Popular Posts

Wednesday, August 22, 2018

ብትፈቅድ

ብትፈቅድ ይህችን ጽዋ ከእኔ ውሰድ፤ ነገር ግን የእኔ ፈቃድ አይሁን የአንተ እንጂ እያለ ይጸልይ ነበር። የሉቃስ ወንጌል 22፡42
ጥቂትም ወደ ፊት እልፍ ብሎ በፊቱ ወደቀና ሲጸልይ፦ አባቴ፥ ቢቻልስ፥ ይህች ጽዋ ከእኔ ትለፍ፤ ነገር ግን አንተ እንደምትወድ ይሁን እንጂ እኔ እንደምወድ አይሁን አለ። የማቴዎስ ወንጌል 26፡39
የፀሎት ዋናው ክፍል የእግዚአብሄር ፈቃድ ማወቅ ነው፡፡ ስላለንበት ሁኔታ የእግዚአብሄር ፈቃድ ማወቅ የፀሎታችን መሰረት ነው፡፡ የእግዚአብሄር ፈቃድ ሳናውቅ የምንፀልየው ፀሎት እንደሚመለስ እርግጠኛ አንሆንም፡፡ ስለሁኔታችን የእግዚአብሄርን ፈቃድ ከቃሉ ካገኘን በኋላ ፀሎት የደቂቃዎች ስራ ነው፡፡
እግዚአብሄር የለመንነውን ሁሉ ሳይሆን እንፈቃዱ የለመንነውን ሁሉ ይሰማናል የለመንነውንም እንቀበላለን፡፡
በእርሱ ዘንድ ያለን ድፍረት ይህ ነው፤ እንደ ፈቃዱ አንዳች ብንለምን ይሰማናል። 1ኛ የዮሐንስ መልእክት 5፡14
እንደፈቃዱ ከለመንን ብቻ እንደተቀበልን እናውቃለን፡፡
የምንለምነውንም ሁሉ እንዲሰማልን ብናውቅ ከእርሱ የለመነውን ልመና እንደ ተቀበልን እናውቃለን። 1ኛ የዮሐንስ መልእክት 5፡15
ፀሎት ትጋትን የሚጠይቅ ስራ ነው፡፡ ፀሎት የእግዚአብሄር ፈቃድ ፈልጎ ማግኘት የሚጠይቅ ስራ ነው፡፡
ምክንያቱም ወደ እግዚአብሔር የሚቀርብ ሁሉ እግዚአብሔር መኖሩንና ከልብ ለሚሹትም ዋጋ እንደሚሰጥ ማመን አለበት። ወደ ዕብራውያን 11፡6 (አዲሱ መደበኛ ትርጉም)
አንዳንድ ክርስትያኖች ግን እንደፈቃዱ መጸፀለይ ስለሚፈልጉ ፈቃዱን ከእግዚአብሄር ቃል ከመፈለግ ይልቅ ሲፀልዩ ብቻ "እንደ ፈቃድህ እንፀልያለን" ወይም "ፈቃድህ ቢሆን ይህን አድርግልን" "ፈቃድህ ቢሆን ያንን አድርግልን" ብለው ፈቃዱን የመለየት ሃላፊነታቸን ወደ እግዚአብሄር ያስተላለፉታል፡፡ ይህ አይነት ፀሎት እንደፈቃዱ መፀለያችንን እርግጠኛ ስለማያደርገን እንደምንቀበል እርግጠኛ አንሆንም፡፡
የእግዚአብሄርን ፈቃድ ከቃሉ ፈልጎ ማግኘት የእኛ ስራ ነው፡፡ የእግዚአብሄን ፈቃድ ፈልገን ለማግኘት ሳንተጋ በጸሎታችን ውስጥ እንደፈቃድህ እያልን የምንለምን ከሆነ የፀሎት ህይወታችን እንዲቀጭጭ እናደርገዋለን፡፡  
የእግዚአብሄርን ፈቃድ አግኝተን በዚያ መሰረት መፀለይ ሲገባን "ብትፈቅድ" እያል ሁሌ የምንፀልይ ከሆነ የፀለየንውን እንደምንቀበል እርግጠኛ ልንሆን በፍፁም እንችልም፡፡  
ኢየሱስ በሌሎቹ ሁሉ ፀሎቶቹ የእግዚአብሄርን ፈቃድ ተረድረቶ እንደ እግዚአብሄር ፈቃድ ይፀልይ ነበር፡፡ ኢየሱስ በሌሎቹ ፀሎቶቹ ሲፀልይ ይፀልይ የነበረው እንድትሰማኝ አውቃለሁ እያለ ነበር፡፡
በመፀሃፍ ቅዱስ ኢየሱስ እንደ ፈቃድህ ብሎ የፀለየው አንድ ጊዜ ብቻ ነው፡፡ ይህም ፀሎት ከልመና ፀሎት የሚለይና ራስን የመስጠት ፀሎት ነበር፡፡ ኢየሱስ ራስን ለመስጠት ያደረገው ለእግዚአብሄር ፈቃድ ራስን በድጋሚ የመስጠት ኑዛዜ እንጂ የእግዚአብሄርን ፈቃድ አውቆ መፀለይ ሲገባው ያንን ክፍተት ለመሸፈን ያወጣው ቃል አይደለም፡፡
በእርሱ ዘንድ ያለን ድፍረት ይህ ነው፤ እንደ ፈቃዱ አንዳች ብንለምን ይሰማናል። የምንለምነውንም ሁሉ እንዲሰማልን ብናውቅ ከእርሱ የለመነውን ልመና እንደ ተቀበልን እናውቃለን። 1 የዮሐንስ መልእክት 5፡14-15
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #የእግዚአብሄርፈቃድ #ፀሎት #ልመና #እንዲሰማን #ቤተክርስትያን #አማርኛ #የእግዚአብሄርቃል #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #መጠየቅ #መንበርከክ #ምስጋና

No comments:

Post a Comment