Popular Posts

Tuesday, August 7, 2018

በጕብዝናህ ወራት ፈጣሪህን አስብ

የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጕብዝናህ ወራት ፈጣሪህን አስብ፤ ደስ አያሰኙም የምትላቸውም ዓመታት ሳይደርሱ፤መጽሐፈ መክብብ 121
ብዙ ሰዎች የሚዘናጉትና ህይወታቸውን የሚያባክኑት ወደፊት ጊዜ አለኝ እድል አለኝ ብለው ሲያስቡ ነው፡፡
ያለን አንድ እድል ዛሬ እንደሆነ መፅሃፍ ቅዱስ ነገ ምን አንደሚሆን አታውቅምና ስለነገው አትመካ በማለት ያስታውሰናል፡፡  
ቀን የሚያመጣውን ምን እንደ ሆነ አታውቅምና ነገ በሚሆነው አትመካ። መጽሐፈ ምሳሌ 271
እንደድካም ወራት በጉብዝና ወራት እግዚአብሄርን ማሰብ አይቀልም፡፡ ሁሉንም ማድረግ የምንችል በሚመስለን ጊዜ የእግዚአብሄርን እርዳታ መፈለግ ቀላል አይደለም፡፡ ከእግዚአብሄር ፍጥነት አልፈን በፍጥነት መሄድ የምንችል በሚመስለን ጊዜ በእግዚአብሄር ለመመከር ዝግ ማለት ይከብዳል፡፡ ሁሉን ነገር ማድረግ በቻልን ጊዜ ያን ጊዜ እግዚአብሄር በእርሱ እንድንደገፍ ይፈልጋል፡፡  
ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ፤ መንፈስስ ተዘጋጅታለች ሥጋ ግን ደካማ ነው አለው። የማቴዎስ ወንጌል 26፡41
ፈተና ሳይመጣ በሰላ ጊዜ መከራ የሚመጣ አይመስልም፡፡ ሰው ወደ እግዚአብሄር መቅረብ ያለበት ፈተና ሳይመጣ በዝምታው ቀን ነው፡፡
ስለዚህ ቅዱስ ሁሉ በምቹ ጊዜ ወደ አንተ ይለምናል፤ ብዙ የጥፋት ውኃም ወደ እርሱ አይቀርብም። መዝሙረ ዳዊት 326
እግዚአብሄር የለም የሚለውን ሰው ጨምሮ በመከራ ቀን እግዚአብሄርን መፈለግ የሁሉም ነው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር የሚፈልገው በሰላሙ ጊዜ በዝምታው ጊዜና በስኬቱ ጊዜ እግዚአብሄርን እንድንፈልግ ለእርሱ አምላክነት እውቅና እንድንሰጥ ነው፡፡ ሁሉ ነገር ከፍ በሚያደርገን ጊዜ ራሳችንን እንድናዋርድ እግዚአብሄር ይፈልጋል፡፡ ሁሉ ነገር በራስህ ትችላለህ ጉልበት አለህ አቅሙ አለህ በሚልህ ጊዜ እርሱን እንድትፈልግ ነው፡፡
ባለህ ጊዜ በምትችል ጊዜ በጉልበትህ ጊዜ ራስሀን ማዋረድ ይገባል፡፡ በከፍታህ ጊዜ ትህትናን መፈለግ ጥበብ ነው፡፡
የተዋረደው ወንድም ግን በከፍታው፥ ባለ ጠጋም በውርደቱ ይመካ፤ እንደ ሣር አበባ ያልፋልና። ፀሐይ ከትኵሳት ጋር ይወጣልና፥ ሣርንም ያጠወልጋልና፥ አበባውም ይረግፋልና፥ የመልኩም ውበት ይጠፋልና፤ እንዲሁ ደግሞ ባለ ጠጋው በመንገዱ ይዝላል። የያዕቆብ መልእክት 1፡9-11
ሰው ራሱን ሙሉ ለሙሉ መስጠት ያለበት አሁን ነው፡፡ ሰው ራሱን አሁን ለእግዚአብሄር ለመስጠት ከሳሳት ህይወቱን ያባክነዋል፡፡ አይ አሀነ ችግር የለም የራሴን መንገድ ልሂድና በኋላ እመለሳለሁ የሚል ሰው ስለመመለሱ ምንም ማረጋገጫ የለውም፡፡ ሰው ለእግዚአብሄር ራሱን ሙሉ ለሙሉ ለእግዚአብሄ ፈቃድ ለመስጠት የሚድነው አሁን ነው፡፡
በተወደደ ሰዓት ሰማሁህ በመዳንም ቀን ረዳሁህ ይላልና፤ እነሆ፥ የተወደደው ሰዓት አሁን ነው፤ እነሆ፥ የመዳን ቀን አሁን ነው። 2ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 6፡2
የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጕብዝናህ ወራት ፈጣሪህን አስብ፤ ደስ አያሰኙም የምትላቸውም ዓመታት ሳይደርሱ፤መጽሐፈ መክብብ 12፡1
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #እምነት #ሃሳብ #አእምሮ #ልብ #እግዚአብሔርንመፍራት #ጕብዝና #ጥበብ #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ  #እምነት #ቃል  #ማደስ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment