Popular Posts

Saturday, June 16, 2018

ነገር ግን በቃልህ

ዓሣ አጥማጆች ግን ከእነርሱ ውስጥ ወጥተው መረቦቻቸውን ያጥቡ ነበር። ነገሩንም ከጨረሰ በኋላ፥ ስምዖንን፦ ወደ ጥልቁ ፈቀቅ በል መረቦቻችሁንም ለማጥመድ ጣሉ አለው። ስምዖንም መልሶ፦ አቤቱ፥ ሌሊቱን ሁሉ አድረን ስንደክም ምንም አልያዝንም፤ ነገር ግን በቃልህ መረቦቹን እጥላለሁ አለው። የሉቃስ ወንጌል 5፡2፣4-5
ጴጥሮስ የዘመናት ልምዱን ሁሉ ተጠቅሞ በዚያ ሌሊት አሳ ሊያጠምድ ሲሞክር አድሯል፡፡ ነገር ግን ምንም አሳ ሊያጠምድ አልቻለም፡፡ ጴጥሮስ አሳ ማጥመድ የጀመረው ኢየሱስ ባናገረው ጊዜ አይደለም፡፡ ጴጤሮስ አሳ ማጥመድ የጀመረው ሌሊቱ ሲጀምር ነው፡፡ ጴጥሮስ ጴጥሮስ አሳ ማጥመድ መሞከር የጀመረው አሳ ይገኝበታል ብሎ የሚያስበው ምቹ ጊዜ ነበር፡፡ ነገር ግን አሳ ማጥመድ አልቻለም፡፡
ጴጥሮስ ሰነፍ አይደለም፡፡ ጴጥሮስ ሌሊቱን ሙሉ ሲሞክር ነበር፡፡ ነገር ግን አሳ ሊያጠምድ አልቻለም፡፡ ጴጥሮስ አሳ ለማጥመድ አለ የሚባለውን መንገድ ሁሉ ሞክሯል፡፡ ጴጥሮስ አሳ ለማጥመድ ያለውን እውቀት ሁሉ አንጠፍጥፎ ተጠቅሞዋል፡፡ ጴጥሮስ አሳ ለማጥመድ ያለውን ጉልበት ሁሉ ተጠቅሞ ሞክሮ አሳ ማጥመድ ግን አልተሳካለትም፡፡ ጴጥሮስ አሳ ለማጥመምድ ጊዜ ሰጥቶ ጠብቆ ሞክሯል ነገር ግን አልቻለም፡፡
ጴጥሮስ አሳ ለማጥመድ መሞከር ደክሞታል ሰልችቶታል፡፡ ለጴጥሮስ አንድ ተጨማሪ አሳ የማጥመድ ሙከራ ማድረግ ጉልበትንና ጊዜን ማባከን ነው፡፡
ያለፈበት የአሳ ማጥመድ ልምድ ሁሉ የሚነግረው አይቻልም ነው፡፡ ያለፈው ሌሊት ሁሉ አሳ ማጥመድ እንደማይቻል አስተምሮታል፡፡ ያለውን እውቀት ሁሉ ተጠቅሞ አሳ ማጥመድ ባለመቻሉ አሳ ለማጥመድ የሚያስችል የቀረው አንድም እውቀት አልነበረም፡
ኢየሱስ መረብህን ጣል ሲለው "ነገር ግን" ያለው ለዚያ ነው፡፡
ስምዖንም መልሶ፦ አቤቱ፥ ሌሊቱን ሁሉ አድረን ስንደክም ምንም አልያዝንም፤ ነገር ግን . . . የሉቃስ ወንጌል 5፡5
እኛም አንዳንድ ጊዜ በህይወት እንደዚህ አይነት ደረጃ ላይ እንደርሳለን፡፡ እግዚአብሄር እንደሚመራን እምነን ያደረግናቸው ነገሮች ሁሉ ወደውጤት እንዲመጡ አሁንም አንድ ተጨማሪ ነገር እንድናደርግ ይጠብቁብናል፡፡ ጨረስን ያላደረግነው ምንም ነገር የለም ስንል ይህንን አድርግ የሚል የእግዚአብሄር ድምፅ ይመጣል፡፡  
ፀልየን ፀልየን ፀልየን አንድ ተጨማሪ ፀሎት ለመፀለይ ጉልበት ያጥረናል፡፡
የእግዚአብሄር ቃል ግን እስኪመለስ እንድንፀልይና እግዚአብሄን በማመን እንድንቀጥል ያስተምረናል፡፡
ለምኑ፥ ይሰጣችሁማል፤ ፈልጉ፥ ታገኙማላችሁ፤ መዝጊያን አንኳኩ፥ ይከፈትላችሁማል። የሚለምነው ሁሉ ይቀበላልና፥ የሚፈልገውም ያገኛል፥ መዝጊያንም ለሚያንኳኳ ይከፈትለታል። የማቴዎስ ወንጌል 7፡7-8
እግዚአብሔር እንኪያስ ቀንና ሌሊት ወደ እርሱ ለሚጮኹ ለሚታገሣቸውም ምርጦቹ አይፈርድላቸውምን? እላችኋለሁ፥ ፈጥኖ ይፈርድላቸዋል። ነገር ግን የሰው ልጅ በመጣ ጊዜ በምድር እምነትን ያገኝ ይሆንን? የሉቃስ ወንጌል 18፡7-8
