Popular Posts

Thursday, February 1, 2018

በጥበብ መነገድ ይሻላል

በህይወት ስኬታማ የሚያደርገን ዋጋ የሚሰጠውን ነገር ዋጋ ስንሰጥና ቅድሚያ የሚሰጠውን ነገር ቅድሚያ ስንሰጥ ብቻ ነው፡፡ በህይወት በጣም የምንጓጓለት ነገር ሁሉ የሚያጓጓ እንዳይደለ የምናውቀው በጥበብ ነው፡፡ በህይወት ቅድሚያ የሚሰጠው ነገር ብለን የምናስበው ነገር ሁሉም ቅድሚያ እንደማይሰጠው የምናውቀው በጥበብ ነው፡፡ ጥበብ ጉልበታችንን ጊዜያችንን በማይሆን ነገር ላይ እንዳናባክን ያደርገናል፡፡  
በህይወታችን ጉዳዬ የምንላቸው ብዙ ነገሮች ጉዳዬ የሚባሉ አይደሉም፡፡ በህይወት ጠቃሚ የሚመስሉን ነገሮች ሁሉ እንደምናስበው ጠቃሚ እንዳልሆኑ በጥበብ እናስተውላለን፡፡
ጥበብን የሚያገኝ ሰው ምስጉን ነው፥ ማስተዋልንም ገንዘቡ የሚያደርግ፤ በወርቅና በብር ከመነገድ ይልቅ በእርስዋ መነገድ ይሻላልና። ምሳሌ 3፡13-14
ጥበብን የሚያገኝ ሰው ምስጉን ነው፡፡ ጥበብን የሚያገኝ ሰው ተመራጭ ፣ ዕድለኛ ፣ ተጠቃሚ ፣ የታደለ ፣ የተመረጠ ፣ ደስተኛ ፣  የተባረከና የሚቀናበት ሰው ነው፡፡
በማስተዋል ሃብታም የሆነ ምስጉን ነው፡፡ ይበልጥ ማስተዋል ያለው ይበልጥ ባለጸጋ ነው፡፡  
ምክኒያቱም በብር ሃብታም ከመሆን በጥበብ ሃብታም መሆን ይሻላል፡፡ በወርቅ ከመብዛት በጥበብ መብዛት ይሻላል፡፡ ጥበብ ከሚጎድልብን ገንዘብ ቢጎድልብን ይሻላል፡፡  
ከእግዚአብሄር ጋር እንደሚገባ እንድትኖር የሚያደርግህ እግዚአብሄርን የመፍራት ጥበብ እንጂ ሃብት አይደለም፡፡
የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው፤ ሰነፎች ግን ጥበብንና ተግሣጽን ይንቃሉ። ምሳሌ 1፡7
የህይወት ፈተና በገጠመህ ጊዜ ከፈተና የሚያስመልጥህ ሃብትህ ሳይሆን ጥበብ ነው፡፡
ወንድሞቼ ሆይ፥ የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ አውቃችሁ፥ ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ እንደ ሙሉ ደስታ ቍጠሩት ትዕግሥትም ምንም የሚጎድላችሁ ሳይኖር ፍጹማንና ምሉዓን ትሆኑ ዘንድ ሥራውን ይፈጽም። ከእናንተ ግን ማንም ጥበብ ቢጎድለው፥ ሳይነቅፍ በልግስና ለሁሉ የሚሰጠውን እግዚአብሔርን ይለምን፥ ለእርሱም ይሰጠዋል። ያዕቆብ 1፡2-5
ምንም ነገር ቢኖርህ ለምታስበው አላ ሁሉ አይበቃም፡፡ በህይወት ቅድሚያ የምትሰጠውና ቅድሚያ የማትሰጠው ነገር መኖር አለበት፡፡ ስለዚህ ጥበብ ከሌለህ ቅድሚያ መስጠት እንደምትችል አታውቅም፡፡
ብዙ የምንፈልጋቸው ነገሮች እንደምናስበው ያህል አያስፈልጉንም፡፡ ከዚያ ይበልጥ የሚየስፈልገን ጥበብ ነው፡፡ ብዙ የምንተማመንባቸው ነገሮች የህይወታችንን ጥያቄዎች አይፈቱም፡፡ አብዛኛው የህይወታችን ጥያቄዎች በዝና በገንዘብ በእውቀት አይመለሱም፡፡ ብዙ የህይወታቸን ጥያቄዎች የሚመለሱት በጥበብ ነው፡፡
ጥበብን የሚያገኝ ሰው ምስጉን ነው፥ ማስተዋልንም ገንዘቡ የሚያደርግ፤ በወርቅና በብር ከመነገድ ይልቅ በእርስዋ መነገድ ይሻላልና። ምሳሌ 3፡13-14
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ጥበብ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ማስተዋል #እምነት #ፈተና #ፀሎት #ጌታ #የእግዚአብሄርቃል #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment