Popular Posts

Thursday, June 7, 2018

ራሳችንን ብንመረምር ግን ባልተፈረደብንም ነበር

ራሳችንን ብንመረምር ግን ባልተፈረደብንም ነበር፤ 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 11፡31
በሌላ ሰው እጅ ከመውደቅ ይልቅ ቀላሉ በራስ እጅ መውደቅ ነው፡፡ በሌላ ሰው ከመፈረድ የሚቀለው ራስ ላይ መፍረድ ነው፡፡ ሌላ ሰው ከሚቀጣን ራሳችንን መቅጣት ይቀላል፡፡
እግዚአብሄር የመርህ አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሄር አብሮ የማይኖራቸው ነገሮች አሉ፡፡ ክፋት መፈረዱ አይቀርም፡፡ ትእቢት መዋረዱ አይቀርም፡፡ ትእቢት መዋረዱ የጊዜ ጉዳይ ብቻ ነው፡፡ ክፋት መፈረዱ የጊዜ ጉዳይ እንጂ የማይቀር ነው፡፡
የማይገለጥ የተሰወረ የለምና፥ የማይታወቅም ወደ ግልጥም የማይመጣ የተሸሸገ የለም። የሉቃስ ወንጌል 8፡17
ሰው በእግዚአብሄር እንዳይጣል ስጋውን መጎሸም አለበት፡፡ ሃዋሪያው በእግዚአብሄር ከሚፈረድበት ይልቅ ራሱ ስጋው ላይ መፍረድን መርጧል፡፡
ነገር ግን ለሌሎች ከሰበክሁ በኋላ ራሴ የተጣልሁ እንዳልሆን ሥጋዬን እየጎሰምሁ አስገዛዋለሁ። 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 9፡27
በተለይ ደግሞ እግዚአብሄር እጅ ከመውደቅ እና በእግዚአብሄር ከመዋረድ ራስን ማዋረድ ይሻላል፡፡
እንግዲህ በጊዜው ከፍ እንዲያደርጋችሁ ከኃይለኛው ከእግዚአብሔር እጅ በታች ራሳችሁን አዋርዱ፤ 1ኛ የጴጥሮስ መልእክት 5፡6
በሌላ ሰው ከማዋረድ ራስን ማዋረድ ይቀላል፡፡ በሌላ ሰው ከመጋፈጥ ራስን መጋፈጥ ይቀላል፡፡ በሌላ ሰው ከመፈተሽ ራስን መፈተሽ ይቀላል፡፡ ሌላ ሰው ከሚያየን ራሳችንን ማየት ይሻላል፡፡ ሌላ ሰው ከሚገዳደረን ራሳችንን መገዳደር ይሻላል፡፡
ስለዚህ ነው ኢየሱስ ፈጥነህ ተስማማ እያለ የሚያስተምረው፡፡
አብረኸው በመንገድ ሳለህ ከባላጋራህ ጋር ፈጥነህ ተስማማ፤ ባላጋራ ለዳኛ እንዳይሰጥህ ዳኛም ለሎሌው፥ ወደ ወህኒም ትጣላለህ፤
አብረኸው በመንገድ ሳለህ ከባላጋራህ ጋር ፈጥነህ ተስማማ፤ ባላጋራ ለዳኛ እንዳይሰጥህ ዳኛም ለሎሌው፥ ወደ ወህኒም ትጣላለህ፤ እውነት እልሃለሁ፥ የመጨረሻዋን ሳንቲም እስክትከፍል ድረስ ከቶ ከዚያ አትወጣም። የማቴዎስ ወንጌል 5፡25-26
ራስን መርምሮ በድብቅ ራስን ማስተካከል የመሰለ ነገር የለም፡፡ ልብን መርምሮ ንስሃ መግባትን የመሰለ ነገር ጣፋጭ ነገር የለም፡፡ ራስን ማዋረድን የመሰለ ፍሬያማነት የለም፡፡
ራሳችንን ካላዋረድን የምንዋረድበት መድረኩ እየሰፋ ነው የሚሄደው ፡፡ ራሳችንን ካላዋረድን የምንዋረድበት መዋረድ እየከፋና እየመረረ ነው የሚሄደው፡፡
ወንድምህም ቢበድልህ፥ ሄደህ አንተና እርሱ ብቻችሁን ሆናችሁ ውቀሰው። ቢሰማህ፥ ወንድምህን ገንዘብ አደረግኸው፤ ባይሰማህ ግን፥ በሁለት ወይም በሦስት ምስክር አፍ ነገር ሁሉ እንዲጸና፥ ዳግመኛ አንድ ወይም ሁለት ከአንተ ጋር ውሰድ፤ እነርሱንም ባይሰማ፥ ለቤተ ክርስቲያን ንገራት፤ ደግሞም ቤተ ክርስቲያንን ባይሰማት፥ እንደ አረመኔና እንደ ቀራጭ ይሁንልህ። የማቴዎስ ወንጌል 18፡15-17
በድብቅ ራሳችንን መርምረን ካልተመለስን በወንድማችን ፊት መዋረድ ይሻላል፡፡ ወንድማችን ፊት ካልተዋረድን በሁለት ወይም በሶስት ምስክር ፊት እንዋረድ፡፡ እምቢ ካልን ግን በቤተክርስትያን ፊት እንዋረዳለን፡፡ በቤተክርስትያን ፊት ካልተዋረድን ደግሞ እንደ አረመኔና እንደ ቀራጭ በመሆን እንዋረዳለን፡፡
ከዚህ ሁሉ የሚቀለው የውርደታችንን አድማስ የሚያጠበው ራሳችንን ማዋረድ ነው፡፡ በራሳችን ፊት ለመዋረድ ከፈቀድን ፍሬያችን እየበዛ ይሄዳል፡፡ በራሳችን ፊት ለመዋረድ ግልፅ ከሆንንና ጊዜ ከሰጠን ለእግዚአብሄር የምንጠቅም የክብር እቃዎች እንሆናለን፡፡  
ራሳችንን ማታለል የለብንም፡፡ ለራሳችን ታማኝ ከሆንን ራሳችንን ስራችንን እናውቀዋለን፡፡ ለራሳችን ታማኝ ከሆንን ስራችንን እንደ እግዚአብሄር ቃል እንመዝነዋለን፡፡ ለራሳችን ታማኝና ግልፅ ከሆንን ያደረግነውን ነገር ያደረግነው በምን መነሻ ሃሳብ /motive/ ሞቲቭ መሆኑን እናውቀዋለን፡፡
አንዱ ምንም ሳይሆን ምንም የሆነ ቢመስለው ራሱን ያታልላልና። ነገር ግን እያንዳንዱ የገዛ ራሱን ሥራ ይፈትን፥ ከዚያም በኋላ ስለ ሌላው ሰው ያልሆነ ስለ ራሱ ብቻ የሚመካበትን ያገኛል፤ ወደ ገላትያ ሰዎች 6፡3-4
ከሰው ፊት ከዋረድ ሁሉ ደግሞ የከፋው በእግዚአብሄር መዋረድ ነው፡፡ በሰው ከመፈረድ የከፋው በእግዚአብሄር መፈረድ ነው፡፡
በቀል የእኔ ነው፥ እኔ ብድራትን እመልሳለሁ ያለውን እናውቃለንና፤ ደግሞም፦ ጌታ በሕዝቡ ይፈርዳል። በሕያው እግዚአብሔር እጅ መውደቅ የሚያስፈራ ነው። ወደ ዕብራውያን 10፡30-31
ራሳችንን ብንመረምር ግን ባልተፈረደብንም ነበር፤ 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 11፡31
ፀሎት
እግዚአብሄር ሆይ ስላስተማርክኝ ትምህርት አመሰግንሃለሁ፡፡ እግዚአብሄር ሆይ ለአንተ ብቻ መኖር እፈልጋለሁ፡፡ እግዚአብሄር ሆይ ራስን የመመርምር እና የመመለስ የሰጠኸኝን እድል መጠቀም እፈልጋለሁ፡፡ እግዚአብሄር ሆይ ሰው እኔን ከማዋረዱ በፊት የውርደቴ አድማሱ ከመስፋቱ በፊት ራሴን ለማዋረድ ራሴን ለመመርመር ጊዜ እሰጣለሁ፡፡ እግዚአብሄር ሆይ ራሴን ለመመርመር ታማኝ እሆናለሁ፡፡ ከሁሉም በላይ በአንተ ከመዋረድ አስቀድሜ ራሴን አዋርዳለሁ፡፡ እግዚአብሄር ሆይ ራሴን ለመመርመር ስለሰጠኸኝ እድል አመሰግንሃለሁ፡፡ በኢየሱስ ስም፡፡ አሜን፡፡
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ህይወት #የሚፈርድ #የሚያማ #ወንጌል #መውደድ #ፍቅር #የህይወትምስክርነት #ራስንማዋረድ #ራስንመመርመር #መውደድ #እውነት #ትህትና #ትንሳኤ #ህይወት #ወንጌል #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ  #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ  

No comments:

Post a Comment