Popular Posts

Friday, July 8, 2016

ይቻላል - እግዚአብሄርን ማስደሰት

በምድር ላይ ሰዎችን የሚያስደስቱና የሚያስደንቁ ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ ሰዎች መልካመ ሲለብሱ ደስ ይላቸዋል፡፡ ሰዎች መልካም ሲበሉ ከፍ ይላሉ፡፡ ሰዎች ትልቅ ቤት ውስጥ ሲኖሩ ደስ ይላቸዋል ይደነቃሉ፡፡
እግዚአብሄር በመልኩና በአምሳሉ ቁርጥ እርሱን አስመስሎ ፈጥሮናል፡፡ እግዚአብሄርም እንደ እኛ ስሜት አለው፡፡ እኛን የሚያስደንቁና የማያስደንቁ ነገሮች እንዳሉ እንዲሁ እግዚአብሄርን የሚያስደንቁትና የማያስደንቁት ነገሮች አሉ፡፡

እኛን የሚያስደስቱን ነገሮች ሁሉ ግን እግዚአብሄርን አያስደስቱትም ወይም አያስደንቁትም፡፡ እዚህ ጋር ግን እግዚአብሄርን የሚያስደስተው ምን እንደሆነ በግልፅና በማያሻማ ቋንቋ ተገልጾ እናገኘዋለን፡፡ ደግሞም በእምነት ባልተደረገ ማንኛውም ነገር እግዚአብሄርን ማስደሰት ዘበት እንደሆነ መፅሃፍ ቅዱስ ያስረዳል፡፡  

ያለ እምነትም ደስ ማሰኘት አይቻልም፤ ወደ እግዚአብሔር የሚደርስ እግዚአብሔር እንዳለ ለሚፈልጉትም ዋጋ እንዲሰጥ ያምን ዘንድ ያስፈልገዋልና። ዕብራውያን 11፡6

በዚህ ምድር ስንኖር በምድራዊ በአይናችን ከሚታየው ነገር ባሻገር የእግዚአብሄርን መንግስት ስናይና እግዚአብሄርን በውሳኔያችን ስናስቀድም ለእርሱ እውቅና ስንሰጥ እግዚአብሄርን ያስደስተዋል፡፡ ሮሜ 8፡14 እና ምሳሌ 3፡5-6

በዙሪያችን ከከበበን ነገሮች በላይ የእግዚአብሄርን ቃል ስናምን እግዚአብሄር ደስ ይለዋል፡፡ ሮሜ 4:18

በምድር ኑሮዋችን በአይን የማይታየውን የሰማያዊውን መንግስት ያውም መንግስተ ሰማያት በመጠበቅ ስንኖር እግዚአብሄርን እናስደስተዋለን፡፡ ፊሊጲስዩስ  3፡20

በእለት ኑሮዋችን በተፈጥሮ አይን የማይታየውን በውስጣችን የሚኖረውን ጌታ እየሰማንና እየታዘዝን ስንኖር እግዚአብሄር ይደሰታል፡፡ ገላቲያ 2፡20

በእምነት በሰማይ ቤት እንዳለን የምድር ኑሮዋችን ጊዜያዊ መተላለፊያ ብቻ እንደሆነ አድርገን እንደ እንግዳና መፃተኛ ስንኖር እግዚአብሄር ደስ ይለዋል፡፡ 1ኛ ጴጥሮስ 2፡11  እና 2ኛ ቆሮንጦስ 5፡7-8

በስጋዊ አይናችን የማይታየውን እግዚአብሄርን በኑሮዋችን ሁሉ እየፈራን ስንኖር እግዚአብሄር ደስ ይለዋል፡፡ ማቴዎስ 10፡28

ያለ እምነትም ደስ ማሰኘት አይቻልም፤ ወደ እግዚአብሔር የሚደርስ እግዚአብሔር እንዳለ ለሚፈልጉትም ዋጋ እንዲሰጥ ያምን ዘንድ ያስፈልገዋልና። ዕብራውያን 11፡6

No comments:

Post a Comment