Popular Posts

Monday, July 10, 2017

ህይወታችንን የምናባክንባቸው 8 መንገዶች

1.      ከእግዚአብሄር ውጭ ህይወትን መፈለግ
ሰው የተፈጠረው እና ዲዛይን የተደረገው በእግዚአብሄር እንዲኖር ነው፡፡ ሰው በእንጀራ ብቻ አይኖርም፡፡ ሰው የሚያየውና የሚከተለው የሚታየውን ቁሳቁስ ብቻ ከሆነ ህይወቱን እያባከነ ነው፡፡
እርሱም መልሶ፦ ሰው ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣ ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም ተብሎ ተጽፎአል አለው። ማቴዎስ 4፡4
2.     እግዚአብሄር ያልመራንን ለመስራት መሞከር
እግዚአብሄር በህይወታችን ያስቀመጠው ነገር ሁሉ የተቀመጠው እግዚአብሄር በህይወታችን ላለው አላማ ነው፡፡ የምናባክነው ትርፍ ነገር የለም፡፡ ሰው በህይወቱ ያለውን የእግዚአብሄርን አላማ መፈለግና መከተል ትቶ እግዚአብሄር ያላለውን ነገር ሲያደርግ ህይወቱን ያባክናል፡፡
እኛ ፍጥረቱ ነንና፤ እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ በክርስቶስ ኢየሱስ ተፈጠርን። ኤፌሶን 2፡10
3.     ከጎረቤታችን ጋር መፎካከር  
እግዚአብሄር ልዪ ለሆነ የህይወት አላማ እያንዳንዳችንን ጠርቶናል፡፡ የጎረቤታችንና የእኛ የህይወት አላማ ይለያያል፡፡ እኛ ግን ከጎረቤታችን ጋር ከተፎካከረን የማይገናኝና የማይሆን ነገር እያፎካከርን ነው፡፡ እኛ መወዳደር ያለብን እግዚአብሄር በህይወታችን ካስቀመጠው የህይወት ግብ ጋር ነው፡፡ እግዚአብሄር በህይወታችን ያስቀመጠውን ግብ ከመታን ስኬታማ ነን፡፡ እግዚአብሄር በህይወታችን ያስቀመጠውን አላማ ግብ ካልመታን ደግሞ ከማንም የበለጥን ቢመስለን ህይወታችንን እባክነናል፡፡  
ራሳቸውን ከሚያመሰግኑ ከአንዳንዶች ጋር ራሳችንን ልንቆጥር ወይም ራሳችንን ልናስተያይ አንደፍርምና፤ ነገር ግን እነርሱ ራሳቸውን ከራሳቸው ጋር ሲያመዛዝኑ፥ ራሳቸውንም ከራሳቸው ጋር ሲያስተያዩ፥ አያስተውሉም። 2ኛ ቆሮንቶስ 10፡12
4.     ባለፈው ህይወት ውስጥ መኖር
ሰው ያለፈውን ካልረሳ ደጋግሞ ይኖረዋል፡፡ ሰው ያለፈውን ካልረሳ ከወደፊቴ ይልቅ ያለፈው ይሻላል እያለ ነው፡፡ ሰው ያለፈውን ካልረሳ በወደፊቱ ተስፋ ቆርጧል ማለት ነው፡፡ ሰው ባለፈው ከኖረ በልቡ አርጅቷል ማለት ነው፡፡
ወንድሞች ሆይ፥ እኔ ገና እንዳልያዝሁት እቈጥራለሁ፤ ነገር ግን አንድ ነገር አደርጋለሁ፤ በኋላዬ ያለውን እየረሳሁ በፊቴ ያለውን ለመያዝ እዘረጋለሁ፥ ፊልጵስዩስ 3፡13
5.     ስለኑሮ መጨነቅ
ሰው ድርሻውን የእግዚአብሄርን ፅድቅና መንግስቱን መፈለግ ትቶ ስለኑሮ ከተጨነቀ ህይወቱን ያባክናል፡፡ ሰው በአንድ ጊዜ የእግዚአብሄርን መንግስት መፈለግ እንዲሁም ስለኑሮ መጨነቅ አይችልም፡፡ ሰው ለሁለት ጌቶች መገዛት አይችልም፡፡ ለገንዘብ የሚገዛ ሰው ለእግዚአብሄር መገዛት አይችልም፡፡ ለኑሮ የሚጨነቅ ሰው ለእግዚአብሄር መንግስት የሚጠቅመውን ውድ ህይወቱን ያባክናል፡፡
ከእናንተ ተጨንቆ በቁመቱ ላይ አንድ ክንድ መጨመር የሚችል ማን ነው? ሉቃስ 12፡25
6.     በሚታይ መኖር
ሰው በሚታየው ብቻ የሚኖር ከሆነ የማይታየውን የእግዚአብሄርን መንግስት ማየት ካልቻለ ህይወቱን ያባክናል፡፡ ሰው በምድር ላይ ብቻ ስላለው ኑሮ ካሰብ ለዘላለም ስለሚኖርበት ህይወት ካላሰበና የዘላለም ህይወትን ካልያዘ ህይወቱን በከንቱ ያባክናል፡፡
የማይታየውን እንጂ የሚታየውን ባንመለከት፥ ቀላል የሆነ የጊዜው መከራችን የክብርን የዘላለም ብዛት ከሁሉ መጠን ይልቅ ያደርግልናልና፤ የሚታየው የጊዜው ነውና፥ የማይታየው ግን የዘላለም ነው። 2ኛ ቆሮንቶስ 4፡17-18
7.       ነፍስን ማጉደል
ሰው ስለስጋው ብቻ ከሮጠ ነፍሱን ግን ከበደለ ብክነት ነው፡፡ ሰው ስጋውን ጎድቶ ነፍሱን ቢያለማ ይሻለው ነበር፡፡ ሰው ግን በምድር ላይ ሁሉንም አግኝቶ ዘላለማዊ ነፍሱን ግን ከጎዳ ምንም አይጠቅመቅውም፡፡
ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጐድል ምን ይጠቅመዋል? ወይስ ሰው ስለ ነፍሱ ቤዛ ምን ይሰጣል? ማቴዎስ 16፡26
8.       በፍቅር አለመኖር
ሰው ሁሉንም ነገር ትክክል አድርጎ ነገር ግን በፍቅር ካላደረገው ብክነት ነው፡፡ እግዚአብሄር ፍቅር ነው፡፡ ሰው ምንም ነገር የሚያደርገው ከፍቅር መሆን አለበት፡፡ ሰው ግን ሁሉን ነገር አድርጎ በፍቅር ግን ካላደረገው ከንቱ ነው፡፡
ትንቢትም ቢኖረኝ ምሥጢርንም ሁሉና እውቀትን ሁሉ ባውቅ፥ ተራሮችንም እስካፈልስ ድረስ እምነት ሁሉ ቢኖረኝ ፍቅር ግን ከሌለኝ ከንቱ ነኝ። ድሆችንም ልመግብ ያለኝን ሁሉ ባካፍል፥ ሥጋዬንም ለእሳት መቃጠል አሳልፌ ብሰጥ ፍቅር ግን ከሌለኝ ምንም አይጠቅመኝም። 1ኛ ቆሮንቶስ 13፡2-3
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #መሪ #ፀጋ #ጭንቀት #ፉክክር #ምስጋና #ሁልጊዜ #ልብ #ለበጎስራሁሉ #ፀጋንሁሉ #እምነት #ፀሎት #ማማጠን #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ትጋት #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment