Popular Posts

Sunday, July 8, 2018

የልብ ሽምግልና

ኢያሱም ሸመገለ በዕድሜም አረጀ እግዚአብሔርም አለው፦ አንተ ሸመገልህ፥ በዕድሜህም አረጀህ፤ ያልተወረሰች እጅግ ብዙ ምድር ገና ቀርታለች፤ ኢያሱ 13፡1
መጀመሪያ ለእግዚአብሄ ሩጥንም አንጠግብም፡፡ ለእግዚአብሄር ሰጥተን አንረካም፡፡ ቀስ በቀስ ግን የልብ ሽምግልና እየያዘን ይመጣል፡፡ የልብ ሽምግልና እግዚአብሄር ያዘጋጀልን ርስት ውስጥ እንዳንገባ የሚያግደን ትልቅ እንቅፋት ነው፡፡ የእድሜ ሽምግልና በፅድቅ መንገድ የሚገኝ እግዚአብሄር የምናመሰግንበት በረከት ነው፡፡
የሸበተ ጠጕር የክብር ዘውድ ነው፥ እርሱም በጽድቅ መንገድ ይገኛል። ምሳሌ 16፡31
የጎበዛዝት ክብር ጕልበታቸው ናት፥ የሽማግሌዎችም ጌጥ ሽበት ነው። ምሳሌ 20፡29
የእድሜ መጨመር ሽምግልናን ሳይሆን የልብ ሽምግልና በቀጣይነት ልንዋጋው የሚገባ የርስታችን ጠላት ነው፡፡
እስኪ ከመኝሃፍ ቅዱስ ልቡ ያልሸመገለን ሰው እንመልከት፡፡
አሁንም፥ እነሆ፥ እግዚአብሔር ለሙሴ ይህን ቃል ከተናገረ በኋላ፥ እስራኤል በምድረ በዳ ሲዞሩ፥ እርሱ እንደ ተናገረኝ እግዚአብሔር እነዚህን አርባ አምስት ዓመት በሕይወት አኖረኝ፤ አሁንም፥ እነሆ፥ ለእኔ ዛሬ ሰማንያ አምስት ዓመት ሆነኝ። ሙሴም በላከኝ ጊዜ እንደ ነበርሁ፥ ዛሬ ጕልበታም ነኝ፤ ጕልበቴም በዚያን ጊዜ እንደ ነበረ፥ እንዲሁ ዛሬ ለመዋጋት ለመውጣትም ለመግባትም ጉልበቴ ያው ነው። መጽሐፈ ኢያሱ ወልደ ነዌ 14፡10-11
እግዚአብሄር ብዙ ምድሮች አዘጋጅቶልን ሳለና የምንወርስበት ጉልበት እያለን ሃሞታችን የሚፈስበት የተለያዩ ምክንያቶች አሉ፡፡ ልባችንን የሚያሸመግሉትን ምክንያቶች ከተከታልን ለልብ ሽምግልና ቦታ ሳንሰጥ በሙላት እግዚአብሄርን በዘመናችን አገልግለን ማለፍ እንቻለን፡፡
ልባችን የልብ ሽምግልና የሚመጣባቸው በተለያዩ ምክኒያቶች ይመጣል፡፡
የህይወት ውድቀት ሲያጋጥመን
አንድ ጊዜ ከወደቅን መልሰን ለመሞከር ቅናታችን ይመታል፡፡ ነገር ግን ውድቀት የማይሰራበትን መንገድ የተማርነበት የትምህርት እንጂ መጨረሻችን እንዳይደለ ማወቅ ከልብ ሽምግልና ያድነናል፡፡  
ወንድሞች ሆይ፥ እኔ ገና እንዳልያዝሁት እቈጥራለሁ፤ ነገር ግን አንድ ነገር አደርጋለሁ፤ በኋላዬ ያለውን እየረሳሁ በፊቴ ያለውን ለመያዝ እዘረጋለሁ፥ ፊልጵስዩስ 3፡13
ለእግዚአብሄር ብዙ የሰራን ሲመስለን
ለእግዚአብሄር ብዙ የሰራን ሲመስለንና በቀድሞው ግኝታችን አለመጠን ከተኩራራን ልባችን ቀድሞ ያረጃል፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር እንድንወርስ ያዘጋጀልንን ሁሉ ከመውረሳችን በፊት አናረጅም፡፡ እግዚአብሄር የሚወረስ አለ እስካለ ድረስ አናቆምም፡፡ እግዚአብሄር ያየልኝን ሳልወርስ አይበቃም ካልና ለተጨማሪ ድሎች ከተራብን የልብን ሽምግልና በመዋጋት እግዚአብሄር እንድንወርስ ያዘጋጀልንን ሁሉ ወርሰን እናልፋለን፡፡  
እርሱም አንድ ቀን የሚያህል መንገድ በምድረ በዳ ሄደ፤ መጥቶም ከክትክታ ዛፍ በታች ተቀመጠና፦ ይበቃኛል አሁንም፥ አቤቱ፥ እኔ ከአባቶቼ አልበልጥምና ነፍሴን ውሰድ ብሎ እንዲሞት ለመነ። መጽሐፈ ነገሥት ቀዳማዊ 19፡4
አሁን ደግሞ ለራሳችን መስራት ሲያምረን
ለጌታ እንሮጥና አሁን ደግሞ ለራሴ ልስራ ለራሴ አንድ ነገር ልያዝ ስንል ከእግዚአብሄር ስራ ልባችን ያረጃል፡፡ እኛ የጌታ ነን፡፡ ለጌታ የምንሰራበትና ለራሳችን የምንሰራበት ጊዜ የለም፡፡ ሁልጊዜ ለጌታ አንሰራለን፡፡ ሁልጊዜ እርሱ ለእኛ ይሰራል፡፡
ነገር ግን አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፥ ይህም ሁሉ ይጨመርላችኋል። የማቴዎስ ወንጌል 6፡33
እግዚአብሄር እስከ ሽበት እስከሽምግልና ይሸከመናል፡፡
የእግዚአብሄርን ስራ የምንሰራው እስክናረጅ አይደለም፡፡ እስክንሞት የጌታን ስራ እንሰራለን፡፡ ከእምነት ጡረታ አንወጣም፡፡ እንዲያውም የምንሞተው የጌታን ስራ በመስራት ላይ እያለን ነው፡፡
እስከ ሽምግልና ድረስ እኔ ነኝ፥ እስከ ሽበትም ድረስ እሸከማችኋለሁ፤ እኔ ሠርቻለሁ እኔም አነሣለሁ፤ እኔ እሸከማለሁ እኔም አድናለሁ። ትንቢተ ኢሳይያስ 464
እንግዲህ ታላቅ ብድራት ያለውን ድፍረታችሁን አትጣሉ። ወደ ዕብራውያን 10፡35
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #እሳት #ህብረት #ቃል #ሽበት #ሽምግልና #ድፍረት #መቀጣጠል #ክብር #አገልግሎት #መዋረድ #መርካት #ፀጋ #እውቀት #ኢየሱስንተመልክተን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ብፅእና #እምነት #ታላቅነት #ማገልገል #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment