Popular Posts

Saturday, February 24, 2018

በውስጥ ሰውነታችሁ በኃይል እንድትጠነክሩ

በመንፈሱ በውስጥ ሰውነታችሁ በኃይል እንድትጠነክሩ . . .  ኤፌሶን 3፡16-17
ሁላችንም ጤናችን እንዲጠበቅና የውጭው ሰውነታችን ለየትኛውም በሽታና አደጋ የማይበገር ጠንካራ እንዲሆን እንፈልጋለን፡፡ ሰውነታችን እንዲጠነክር የሚያስፈልገውን የምግብ ንጥረ ነገር እንመግበዋለን፡፡ የሰውነታችንን ጤንነት በየጊዜው እንከታተላለን፡፡ የሰውነታችንን ጥንካሬ በትጋት እንቆጣጠራለን፡፡
የሰውነታችን ጥንካሬ በምድር ላይ በሚገባ እንድንኖር ያስችለናል፡፡ የሰውነታችን ጥንካሬ የምናስበውን ነገር ተንቀሳቅሰን ከግብ እንድናደርሰው ያስችለናል፡፡ የሰውነታችን ጥንካሬ በምናደርገው ነገር ሁሉ ፍሬያማ እንድንሆን ያስችለናል፡፡  
የውጭው ሰውነታችን የመንፈሳችን የውስጡ ሰውነታችን መኖሪያ ነው፡፡ የውጭ ሰውነታችን እየተንከባከብን የውስጡን ሰውነታችንን ካልተንከባከብነው ምንም ጥቅም የለውም፡፡ የውስጥ ሰውነታችን ካልጠነከረ በእግዚአብሄር መንግስት ውስጥ በመንፈሳዊው አለም እንደሚገባ መኖር አንችልም፡፡ በተፈጥሮ ህፃን ልጅ ካላደገና ካልጠነከረ ወደአለም ውስጥ ገብቶ አምራችና ውጤታማ መሆን እንደማይችል ሁሉ የውስጥ ሰውነታችን ካልጠነከረ በእግዚአብሄር መንግስት ውስጥ ምንም ትርጉም ያለው ነገር ማድረግ አንችልም፡፡ የውስጡ ሰውነታችን ካልጠነከረ ሁሌ ተሸናፊ እንሆናለን፡፡  
የውጭው ሰውነታችን ምንም ቢያምርና ቢጠነክር በውጭው ሰውነታችን ውስጥ የሚኖረው ሰው የውስጡ ሰውነታችን ደካማ ከሆነ ካለፍሬ ይቀራል፡፡
በውስጥ ሰውነታችን ከጠነከርን በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ለመጠበቅና ለመፅናት እንችላለን፡፡ በውስጥ ሰውነታችን ከጠነከረን ሰዎችን የሚያፍገመግመው ነገር አያፍገመግመንም፡፡
እንደ ስሕተት ሽንገላ ባለ ተንኮል በሰዎችም ማታለል ምክንያት በትምህርት ነፋስ ሁሉ እየተፍገመገምን ወዲያና ወዲህም እየተንሳፈፍን ሕፃናት መሆን ወደ ፊት አይገባንም፥ ኤፌሶን 4፡14
ስለዚህ ነው መፅሃፍ ቅዱስ የውስጡን ሰውነታችንን በእግዚአብሄር ቃል እለት እለት ማደስና ማጠንከር እንዳለብን የሚያስተምረው፡፡ የውስጡ ሰውነታችን የሚጠነክረው በእግዚአብሄር መንፈስ ሃይል ነው፡፡
የፈጠረውንም ምሳሌ እንዲመስል እውቀትን ለማግኘት የሚታደሰውን አዲሱን ሰው ለብሳችሁታል፤ ቆላስይስ 3፡10
የእግዚአብሄርን ቃል ከሰማንና ከታዘዝን በዚያም በእምነት ከኖርን የውጭው ሰውነታችን በስደትና በእድሜ ብዛትና በመሳሰሉት ምክኒያቶች ቢጠፋ እንኳን የውስጡ ሰውነታችን በመንፈስ ቅዱስ አማካኝነት እለት እለት ይታደሳል ይጠነክራል፡፡
ስለዚህም አንታክትም፥ ነገር ግን የውጭው ሰውነታችን ቢጠፋ እንኳ የውስጡ ሰውነታችን ዕለት ዕለት ይታደሳል። 2ኛ ቆሮንቶስ 4፡16
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #የስውጥሰውነት #ጥንካሬ #ጠብቅ #እውቀት #ቃል #ህይወት #አገልግሎት #አምልኮ #ፀሎት #ጥሪ #ተመልክተን #መቃጠል #መቀጣጠል #ክብር #አገልግሎት #መዋረድ #መርካት #ፀጋ #እውቀት #ኢየሱስንተመልክተን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ብፅእና #እምነት #ታላቅነት #ማገልገል #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment