Popular Posts

Monday, July 30, 2018

የትዳር ችግር የእግዚአብሄር ችግር ነው

የህይወትና የአገልግሎት ችግሮች ሁሉ የሚመነጩት ከእግዚአብሄር ችግር ነው፡፡ ሰው የተፈጠረው ከእግዚአብሄር ጋር መልካም ግንኙነት እንዲኖረው በእግዚአብሄር መልክና አምሳል ነው፡፡ ሰው ሲፈጠር ከእግዚአበሄር ጋር የነበረው ግንኙነት ፍፁም ነበር፡፡ ሰው ሃጢያትን ሲሰራ ከእግዚአብሄር ጋር ያለው ግንኙነት በመበላሸቱ ሰው ከሰው ጋር ያለው ግንኙነት ተበላሸ፡፡
የሰው ችግር የጀመረው ከእግዚአብሄር ነው፡፡ ሰው ከእግዚአብሄር ጋር ያለው ግንኙነት መልካም እከነበረ ድረስ የሰው ግንኙነቶች ሁሉ መልካምና የተሳኩ ነበሩ፡፡ ሰው ከእግዚአብሄር ጋር ያለው ግንኙነት ከተበላሸ በኋላ ከማንም ከጋር ያለው ግንኙነት ሊስተካከል አልቻለም፡፡
አሁንም የሰው ግንኙነት መስተካካል ካለበት የሚጀመረው ከእግዚአብሄር ጋር ባለው ግንኙነት ነው፡፡ ሰው ከእግዚአብሄር ጋር ያለው ግንኘኙነት የሁሉም ግንኙነቶች መሰረት ነው፡፡ ሰው ከእግዚአብሄር ጋር ያለው ግንኙነት ሳይሳካ ከሰው ጋር ያለው ግንኙነት ይሳካል ማለት ዘበት ነው፡፡
የሰው የግንኙነት ችግር ምንጩ የሰው ከእግዚአብሄር ጋር ያለው ግንኙነት ችግር ነው፡፡ የሰው ከእግዚአብሄር ጋር ያለው ግንኙነት ችግር መፈታት የሰውን ማንኛውም የግንኙነት ችግሮች ይፈታል፡፡
የትዳር ችግር የእግዚአብሄር ችግር ነው፡፡
በትዳር ሚስት ለጌታ እንዴት እንደምትገዛ ካወቀች ለባልዋ እንዴት እንደምትገዛ ታውቃለች፡፡ ሚስት ለባልዋ የመገዛት ችግር ምንጩ የሚስት ለጌታ የመገዛት ችግር ነው፡፡  የሚስት ለጌታ የመገዛት ችግሯ መፍትሄ ሲያገኝ ሚስት ለባልዋ የመገዛት ችግሯ መፍትሄ ያገኛል፡፡ ሴት ለጌታ በመገዛት ከሰለጠነች ለባልዋ ለመገዛት አይቸግራትም፡፡ ሴት ለጌታ በመገዛት ምሳሌነት ለባልዋ መገዛት ትችላለች፡፡ ሴት ለጌታ በመገዛት ልምዷ ለባልዋ መገዛት ትችላለች፡፡
ለእያንዳንዳችሁ በክርስቶስ ፍርሃት የተገዛችሁ ሁኑ። ሚስቶች ሆይ፥ ለጌታ እንደምትገዙ ለባሎቻችሁ ተገዙ፤ ወደ ኤፌሶን ሰዎች 5፡21-22
ባል ሚስቱን የመውደድ ችግር የእግዚአብሄር ፍቅር ችግር ነው፡፡ ባል በእግዚአብሄር እንዴት እንደተወደደ ካላወቀ ሚስቱን እንዴት እንደሚወድ አያውቅም፡፡ ባል በእግዚአብሄር በመወደድ ልምዱ ሚስቱን ሊወድ ይችላል፡፡ ባል ከእግዚአብሄር ጋር ባሳለፈው የመውደድና የመወደድ ምሳሌነት ሚስቱን መውደድ ይችላል፡፡ ባል በጌታ እንዴት እንደተወደደ ሲረዳ ሚስቱን እንዴት እንደሚወድ ያውቃል፡፡ ባል በእግዚአብሄር በተወደደበት ፍቅር ጉልበት ሚስቱን ይወዳል፡፡
ባሎች ሆይ፥ ክርስቶስ ደግሞ ቤተ ክርስቲያንን እንደ ወደዳት ሚስቶቻችሁን ውደዱ፤ በውኃ መታጠብና ከቃሉ ጋር አንጽቶ እንዲቀድሳት ስለ እርስዋ ራሱን አሳልፎ ሰጠ፤ ወደ ኤፌሶን ሰዎች 5፡25-26
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ህይወት #ጋብቻ #ትዳር #ባል #ሚስት #ፍቅር #መውደድ #መታዘዝ #ይተዋል #ይጣበቃል #አንድስጋ #እውነት #ትህትና #ትንሳኤ #ህይወት #ወንጌል #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ  #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ  

No comments:

Post a Comment