Popular Posts

Sunday, July 15, 2018

ሰውን በክርስቶስ ማወቅ

ስለዚህ እኛ ከአሁን ጀምሮ ማንንም በሥጋ እንደሚሆን አናውቅም፤ ክርስቶስንም በሥጋ እንደ ሆነ ያወቅነው ብንሆን እንኳ፥ አሁን ግን ከእንግዲህ ወዲህ እንደዚህ አናውቀውም። 2ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 5፡16
ሰው የሚያይበትና እግዚአብሄር የሚያይበት አስተያየት ይለያያል፡፡
እግዚአብሔር ግን ሳሙኤልን፦ ፊቱን የቁመቱንም ዘለግታ አትይ፤ ሰው እንዲያይ እግዚአብሔር አያይምና ናቅሁት፤ ሰው ፊትን ያያል፥ እግዚአብሔር ግን ልብን ያያል አለው። መጽሐፈ ሳሙኤል ቀዳማዊ 16፡7
የሰውን እውነተኛ ማንነት ሊነግረን የሚችለው የፈጠረው እግዚአብሄር ብቻ ነው፡፡ ሰው ስለሰው ማንነት ቢነግረን ሊሳሳት ይችላል፡፡
ሰውን በክርስቶስ ማየት ማለት ሰውን እግዚአብሄር እንደሚያየው ማየት ማለት ነው፡፡ እግዚአብሄር እንደሚያየው ካላየ በስተቀር ሰው ሰውን በትክክል ሊረዳው አይችልም፡፡ እግዚአብሄር እንደሚያየው ካላየ በስተቀር ሰው ከሰው ጋር በትክክል ህብረት ሊያደርግ አይችልም፡፡  
ሰውን በሥጋ እንደሚሆን አናውቅም ሰውን የምናውቅው በክርስቶስ ነው ማለት ምንድነው?
·         ሰውን በክርስቶስ እንጂ በስጋ እንደሚሆን አላውቀውም ማለት ክርስትያንን እግዚአብሄር እንደሚወደው እንጂ ሰው እንደሚያየው አላየውም፡፡

ሰው በሰው ላይ ብዙ አቃቂር ሊያወጣ ይችላል፡፡ ሰው እንኳን በሰው ላይ በራሱ ላይ እንኳን እንከን ያገኛል፡፡ የሰው ፍርድ ትክክል የማይሆነው ሰው አይኑ እንዳየ ጆሮው እንደሰማ ከፈረደ ነው፡፡ የሰው ፍርድ ትክክል የሚሆነው ሰው እግዚአብሄር አንደሚያየው አይቶ በፅድቅ ከፈረደ ነው፡፡ በፅድቅ መፍረድ ማለትደግሞ እግዚአብሄር እንደሚያየው አይቶ መፍረድ ማለት ነው፡፡
ቅን ፍርድ ፍረዱ እንጂ በመልክ አትፍረዱ። የዮሐንስ ወንጌል 7፡24

·         ሰውን በክርስቶስ እንጂ በስጋ እንደሚሆን አላውቀውም ማለት ክርስትያን በክርስቶስ በመሆኑ ያለውን ቦታ እንጂ ሌሎች ነገሮችን አላይም ማለት ነው
ክርስትያን በእግዚአብሄር ቤተሰብ ውስጥ ባለው ቦታ እንጂ በስሜታችን ልናየው አይገባም፡፡ ክርስትያን በእግዚአብሄር መንግስት ባለው ቦታ ብቻ ክብር አለው፡፡ ክርስትያን ቦታው የሚጠይቀውን ክብር ማግኘት አለበት፡፡ 
ለሁሉ የሚገባውን አስረክቡ፤ ግብር ለሚገባው ግብርን፥ ቀረጥ ለሚገባው ቀረጥን፥ መፈራት ለሚገባው መፈራትን፥ ክብር ለሚገባው ክብርን ስጡ። ወደ ሮሜ ሰዎች 13፡7
·         ሰውን በክርስቶስ እንጂ በስጋ እንደሚሆን አላውቀውም ማለት ክርስቲያን በክርስቶስ ባለው እምቅ ሃይል እንጂ በውጭ በሚታየው ድካም አላየውም፡፡

ክርስትያን የእግዚአብሄር ልጅ ነው፡፡ ቢደክም ድካሙን የሚሸፍን የእግዚአብሄር ፀጋ ተገልጦዋል፡፡ ስለዚህ ድካምን ብቻ አይቶ የሚያበረታውን ፀጋ አለማየት ፍርዳችንን ፍርደ ገምድል ያደረገዋል፡፡
እርሱም፦ ጸጋዬ ይበቃሃል፥ ኃይሌ በድካም ይፈጸማልና አለኝ። እንግዲህ የክርስቶስ ኃይል ያድርብኝ ዘንድ በብዙ ደስታ በድካሜ ልመካ እወዳለሁ። ስለዚህ ስለ ክርስቶስ በድካም በመንገላታትም በችግርም በስደትም በጭንቀትም ደስ ይለኛል፤ ስደክም ያን ጊዜ ኃይለኛ ነኝና። 2ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 12፡9-10

·         ሰውን በክርስቶስ እንጂ በስጋ እንደሚሆን አላውቀውም ማለት ሰውን በስጋ ያሉትን ነገሮች አልቆጥራቸውም
ሰውን በክርስቶስ እንጂ በስጋ እንደሚሆን አላውቀውም ማለት ሰውን ዘሩን አላይም፣  ተፈጥሮአዊ ድካሙን አላይም ፣ ፆታውን አላይም የመጣበትን የኋላ ታሪክ አላይም ማለት ነው፡፡
አለቆች የመሰሉት ግን፥ በፊት ማን እንደ ነበሩ አይገደኝም፤ እግዚአብሔር የሰውን ፊት አይቶ አያደላም፤ አለቆች የመሰሉት አንዳች እንኳ አልጨመሩልኝምና፥ ወደ ገላትያ ሰዎች 2፡6
·         ሰውን በክርስቶስ እንጂ በስጋ እንደሚሆን አላውቀውም ማለት ሰውን እግዚአብሄር እንደሚያየው እንጂ ሰው እንደሚያየው አላየውም፡፡
ሰውን በክርስቶስ እንጂ በስጋ እንደሚሆን አላውቀውም ማለት እግዚአብሄር ኢየሱስን ፍፁም አድርጎ እንደሚመለከተው እግዚአብሄር ሰውን ፍጹም አድርጎ እንደሚመለከተው መመልከት ማለት ነው፡፡
አንድ ጊዜ በማቅረብ የሚቀደሱትን የዘላለም ፍጹማን አድርጎአቸዋልና። ወደ ዕብራውያን 10፡14
·         ሰውን በክርስቶስ እንጂ በስጋ እንደሚሆን አላውቀውም ማለት እግዚአብሄር ኢየሱስን እንደወደደው ሰውን እንደሚወደው ማወቅ ነው፡፡

እንዲሁም ዓለም አንተ እንደ ላክኸኝ በወደድኸኝም መጠን እነርሱን እንደ ወደድሃቸው ያውቃል። የዮሐንስ ወንጌል 17፡22-23

·         ሰውን በክርስቶስ እንጂ በስጋ እንደሚሆን አላውቀውም ማለት እግዚአብሄር ኢየሱስን በሚያይበት መነፅር ሰውን እንደሚያይ ማወቅ ነው፡፡

እኛም አንድ እንደ ሆንን አንድ ይሆኑ ዘንድ፤ እኔም በእነርሱ አንተም በእኔ ስትሆን፥ በአንድ ፍጹማን እንዲሆኑ፥ የሰጠኸኝን ክብር እኔ ሰጥቻቸዋለሁ፤ የዮሐንስ ወንጌል 17፡22-23
     
·         ሰውን በክርስቶስ እንጂ በስጋ እንደሚሆን አላውቀውም ማለት እግዚአብሄር ሰዎችን ለመገሰፅ ካልተጠቀመብን በስተቀር በራሳችን አነሳሽነት ብቻ በሰዎች ላይ እንፈርድም ማለት ነው፡፡
ነገር ግን በእናንተ ዘንድ ወይም በሌላ ሰው ዘንድ ብፈረድ ለእኔ ምንም አይደለም፤ እኔም በራሴ እንኳ አልፈርድም፤ 1 ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 4፡3
·         ሰውን በክርስቶስ እንጂ በስጋ እንደሚሆን አላውቀውም ማለት ሰውን በክቡር ደሙ እንደተዋጀ ክቡር ፍጥረት እንጂ እንደተራ ሰው አላየውም ማለት ነው፡፡
ከአባቶቻችሁ ከወረሳችሁት ከከንቱ ኑሮአችሁ በሚያልፍ ነገር በብር ወይም በወርቅ ሳይሆን፥ ነውርና እድፍ እንደ ሌለው እንደ በግ ደም በክቡር የክርስቶስ ደም እንደ ተዋጃችሁ ታውቃላችሁ። 1ኛ የጴጥሮስ መልእክት 1፡18-19
ስለዚህ እኛ ከአሁን ጀምሮ ማንንም በሥጋ እንደሚሆን አናውቅም፤ ክርስቶስንም በሥጋ እንደ ሆነ ያወቅነው ብንሆን እንኳ፥ አሁን ግን ከእንግዲህ ወዲህ እንደዚህ አናውቀውም። 2ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 5፡16
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #በክርስቶስ #ማንነት #የእግዚአብሄርንእይታ #በስጋ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ማየት #በስጋደረጃ #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #አዲስፍጥረት #ክርስቶስ #ስፍራ #ማእረግ #ስልጣን

No comments:

Post a Comment