Popular Posts

Friday, July 20, 2018

የእውቀት ችግር የእግዚአብሔር ችግር ነው

ሰው እውቀት ያስፈልገዋል፡፡ መፅሃፍ ቅዱስ ነፍስ ያለእውቀት ትሆን ዘንድ መልካም አይደለም ይላል፡፡ ሰው እውቀት ከጎደለውቅ ሁሉ ነገር ይጎድለዋል፡፡
ነፍስ እውቀት የሌለባት ትሆን ዘንድ መልካም አይደለም፤ እግሩንም የሚያፈጥን ከመንገድ ይስታል። መጽሐፈ ምሳሌ 19፡2
ሰው በእግዚአብሄር የተፈጠረው በእግዚአብሄር መልክና አምሳል ነው፡፡ ሰው የተፈጠረው ከሚያስፈልገው ከሙሉ እውቀት ጋር ነው፡፡ ሰው ለኑሮ የሚያስፈልገው እውቀት ሁሉ ነበረው፡፡ ሰው እግዚአብሄርን በሚገባ ያውቀው ነበር፡፡ ሰው ስለ እግዚአብሄር የሚያስፈልገው እውቀት ሁሉ ነበረው፡፡
ሰው በሰይጣን ማታለል ምክንያት የማያስፈልገውን እውቀት ሲፈልግል ለኑሮና ለስኬት የሚያስፈልገውን ዋናውን እውቀት አጣው፡፡ ሰው የእግዚአብሄርን እውቀት ሲያጣው ስለሌላ ስለሁሉም ነገሮች ያሉት እውቀቶች ሁሉ ተዛቡበት፡፡ ሰው ስለ እግዚአብሄር ያለውን ትክክለኛውን እውቀት ሲያጣው ስለራሱ ያለውን ትክክለኛ እውቀት አጣው፡፡ ሰው ስለ እግዚአብሄር ያለውን ትክክለኛ እውቀት ሲያጣው በእግዚአብሄር መልክና አምሳል ስለተፈጠረው ሰው ትክክለኛውንና ንፁህን እውቀት አጣው፡፡
ነገር ግን እባብ በተንኮሉ ሔዋንን እንዳሳታት፥ አሳባችሁ ተበላሽቶ ለክርስቶስ ከሚሆን ቅንነትና ንጽሕና ምናልባት እንዳይለወጥ ብዬ እፈራለሁ። 2 ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 11፡3
የሰው የእውቀት ችግር የተጀመረው ከእግዚአብሄር ነው፡፡ ሰው ለእግዚአብሄር ያለው እውቀት ሲዛባ ሌላ ሁሉ እውቀቱ ተዛባ፡፡
ሰው እውቀት ካስፈለገው መጀመሪያ ማወቅ ያለበት የእግዚአብሄርን እውቀት ነው፡፡ ሰው ወደ እውቀት ከተመለሰ መመለስ ያለበት ወደ እግዚአብሄር እውቀት ነው፡፡ ሰው እውቀት ካስፈለገው እውቀትን መጀመር ያለበት እንዴት ከእግዚአብሄር ጋር እንደሚኖር በማወቅ ነው፡፡
ሰው እውቀት አለኝ የሚለው መጀመሪያ ከፈጠረው ከእግዚአብሄር ጋር እንዴት እንደሚኖር በማወቅ ነው፡፡ ሰው እውቀት አለኝ ማለት የሚችለው ለእግዚአብሄር አምላክነት እውቅና በመስጠት ነው፡፡ ሰው እውቀት አለኝ ማለት የሚችለው እግዚአብሄርን በመፍራት ነው፡፡
የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው፤ ሰነፎች ግን ጥበብንና ተግሣጽን ይንቃሉ። መጽሐፈ ምሳሌ 1፡7
የሰው እውነተኛ እውቀት የሚጀምረው በመልኩና በአምሳሉ የፈጠረውን እግዚአብሄርን እንደ አምላክነቱ አውቅና በመስጠት ነው፡፡
ስለዚህም እግዚአብሔርን እያወቁ እንደ እግዚአብሔርነቱ መጠን ስላላከበሩትና ስላላመሰገኑት የሚያመካኙት አጡ፤ ነገር ግን በአሳባቸው ከንቱ ሆኑ የማያስተውለውም ልባቸው ጨለመ። ወደ ሮሜ ሰዎች 1፡20-21
ሰው ከፈጣሪው ጋር እንደት በትህትና እንደሚሄድ ካላወቅ ሌላው እውቀቱ ሁሉ ከንቱ ነው፡
ሰው ሆይ፥ መልካሙን ነግሮሃል፤ እግዚአብሔርም ከአንተ ዘንድ የሚሻው ምንድር ነው? ፍርድን ታደርግ ዘንድ፥ ምሕረትንም ትወድድ ዘንድ፥ ከአምላክህም ጋር በትሕትና ትሄድ ዘንድ አይደለምን? ትንቢተ ሚክያስ 6፡8
ሰው ከእግዚአብሄር ጋር እንዴት እንደሚኖር ካላወቀ ሌላ እውቀትን መሰብሰብ ራስብን ማድከም ነው፡፡
ከዚህም ሁሉ በላይ፥ ልጄ ሆይ፥ ተግሣጽን ስማ፤ ብዙ መጻሕፍትን ማድረግ ፍጻሜ የለውም፥ እጅግም ምርምር ሰውነትን ያደክማል። የነገሩን ሁሉ ፍጻሜ እንስማ፤ ይህ የሰው ሁለንተናው ነውና፤ እግዚአብሔርን ፍራ፥ ትእዛዙንም ጠብቅ። መጽሐፈ መክብብ 12፡12-13
ሰው እግዚአብሄርን የመፍራት ጥበብ ከሌለው ምንም ጥበብ እንደሌለው ይቆጠራል፡፡ ሰው እግዚአብሄርን የመፍራት ጥበብ ካለው ደግሞ ለኑሮ ለስኬትና ለክንውን የሚያስፈልገው ጥበብ ሁሉ እንዳለው ይቆጠራል፡፡
አሁን ያለው የሰው የእውቀት ችግር ሁሉ የእግዚአብሄር እውቀት ችግር ነው፡፡ የሰው የእውቀት ችግር ሁሉ የሚፈታው የእግዚአብሄር እውቀት ችግር ሲፈታ ነው፡፡ ስለዚህ ነው ህዝቤ አውቀት ከማጣት የተነሳ ጠፍቶዋል የሚለው፡፡
ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሣ ጠፍቶአል፤ አንተም እውቀትን ጠልተሃልና እኔ ካህን እንዳትሆነኝ እጠላሃለሁ፤ የአምላክህንም ሕግ ረስተሃልና እኔ ደግሞ ልጆችህን እረሳለሁ። ትንቢተ ሆሴዕ 4፡6
ሰው የእውቀት ችግሩ የሚፈታው የእግዚአብሄርን እውነት ሲያውቅ በነው፡፡ ሰው ራሱንና ሌላውን ሰው በትክክል የሚያውቅው እግዚአብሄርን ሲያውቅ ነው፡፡ የሰው የእውቀት ችግር የሚፈታው የእግዚአብሄር እውቀት ችግር በህይወቱ ሲፈታ ብቻ ነው፡፡
እውነትንም ታውቃላችሁ እውነትም አርነት ያወጣችኋል አላቸው። የዮሐንስ ወንጌል 832
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #እምነት #ሃሳብ #ጥበብ #ማስተዋል #እግዚአብሔርንመፍራት #ጥበብ #ክፉ #መልካም #ፍርድ #እውቅና #ፍፁም #ችግር #መፍትሄ #አላማ #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ  #እምነት #ቃል  #ማደስ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment