Popular Posts

Friday, July 20, 2018

የፍቅር ችግር የእግዚአብሄር ችግር ነው

እግዚአብሄር ፍቅር ነው፡፡ እግዚአብሄር ሰውን የፈጠረው በመልኩና በአምሳሉ ነው፡፡ ሰው የተፈጠረው በእግዚአብሄር ፍቅር እንዲኖር ነው፡፡ ሰው የተፈጠረው እግዚአብሄርን በመውደድ ከእርሱ ጋር ህብረት እንዲያደርግና እንዲታዘዘውና ነው፡፡ እግዚአብሄር ሰውን የፈጠረው ፍቅር እንዲሰጥና ፍቅር እንዲቀበል ነው፡፡ ሰው የተፈጠረው በፍቅር ለፍቅር ነው፡፡
ሰው በሃጢያት ምክንያት ከእግዚአብሄር ክብር ሲወድቅ ፍቅሩን አጣ፡፡ ሰው ለእግዚአብሄር ያለውን ፍቅር በአመፃ ምክንያት አጣው፡፡ ሰው ከእግዚአብሄር ጋር ጠላት ሆነ፡፡
ጠላቶች ሳለን ከእግዚአብሔር ጋር በልጁ ሞት ከታረቅን፥ ይልቁንም ከታረቅን በኋላ በሕይወቱ እንድናለን፤ ወደ ሮሜ ሰዎች 5፡10
ሰው እግዚአብሄርን መውደድ አቃተው፡፡ ሰው ከእግዚአብሄር ጋር ያለው የፍቅር ግንኙነት ሲበላሽ ከራሱ ጋር ያለው የፍቅር ግንኙነት ተበላሸ፡፡ ሰው ራሱን እንደሚገባ መውደድና ማክበር አቃተው፡፡
ሰው ከእግዚአብሄር ጋር ያለው የፍቅር ግንኙነት ሲበላሽና የእግዚአብሄርን ፍቅር መቀበል ሲያቅተው ሰው ራሱን ብቻ ሳይሆን ሰውን መውደድ አቃተው፡፡
ሰው ለፍቅር ስለተፈጠረ የእግዚአብሄን ፍቅር ስላጣው ለእግዚአብሄር የነበረውን ፍቅር ለሌላ ነገር ለወጠው፡፡ እግዚአብሄርን እና ሰውን ከመውደድ ይልቅ ሰው መወደድ የማይገባቸውን ገንዘንብንና ቁሳቁስን መውደድ ጀመረ፡፡ ሰው እግዚአብሄርንና ገንዘብን መውደድ አይችልም፡፡ እግዚአብሄር ከገንዘብ እኵልለ እንዲወደድ አይፈልግም፡፡ ሰው ሰውንም ገንዘብንም መውደድ አይችልም፡፡ ሰው ገንዘብን ከወደድ እግዚአብሄርን ይጠላል ሰው ገንዘብን ከወደደ ሰውን ይንቃል፡፡
ለሁለት ጌቶች መገዛት የሚቻለው ማንም የለም፤ ወይም አንዱን ይጠላል ሁለተኛውንም ይወዳል፤ ወይም ወደ አንዱ ይጠጋል ሁለተኛውንም ይንቃል፤ ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አትችሉም። የማቴዎስ ወንጌል 6፡24
የሰው የፍቅር ችግር የጀመረው ከሰው አይደለም፡፡ የሰው የፍቅር ችግር የጀመረው ከእግዚአብሄር ነው፡፡ የሰው የፍቅር ግንኙነት ችግር የጀመረው ከእግዚአብሄር ጋር የነረው የፍቅር ግንኙነት በሃጢያት ምክንያት ሲበላሽ ነው፡፡
ሰው ከማይገባው ከእንግዳ ፍቅሮች እንዲድን ወደጥንቱ ወደ እግዚአብሄር ፍቅር መመለስ አለበት፡፡ የሰው የፍቅር ህይወቱ መታደስ ካለበት ከእግዚአብሄር ጋር ያለው የፍቅር ህይወቱ መታደስ አለበት፡፡
በተሰጠንም በመንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ፍቅር በልባችን ስለ ፈሰሰ ተስፋ አያሳፍርም። ወደ ሮሜ ሰዎች 5፡5
ሰው ፍቅር የሆነውን የእግዚአብሄርን ፍቅር እንዴት እንደሚቀበልና ለእግዚአብሄር ፍቅሩን እንዴት እንደሚሰጥ ካላወቀ ፍቅርን አያውቅም ማለት ነው፡፡ ሰው የእግዚአብሄርን ፍቅር መቀበልና እግዚአብሄርን መውደድ ሲጀምር ራሱንና ሰዎችን መውወድ ይጀምራል፡፡ ሰው የፍቅር ምንጭ የሆነውን እግዚአብሄርን ሲወድና የእግዚአብሄርን ፍቅር ሲቀበል ሰዎችን መውደድና ለሰዎች ፍቅርን መስጠት ያውቃል፡፡ ሰው ራሱንና ሌሎችችን ለመውደድ ጉልበት የሚሆነው በእግዚአብሄር መወደዱ ነው፡፡
እርሱ ስለ እኛ ነፍሱን አሳልፎ ሰጥቶአልና በዚህ ፍቅርን አውቀናል፤ እኛም ስለ ወንድሞቻችን ነፍሳችንን አሳልፈን እንድንሰጥ ይገባናል። 1ኛ የዮሐንስ መልእክት 3፡16
የእግዚአብሄርን ፍቅር ክብር የተረዳ ሰው ሌሎችን ለመውደድ ሃይልና ምሳሌ ያገኛል፡፡ የእግዚአብሄርን ፍቅር ካልተቀበለ ሰው ፍቅርን መጠበቅ ከንቱ ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ፍቅር በተረዳንና በተቀበልን መጠን ብቻ ሌሎችን መውደድ እንችላለን፡፡
የእግዚአብሔር ልጆች ተብለን ልንጠራ አብ እንዴት ያለውን ፍቅር እንደ ሰጠን እዩ፥ እንዲሁም ነን። 1 የዮሐንስ መልእክት 3፡1
የሰው የፍቅር ህይወት ችግር ወደኋላ ተመልሶ ቢፈተሽ የሚደረሰው ወደ እግዚአብሄር ጋር ወደአለ የፍቅር ችግር ነው፡፡ የምንም የፍቅር ችግር መንስኤው ከእግዚአብሄር ጋር ያለ የፍቅር ችግር ነው፡፡
ዓለም ቢጠላችሁ ከእናንተ በፊት እኔን እንደ ጠላኝ እወቁ። የዮሐንስ ወንጌል 15፡18
ማንኛውም ፍቅርን የመስጠትና ፍቅርን የመቀበል ችግር የሚመነጨው የእግዚአብሄርን ፍቅር ከመቀበልና እግዚአብሄርን ከመውደድ ችግር ነው፡፡
እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ፥ እንደ ወደድኋችሁ እናንተ ደግሞ እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ አዲስ ትእዛዝ እሰጣችኋለሁ። የዮሐንስ ወንጌል 13፡34
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ፍቅር #መውደድ #መወደድ #ማስተዋል #እግዚአብሔርንመፍራት #ጥበብ #ክፉ #መልካም #ፍርድ #እውቅና #ፍፁም #ችግር #መፍትሄ #አላማ #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ  #እምነት #ቃል  #ማደስ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment