የሚጠላበት ምንም ምክኒያት አይኖረውም፡፡
የእግዚአብሄር ፍቅር በእኛ ሁኔታ ላይ የተደገፈ አይደለም፡፡ የእግዚአብሄር ፍቅር እንደፍቅር ተቀባዩ እና እንደ ተወደደው ሰው አይለዋወጥም፡፡
እግዚአብሄር ታማኝ አፍቃሪ ነው፡፡ ሰው ፍቅሩን ቢቀበለውም ባይቀበለውም እግዚአብሄር የዘላለም አፍቃሪ ነው፡፡ እግዚአብሄር በፍቅር ያዘጋጀውን የመዳኛ መንገድ ሰው ቢቀበልም ባይቀበለም ፍቅሩን ተቀብሎ ቢድንም ባይድንም የሰው ሃላፊነት እንጂ የእግዚአብሄር ሃላፊነት አይደለም፡፡ ሰው የእግዚአብሄርን ፍቅር ተጠቅሞ ከዘላለም ጥፋት ቢያመልጥም ባያመልጥም የስው ጥፋት እንጂ የእግዚአበሄር አለመውደድ አይደለም፡፡ እግዚአብሄር የዘላለም አፍቃሪ ነው፡፡
ባናምነው፥ እርሱ የታመነ ሆኖ ይኖራል፤ ራሱን ሊክድ አይችልምና። 2ኛ ጢሞቴዎስ 2፡13
ካለምክኒያት ከወደደ አሁን ደግሞ ሃሳቡን ለውጦ በምክኒያት አይጠላም፡፡ ስለዚህ ነው ዘማሪ ሃና_ተክሌ ካለ ምክኒያት ወደህ በምክኒያት አትጠላም በማለት በአራት ቃላት የእግዚአብሄርን የማይለወጥ ፍቅር በዝማሬ የገለጠችው፡፡
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes

#ኢየሱስ #ጌታ #እግዚአብሔር #ፍቅር #ምክንያት #ያለምክንያት #እንዲሁ #የዘላለም #ታማኝ #ምንጭ #መውደድ #ስሜት #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ትጋት #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #ትዕግስት #መንፈስቅዱስ #ማስተዋል #ልብ #መሪ  

No comments:

Post a Comment