በተስፋ ደስ ይበላችሁ፤ በመከራ ታገሡ፤ በጸሎት ጽኑ፤ ወደ ሮሜ ሰዎች 12፡12
እግዚአብሄርን አመስግነን አመስግነን አመስግነን ከምናልፍበት አስቸጋሪ ነገር አንፃር አንድ ተጨማሪ ምስጋናን ለማመስገን ይደክመናል፡፡
እግዚአብሄር ቀል ግን የተሰማን ጊዜው ሳይሆን ባልተሰማን ጊዜ የደስታ ምስጋና ሳይሆን የምስጋና መስዋእት እንድንሰዋ ይፈልጋል፡፡
ሳታቋርጡ ጸልዩ፤ በሁሉ አመስግኑ፤ ይህ የእግዚአብሔር ፈቃድ በክርስቶስ ኢየሱስ ወደ እናንተ ነውና። 1ኛ ወደ ተሰሎንቄ ሰዎች 5፡17-18
ሃዋሪያው ጳውሎስ አንድ ቀን ከመራብ ከመጠማት ከመራቆት ከመንከራተት እናመልጣለን ብሎ ጠብቆ እንደነበር እስከ አሁን እንራባለን እስከዚህ ሰዓት እንራባለን፥ እንጠማለን፥ እንራቆታለን፥ እንጐሰማለን፥ እንንከራተታለን የሚለው ንግግሩ ይመሰክራል፡፡
እስከዚህ ሰዓት ድረስ እንራባለን፥ እንጠማለን፥ እንራቆታለን፥ እንጐሰማለን፥ እንንከራተታለን፥ 1 ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 411 
እግዚአብሄርን አምልከን አምልከን አምልከን አንድ ተጨማሪ አምልኮ ለማምለክ ይታክተናል፡፡ ለእኛ ግን በዚህ ከተማ የለንም ወደእውነተኛ አገራችን እስክንሄድ እግዚአብሄርን በሁለንተናችን እናመልካለን፡፡
እንግዲህ ዘወትር ለእግዚአብሔር የምስጋናን መሥዋዕት፥ ማለት ለስሙ የሚመሰክሩ የከንፈሮችን ፍሬ፥ በእርሱ እናቅርብለት። ወደ ዕብራውያን 13፡15
የእምነት አርምጃን ተራምደን ተራምደን ተራምደን ጉልበት ያጥረናል፡፡
እግዚአብሄር ግን የሚፈልገው በእምነት እንድንጸፀና ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ፈቃድ ማድረጋችን በማድረግም መፅናታችን ለክንውን ያደርሰናል፡፡
የእግዚአብሔርን ፈቃድ አድርጋችሁ የተሰጣችሁን የተስፋ ቃል እንድታገኙ መጽናት ያስፈልጋችኋልና። ወደ ዕብራውያን 10፡36
በክርስቶስ ፍሬ የምናፈራው ባለማቋረጥ በመቀጠል በመኖር ነው፡፡
በእኔ ኑሩ እኔም በእናንተ። ቅርንጫፍ በወይኑ ግንድ ባይኖር ከራሱ ፍሬ ሊያፈራ እንዳይቻለው፥ እንዲሁ እናንተ ደግሞ በእኔ ባትኖሩ አትችሉም። የዮሐንስ ወንጌል 15፡4
ነገር ግን ውጤት የሚያመጣው የእግዚአብሄር ቃል በማድረግ መፅናታችን ነው፡፡ ውጤት የሚመጣው ባለማቆማችን ነው፡፡ ውጤት የሚመጣው በመግፋታችን ነው፡፡ ውጤት የሚመጣው በመፅናታችን ነው፡፡
ቃሉን የምንታዘዘው አእምሮዋችንን ሁሉ ፀጥ አሰኝተን ነው፡፡ ቃሉን የምንታዘዘው ልምዳችንን ሳንሰማ እና ሳንከተል ነው፡፡ ቃሉን የምንታዘዘው የሁኔታዎችን ሁሉ ጩኸት ባለመስማት ነው፡፡
ስምዖንም መልሶ፦ አቤቱ፥ ሌሊቱን ሁሉ አድረን ስንደክም ምንም አልያዝንም፤ ነገር ግን በቃልህ መረቦቹን እጥላለሁ አለው። የሉቃስ ወንጌል 5፡5
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ፍሬያማነት #ፍሬ #ማፍራት #ስኬት #በእኔኑሩ #መቀጠል #መፅናት #ቃል #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #መመዘኛ #መስፈርት #ፅናት #ትግስት #መኖር

No comments:

Post a Comment