Popular Posts

Thursday, August 3, 2023

አስቀድማችሁ ከፈሪሳውያን እርሾ ተጠበቁ! ክፍል 6

 

ኢየሱስም፦ ከፈሪሳውያንና ከሰዱቃውያን እርሾ ተጠንቀቁና ተጠበቁ አላቸው። እነርሱም ከፈሪሳውያንና ከሰዱቃውያን ትምህርት እንጂ ከእንጀራ እርሾ እንዲጠበቁ እንዳላላቸው ያን ጊዜ አስተዋሉ። የማቴዎስ ወንጌል 16:6፣12

የፈሪሳዊያንን ትምህርት መከተል ከዋናው የክርስትና ትምህርት አላማ ውጭ በሆነ በማይጠቅም ትእዛዝ ላይ ጊዜን መፍጀት ነው፡፡

ለምሳሌ መፅሃፍ ቅዱስ ህሊናችንን እንዳንስት እና ለስጋችን አርነት እንዳንሰጥ እንዳንሰክር ያዘናል፡፡ ፈሪሳዊያን ደግሞ ከእግዚአብሔር በላይ አብዝተው ሲቀኑለት "አትያዝ፥ አትቅመስ፥ አትንካ" በሚል ትእዛዝ ሊያስፈራሩን ይሞክራሉ፡፡ ፈሪሳዊያን ቃሉን ይበልጥ ሊያጠናክሩት ሲሞክሩ ትእዛዙ ለሰዎች በመጀመሪያ የተሰጠበትን አላማ ይስቱታል፡፡ "አትያዝ፥ አትቅመስ፥ አትንካ" የሚሉ ትእዛት ህሊናን ከመሳት እና ለስጋ አርነት ከመስጠት ጋር ምንም ግንኙነት ስለሌላቸው እግዚአብሔር  ለምንድነው ይህንን ትእዛዝ የሰጠው ብለን ግራ እንድንጋባ ያደርጉናል፡፡

እንደዚህ አይነት "አትያዝ፥ አትቅመስ፥ አትንካ" የሚባሉ ትእዛዛት በውጭ እግዚአብሔርን ለማምለክ ለትህትና ስጋንም ለመጨቆን ጥበብ ያላቸው እና የሚጠቅሙ ይመስላሉ ነገር ግን ሥጋ ያለ ልክ እንዳይጠግብ ለመከልከል ምንም አይጠቅሙም፡፡

እንደ ሰው ሥርዓትና ትምህርት። አትያዝ፥ አትቅመስ፥ አትንካ ለሚሉት ትእዛዛት በዓለም እንደምትኖሩ ስለ ምን ትገዛላችሁ? እነዚህ ሁሉ በመደረግ ሊጠፉ ተወስነዋልና። ይህ እንደ ገዛ ፈቃድህ በማምለክና በትሕትና ሥጋንም በመጨቆን ጥበብ ያለው ይመስላል፥ ነገር ግን ሥጋ ያለ ልክ እንዳይጠግብ ለመከልከል ምንም አይጠቅምም። ወደ ቆላስይስ ሰዎች 2፡20-23

የፈሪሳዊያን በትምህርታቸው ቃሉን እንዳለ ከማስተማር ይልቅ አሻሽለን አጠናክረን እናቀርበዋለን ሲሉ እንዳለ ይሽሩታል፡፡ የእግዚአብሔር ቃል በራሱ ጠንካራ ቃል ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል የማንንም የማጠናከሪያ እርዳታ አይፈልግም፡፡ እንዲያውም የእግዚአብሔርን ቃል ለማጠናከር አስበን ካዛነፍነው ከነጭራሹ የተሰጠበትን አላማ ይስታል ብሎም ሃይሉንም ያጣል፡፡

ባስተላለፋችሁትም ወግ የእግዚአብሔርን ቃል ትሽራላችሁ፤ እንደዚሁም ይህን የሚመስል ብዙ ነገር ታደርጋላችሁ። የማርቆስ ወንጌል 7፡13

አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa

#ኢየሱስ #ጌታ #ፈሪሳውያን #ግብዝነት #የአምልኮትመልክ # #ጻፎች #ቤተክርስቲያን #መፅሐፍቅዱስ #ቃል #እግዚአብሔር #ሰዱቃውያን


No comments:

Post a Comment