Popular Posts

Wednesday, July 25, 2018

ሰውን ማስደሰት ይቻላል

ሰው የሚደሰትበት የተለያየ መንገድ አለ፡፡ ሰው ጥሩ ነገር ሲበላ ይደሰታል፡፡ ሰው ጥሩ ሲለብስ ደስ ይለዋል፡፡ ሰው ጥሩ መኪና ሲነዳ ደስ ይለዋል፡፡ ሰው ገንዘብ ከፍሎ አንድም የሚፈልገውን ነገር ማደረግ ሲችል ደስ ይለዋል፡፡
ሰውን ብዙ ነገሮች ያስደንቁታል፡፡ ሰው ያልጠበቅው መልካም ነገር ሲያገኝ ይደነቃል፡፡ ሰው የማይችለውን ነገር ሲችል ይደነቃል፡፡
እግዚአብሄርን የሚያስደንቀው ሰውን የሚያስደንቁ ነገሮች ሁሉ አይደሉም፡፡ ሰውን የሚያስደንቀው እግዚአብሄርን የማያስደንቀው ብዙ ነገር አለ፡፡
1.      እግዚአብሄር በገንዘባችን አይደነቅም
እግዚአብሄር የሰው ገንዘብ አያስደንቀውም፡፡ የማንም ቢሊየነር ሃብት እግዚአብሄርን አያስደንቀውም፡፡
የምድረ በዳ አራዊት ሁሉ በሺህ ተራራዎች ያሉ እንስሶችም የእኔ ናቸውና። መዝሙረ ዳዊት 50፡10
2.     እግዚአብሄር በውበታችን አይደነቅም
የፈጠረን እግዚአብሄር ነው፡፡ ውበትን ስናይ የምንደነቀው እኛ ነን፡፡ እግዚአብሄር ውበታችንን አይቶ ይገርማል ውበቱ አይልም፡፡ እግዚአብሄር ውበታችንን አያይም፡፡ የመንፈስ እንጂ የስጋ ውበታችን ለእግዚአብሄር አይታየውም፡፡
ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት ዋጋው እጅግ የከበረ የዋህና ዝግተኛ መንፈስ ያለውን የማይጠፋውን ልብስ ለብሶ የተሰወረ የልብ ሰው ይሁንላችሁ። 1 የጴጥሮስ መልእክት 3፡4
3.     እግዚአብሄር በዝናችን አይደነቅም
እኛ እንደሰው ዝነኛ የሆነ ሰው ጋር ስንቀርብ እንለያለን፡፡ ሰው ዝነኛ ሰው ጋር ሲቀርብ ፈጥኖ ለማስታወሻ የሚሆን ፊርማ ያስፈርማል፡፡ ሰው ዝነኛ ሰው ጋር በአጋጣሚ ከተገናኘ አብሮ ፎቶ ለመነሳት ይቸኩላል፡፡ እግዚአብሄር ይሄስ ዝነኛ ነው ብሎ ሁለተኛ ዞር ብሎ አያየውም፡፡ እግዚአብሄር ዝናችን አይገርመውም፡፡  
4.     እግዚአብሄር በጥበባችን አይደነቅም
ማስተዋሉ የማይመረመር እግዚአብሄር ጥበበኛ ሰው አያስደንቀው፡፡ እንደሰው አዋቂ የሆነ ሰው ጋር ስንቀርብ የምንናገረውን ነገር ይበልጥ እንጠነቀቃለን፡፡ እንደ ሰው በሰው ጥበብ እንደነቃለን፡፡ ሰው ጥበበኛ ሰው ጋር ሲቀርብ ያለውን ጥበብ እንዲኖረው ይመኛል፡፡ እግዚአብሄር ግን ማንም ጥበበኛ ሰው በጥበቡ አያስደንቀውም፡፡
የዚህች ዓለም ጥበብ በእግዚአብሔር ፊት ሞኝነት ነውና። እርሱ ጥበበኞችን በተንኰላቸው የሚይዝ፤ ደግሞም፦ ጌታ የጥበበኞችን አሳብ ከንቱ እንደ ሆነ ያውቃል ተብሎ ተጽፎአልና። 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 3፡19-20
5.     እግዚአብሄር በሃይላችን አይደነቅም
እግዚአብሄር ሃያል ነው ማንንም አይንቅም፡፡ እግዚአብሄር ልናቅ ቢል ደግሞ የሚተርፈው ማንም ሰው አይኖርም፡፡ እግዚአብሄር የአሜሪካንን ፕሬዝዳንት አይቶ "ውይ ይሄን መናቅ እንዴት ይሆንልኛል?" አይልም፡፡ እግዚአብሄር አይንቅም እንጂ ቢንቅ ማንም አይተርፈውም፡፡ ስለዚህ እግዚአብሄር ማንንም አይንቅም፡፡
