Popular Posts

Thursday, August 9, 2018

የሰይጣን የማጥቂያ መንገድ

የዲያብሎስን ሽንገላ ትቃወሙ ዘንድ እንዲቻላችሁ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ ልበሱ። መጋደላችን ከደምና ከሥጋ ጋር አይደለምና፥ ከአለቆችና ከሥልጣናት ጋር ከዚህም ከጨለማ ዓለም ገዦች ጋር በሰማያዊም ስፍራ ካለ ከክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት ጋር ነው እንጂ። ስለዚህ በክፉው ቀን ለመቃወም፥ ሁሉንም ፈጽማችሁ ለመቆም እንድትችሉ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ አንሡ። እንግዲህ ወገባችሁን በእውነት ታጥቃችሁ፥ የጽድቅንም ጥሩር ለብሳችሁ፥ በሰላም ወንጌልም በመዘጋጀት እግሮቻችሁ ተጫምተው ቁሙ፤ በሁሉም ላይ ጨምራችሁ የሚንበለበሉትን የክፉውን ፍላጻዎች ሁሉ ልታጠፉ የምትችሉበትን የእምነትን ጋሻ አንሡ፤ የመዳንንም ራስ ቁር የመንፈስንም ሰይፍ ያዙ እርሱም የእግዚአብሔር ቃል ነው። ወደ ኤፌሶን ሰዎች 6፡11-17
የሰይጣን መዋጊያ መሳሪያዎች
1.      ውሸት
እውነት የሰው ሃይል  ነው፡፡ እውነት የእግዚአብሄር ቃል ነው፡፡
ሰይጣም ማንንም በግድ ሃጢያት ማሰራት አይችልም፡፡ ሰይጣን ማንንም ሰው አያስገድድም፡፡ ሰይጣን ሃይል የሚያገኘው በማታለል እውነትን ካስጣለን ብቻ ነው፡፡ መፅሃፍ ቅዱስ ወገባችሁን በእውነት ታጠቁ የሚለው እውነት የሰይጣንን ውሸት የማሸነፊያ ታላቅ መሳሪያ ስለሆነ ነው፡፡
ለእውነት እንጂ በእውነት ላይ ምንም ለማድረግ አንችልምና። 2ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 13፡8
የሰይጣን ሃይል የእግዚአብሄርን ቃል የማያውቁትን ሰዎችን ማሳሳት ነው፡፡
ነገር ግን እባብ በተንኮሉ ሔዋንን እንዳሳታት፥ አሳባችሁ ተበላሽቶ ለክርስቶስ ከሚሆን ቅንነትና ንጽሕና ምናልባት እንዳይለወጥ ብዬ እፈራለሁ። 2 ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 11፡3
2.     ሃጢያት
ሰይጣን ሃይል የሚያታገኘው በፅቅድ ባልሆነ በሃጢያት የህይወት ዘይቤያችን ነው፡፡ እኛ በህይወታችን ስፍራን ካልሰጠነው ሰይጣን በህይወታችን ስፍራ የሚያገኝበትና የሚያሸንፈን ምንም መንገድ የለም፡፡ መፅሃፍ ቅዱስ የፅድቅን ጥሩር ልበሱ የሚለን ካለንፁህ ህይወት የሰይጣን መጫወቻ ስለምንሆን ነው፡፡  
በቁጣችሁ ላይ ፀሐይ አይግባ፥ ለዲያብሎስም ፈንታ አትስጡት። ወደ ኤፌሶን ሰዎች 4፡27
3.     ረብሻና ጭንቀት
ሰይጣን እኛን ስለኑሮ ማስጨነቅ ከቻለ የተሰጠንን የእግዚአብሄርን መንግስት አላማ ሊያስጥለን ይችላል፡፡ ሰይጣነ ሊያስጨንቀን ካልቻለ በዘመናችን የእግዚአብሄርን ፈቃድ አገልግለን ማለፍ ንእንቻለዐን፣፡ ከጭንቀትና ረብሸኻ ራሳችንን ከጠበቅን በህይወታችን ሙሉ ፍሬ እናፈራለን፡፡
በእሾህ መካከል የተዘራውም ይህ ቃሉን የሚሰማ ነው፥ የዚህም ዓለም አሳብና የባለጠግነት መታለል ቃሉን ያንቃል፥ የማያፈራም ይሆናል። የማቴዎስ ወንጌል 13፡22
4.     ጥርጥር
ከእግዚአብሄር ጋር ለመገናኘትና አብረን ለመስራት እምነት ወሳኝ ነው፡፡ በህይወታችን በእግዚአብሄር ፍሬያማ እንዳንሆን ሰይጣን ከሚዋጋበት አንዱ መንገድ የጥርጥር ሃሳብ በመላክ እምነታችን ማስጣል ነው፡፡
የሰይጣን አላማ በሁለት ሃሳብ እንድናነክስና ከእግዚአብሄር እንዳንቀበል አእምሮዋችንን በጥርጥር ሃሳብ ማጥለቅለቅ ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል ሰምተን የምናደርግ ከሆንን ግን በእምነት ሙሉ ፍሬ እናፈራለን፡፡ ለዚህ ነው በህይወታችን የእምነትን ጋሻ ማንሳት የሚያስፈልገው፡፡
የመንግሥትን ቃል ሰምቶ በማያስተውል ሁሉ፥ ክፉው ይመጣል፥ በልቡ የተዘራውንም ይነጥቃል፤ በመንገድ ዳር የተዘራው ይህ ነው። የማቴዎስ ወንጌል 13፡19
ኢየሱስም መልሶ፦ እውነት እላችኋለሁ፥ እምነት ቢኖራችሁ ባትጠራጠሩም፥ በበለሲቱ እንደ ሆነባት ብቻ አታደርጉም፤ ነገር ግን ይህን ተራራ እንኳ፦ ተነቅለህ ወደ ባሕር ተወርወር ብትሉት ይሆናል፤ የማቴዎስ ወንጌል 21፡21
5.     የመዳንን ተስፋ ማጨለም
የሰማይ የዘላለም ህይወት ተስፋ ታላቅ ጉልበታችን ነው፡፡ ሰይጣን ግን የዘላለሙን ህይወት ተስፋ ከላስጣለን ሁሉንም ነገር ሊያስጥለን ይችላል፡፡ የእግዚአብሄር ደስታ ሃይላችን ነው፡፡ ደስታን የሚሰጠን ተስፋ ነው፡፡
በተስፋ ደስ ይበላችሁ፤ በመከራ ታገሡ፤ በጸሎት ጽኑ፤ ወደ ሮሜ ሰዎች። 12:12
ተስፋ ታላቅ ጉልበት ነው፡፡ ሰይጣን ሰውን ተስፋውን ካጨለመ ህይወቱን ያጨልማል፡፡ መፅሃፍ ቅዱስ የመዳንንም ራስ ቁር አድርጉ የሚለን ስለዚህ ነው ፡፡ 
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ሰይጣን #ዲያብሎስን #ሽንገላ #ሃሳብ #አእምሮ #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ብፅእና  #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment