Popular Posts

Sunday, August 26, 2018

በተስፋ ደስ ይበላችሁ

በተስፋ ደስ ይበላችሁ፤ በመከራ ታገሡ፤ በጸሎት ጽኑ፤ ወደ ሮሜ ሰዎች። 12:12
እኛ በኢየሱስ ከሃጢያት አዳኝነት የምናምንና ኢየሱስ ክርስቶስን የምንከተል ያለን ተስፋ ህያው ተስፋ ነው፡፡ ተስፋችን አይጠፋም ወይም አይጠወልግም፡፡ ተስፋችን ህያው ነው፡፡ ተስፋችን በጊዜው የሚፈጸፀም ነው፡፡
ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን በመነሣቱ ለሕያው ተስፋና ለማይጠፋ፥ እድፈትም ለሌለበት፥ ለማያልፍም ርስት እንደ ምሕረቱ ብዛት ሁለተኛ የወለደን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክና አባት ይባረክ፤ ይህም ርስት በመጨረሻው ዘመን ይገለጥ ዘንድ ለተዘጋጀ መዳን በእምነት በእግዚአብሔር ኃይል ለተጠበቃችሁ ለእናንተ በሰማይ ቀርቶላችኋል። 1 የጴጥሮስ መልእክት 1፡3-5
ተስፋችን እንደሚፈፀም የእግዚአብሄር መንፈስ ማረጋገጫው ነው፡፡ ተስፋችን እንደሚሆንና እንደሚፈፀም የእግዚአብሄር መንፈስ መያዣችን ነው፡፡ በመከራ ውስጥ እንኳን በተስፋ ደስ ይለናል፡፡
ይህም ብቻ አይደለም፥ ነገር ግን መከራ ትዕግሥትን እንዲያደርግ፥ ትዕግሥትም ፈተናን ፈተናም ተስፋን እንዲያደርግ እያወቅን፥ በመከራችን ደግሞ እንመካለን፤ በተሰጠንም በመንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ፍቅር በልባችን ስለ ፈሰሰ ተስፋ አያሳፍርም። ወደ ሮሜ ሰዎች 5፡ 3-5
የእግዚአብሄር ተስፋ ፅኑ ነው፡፡
ስለዚህም እግዚአብሔር፥ የተስፋውን ቃል ለሚወርሱ ፈቃዱ እንደ ማይለወጥ አብልጦ ሊያሳያቸው ስለ ፈቀደ፥ እግዚአብሔር ሊዋሽ በማይቻል በሁለት በማይለወጥ ነገር፥ በፊታችን ያለውን ተስፋ ለመያዝ ለሸሸን ለእኛ ብርቱ መጽናናት ይሆንልን ዘንድ፥ በመሓላ በመካከል ገባ፤ ይህም ተስፋ እንደ ነፍስ መልሕቅ አለን እርሱም እርግጥና ጽኑ የሆነ ወደ መጋረጃውም ውስጥ የገባ ነው፤ ወደ ዕብራውያን 6፡17-19
የተፃፈው ሁሉ ተስፋችንን ለማደስ በተስፋ እንድንፀና ለመርዳት ተፅፏል፡፡
በመጽናትና መጻሕፍት በሚሰጡት መጽናናት ተስፋ ይሆንልን ዘንድ አስቀድሞ የተጻፈው ሁሉ ለትምህርታችን ተጽፎአልና። ወደ ሮሜ ሰዎች 15፡4
ተስፋ ያበረታል፡፡ ተስፋ ያበዛል ይጨምራል፡፡ በፊታችን ያለው ብሩህ ተስፋ ልባቸንን ያነቃቃዋል፡፡
የተስፋ አምላክም በመንፈስ ቅዱስ ኃይል በተስፋ እንድትበዙ በማመናችሁ ደስታንና ሰላምን ሁሉ ይሙላባችሁ። ወደ ሮሜ ሰዎች 15፡13
ከሚመጣው ክብር ጋር ሲመዛዘን የጊዜው መከራ ምንም አይደለም፡፡
ለእኛም ይገለጥ ዘንድ ካለው ክብር ጋር ቢመዛዘን የአሁኑ ዘመን ሥቃይ ምንም እንዳይደለ አስባለሁ። ወደ ሮሜ ሰዎች 8፡18
ተስፋችን በቅርቡ ኢየሱስን እናየዋለን፡፡
ነገር ግን፥ ወንድሞች ሆይ፥ ተስፋ እንደሌላቸው እንደ ሌሎች ደግሞ እንዳታዝኑ፥ አንቀላፍተው ስላሉቱ ታውቁ ዘንድ እንወዳለን። ኢየሱስ እንደ ሞተና እንደ ተነሣ ካመንን፥ እንዲሁም በኢየሱስ ያንቀላፉቱን እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ያመጣቸዋልና። በጌታ ቃል የምንላችሁ ይህ ነውና፤ እኛ ሕያዋን ሆነን ጌታ እስኪመጣ ድረስ የምንቀር ያንቀላፉቱን አንቀድምም፤ ጌታ ራሱ በትእዛዝ በመላእክትም አለቃ ድምፅ በእግዚአብሔርም መለከት ከሰማይ ይወርዳልና፥ በክርስቶስም የሞቱ አስቀድመው ይነሣሉ፤ ከዚያም በኋላ እኛ ሕያዋን ሆነን የምንቀረው፥ ጌታን በአየር ለመቀበል ከእነርሱ ጋር በደመና እንነጠቃለን፤ እንዲሁም ሁልጊዜ ከጌታ ጋር እንሆናለን። ስለዚህ እርስ በርሳችሁ በዚህ ቃል ተጽናኑ። 1ኛ ወደ ተሰሎንቄ ሰዎች 4፡13-18
ኢየሱስን ስናየው መልካም፥ አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ እንዲለን ተስፋ እናደርጋለን፡፡
ጌታውም፦ መልካም፥ አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃል፥ በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው። የማቴዎስ ወንጌል 25
የድል አክሊላችንን ለማግኘት ተስፋ እናደርጋለን፡፡
የሚዘምተው ሁሉ ለጦር ያስከተተውን ደስ ያሰኝ ዘንድ ትዳር በሚገኝበት ንግድ ራሱን አያጠላልፍም። ደግሞም በጨዋታ የሚታገል ማንም ቢሆን፥ እንደሚገባ አድርጎ ባይታገል፥ የድሉን አክሊል አያገኝም። 2 ወደ ጢሞቴዎስ 2፡4-5
የማይጠፋውን አክሊል ለማግኘት ተስፋ እናደርጋለን፡፡
በእሽቅድምድም ስፍራ የሚሮጡት፥ ሁሉ እንዲሮጡ ነገር ግን አንዱ ብቻ ዋጋውን እንዲቀበል አታውቁምን? እንዲሁም ታገኙ ዘንድ ሩጡ። የሚታገልም ሁሉ በነገር ሁሉ ሰውነቱን ይገዛል፤ እነዚያም የሚጠፋውን አክሊል ሊያገኙ ነው፥ እኛ ግን የማይጠፋውን። 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 9፡24-25
ለዚህ ሁሉ ተስፋ መሰረቱ በደሙ ሃጢያታችንን ያጠበው በክብር ተመልሶ የሚመጣው የክብር ተስፋ ያለው ክርስቶስ በእኛ ውስጥ ስለሆነ ነው፡፡
ለእነርሱም እግዚአብሔር በአሕዛብ ዘንድ ያለው የዚህ ምሥጢር ክብር ባለ ጠግነት ምን እንደ ሆነ ሊያስታውቅ ወደደ፥ ምሥጢሩም የክብር ተስፋ ያለው ክርስቶስ በእናንተ ዘንድ መሆኑ ነው። ቆላስይስ 1፡27
በተስፋ ደስ ይበላችሁ
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ተስፋ #በልባችን #የእግዚአብሄርቤተመቅደስ #ክርስቶስ #ክርስቶስበእኛ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #የእግዚአብሄርቃል #መፅሃፍቅዱስ #ክርስቶስ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #በመንፈሱ #የእግዚአብሄርቤተመቅደስ #እምነት

No comments:

Post a Comment