እነሆ፥ እግዚአብሔር ኃያል ነው፥ ማንንም አይንቅም እርሱም በማስተዋል ብርታት ኃያል ነው። መጽሐፈ ኢዮብ 36፡5
እግዚአብሄር በእነዚህ ነገሮች አይደነቅም እንጂ እግዚአብሄር ከነጭራሹ አይደነቅም ማለት አይደለም፡፡ እግዚአብሄር ይደነቃል፡፡ ሰዎችን ብዙ የሚያስደንቃቸው ነገሮች እግዚአብሄርን ላያስደንቁት ይችላሉ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር ይደነቃል፡፡ ሰዎችን የሚያስደስቱዋቸው ነገሮች ሁሉ እግዚአብሄርን ላያስደስተው ይችላል፡ሸ ነግር ግን እግዚአብሄር ይደሰታል፡፡ እግዚአብሄ የሚደሰትበት ነገር አለ፡፡
እግዚአብሄርን የሚያስደንቀው ነገር የሰው እምነት ነው፡፡ እግዚአብሄር የሚደሰተው በእምነት ነው፡፡ እንዲያውም ካለእምነት እግዚአብሄን ደስ ማሰኘት አይቻለም፡፡
ለእግዚአብሄር ገንዘባችንን ከምናሳየው ይልቅ ምንም ገንዘብ ሳይኖረን እምነታችንን ብናሳየው ይበልጥ ይደሰታል፡፡
በውበታችን ከምንመካ ይልቅ በእግዚአብሄር ሞገስ ስንመካ እግዚአብሄርን እናድስደስተዋለን፡፡
በዝናችን ደስ ከሚለን ይልቅ በእግዚአብሄር ደስ ሲለን እግዚአብሄር ይይካብናል፡፡
በጥበባችን ከምንደገፍ ይልቅ በእርሱ ብንገደፍ እግዚአብሄርን እናስደስተዋለን፡፡
በሃይላችን ከምንታመን ይልቅ በእርሱ በእግዚአብሄ ብንታመን አግዚአብሄርን እናስደስተዋለን፡፡  
እግዚአብሄር ይደነቃል፡፡ ሰውን ብዙ ነገሮች ሊያስደንቁት ይችላሉ፡፡ ሰውን የሚያስደንቁት ነገሮች ሁሉ እግዚአብሄርን ላያስደንቁይት ይችላሉ፡፡ በተለይ ካለእምነት እግዚአብሄርን ማስደሰት አይቻልም፡፡ ምንም ሰዎች እንዲኖራቸው የሚፈልጉትን ነገር ሁሉ ቢኖረን እምነት ግን ከሌለን እግዚአብሄርን አናስደስተውም፡፡ በተቃራኒ ሰዎች በምድር ላይ የሚፈልጉዋቸው ነገሮች ሁሉ ቢጎድለን ነገር ግን እምነት ካለን እግዚአብሄርን በሚገባ እናስደስተዋለን፡፡
እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ጠቢብ በጥበቡ አይመካ፥ ኃያልም በኃይሉ አይመካ፥ ባለ ጠጋም በብልጥግናው አይመካ፤ ነገር ግን የሚመካው፦ ምሕረትንና ፍርድን ጽድቅንም በምድር ላይ የማደርግ እኔ እግዚአብሔር መሆኔን በማወቁና በማስተዋሉ በዚህ ይመካ፤ ደስ የሚያሰኙኝ እነዚህ ናቸውና፥ ይላል እግዚአብሔር፡፡ ትንቢተ ኤርምያስ 9፡23-24
ያለ እምነትም ደስ ማሰኘት አይቻልም፤ ወደ እግዚአብሔር የሚደርስ እግዚአብሔር እንዳለ ለሚፈልጉትም ዋጋ እንዲሰጥ ያምን ዘንድ ያስፈልገዋልና። ወደ ዕብራውያን 11፡6
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #እምነት #ልብ #ማመን #ቃል #መናገር #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ማሰላሰል #ማድረግ #ሁሉይቻላል #ደስታ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #መናገር #ፅናት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment