Popular Posts

Tuesday, July 5, 2016

እንተያይ

ለፍቅርና ለመልካምም ሥራ እንድንነቃቃ እርስ በርሳችን እንተያይ፤ በአንዳንዶችም ዘንድ ልማድ እንደ ሆነው፥ መሰብሰባችንን አንተው እርስ በርሳችን እንመካከር እንጂ፤ ይልቁንም ቀኑ ሲቀርብ እያያችሁ አብልጣችሁ ይህን አድርጉ። ዕብራውያን 10፡24-25

ሁላችንም በፍቅር መኖር እንፈልጋለን፡፡ ከእኛ ይበልጥ በፍቅር የሚኖር ሰው ስናይ እንደእርሱ ለመሆን እንቀናለን፡፡ ፍቅር ለሰነፎች አይደለም፡፡ ፍቅር ትጋትን ይጠይቃል፡፡ ፍቅር ርካሽ አይደለም፡፡ ፍቅር በትጋትና በንቃት ሊጠበቅ ፡ ሊነቃቃና ሊታደስ ይገባዋል፡፡

ከሰል በደንብ እንዲቀጣጠልና በመቀጣጠል እንዲቆይ መራገብ እንደሚያስፈልገው ሁሉ ፍቅርም እንዲበረታና እንዲቆይና መነቃቃት ይገባዋል፡፡ ፍቅርን የሚያነቃቃው ደግሞ በትጋት መገናኘትና መተያየት ነው፡፡

መልካም ስራም እንዲሁ ትጋትንና ፅናትን ይጠይቃል፡፡ መልካም ስራ ጉልበትን ይጠይቃል፡፡ መልካም ስራ ፅናትንና ብርታትን ይጠይቃል፡፡ መልካም ስራ በትጋት ካልተቀጣጠለ እየሟሸሸ ይሄዳል ቀስ በቀስም ይጠፋል፡፡

በትጋት እርስ በእርስ መተያየት መልካምን ስራ ያነቃቃዋል፡፡ አንዳችን በአንዳችን እምነት እንበረታታለን ፡፡ እንዳችን እንዳችንን እንቀርፃለን፡፡ አንዳችን አንዳችንን እንሞርዳለን እንስላለን፡፡ በመሰብሰብና በመተያየት እንታደሳለን፡፡

ለፍቅርና ለመልካም ስራ እንድንነቃቃ የእግዚአብሄርን ቃል ከሚያምኑ ፡ ከሚኖሩትና ከሚናገሩ ሰዎች ጋር በትጋት እንሰብሰብ ፡፡ እንዴት ለጌታ እንደሚገባ እንደምንኖር እርስ በእርሳችን እንመካከር፡፡

አንዳንዴ መልካም የሰራን እየመሰለን እንስታለን፡፡ ሰው ከተሰበሰብንና እርስ በእርሳችን ከተያየን ሌላው ችግራችንን ይነግረናል፡፡ የሌላውንም ችግር አይተን ለጌታ እንዲኖር በፍቅር ማበረታታት ቤተሰባዊ ሃላፊነታችን ነው፡፡ አንዳችን የሌላው ጠባቂዎች ነን፡፡ ይህንንም የመሰብሰብ መልካም ልማድ አብልጠን እንድናደርግ መፅሃፍ ይመክረናል፡፡

No comments:

Post a Comment