Popular Posts

Thursday, July 20, 2017

የምስክርነት ጥበብ

ምስክርነት በህይወታችን የቀመስነውን የኢየሱስ ክርስቶስን ነፃነት ለሌሎች የምናካፍልበት መንገድ ነው፡፡ ምስክርነት እጅግ ታላቅ ሃይል ያለው ስራ ነው፡፡ ምስክርነት ወይም ወንጌልን መስበክ ምን እንደሆነ ከመፅሃፍ ቅዱስ እንመልከት፡፡
1.      ምስክርነት ማስተማር አይደለም፡፡
ምስክርነት ወይም የወንጌል ስብከት ሰዎች ኢየሱስ በመስቀል ከላይ የከፈለላቸውን የሃጢያት ክፍያ ለእኔ ነው ብለው እንዲቀበሉ የእግዚአብሄርን ቃል ማስረዳት ነው፡፡ ስብከት መፅሃፍ ቅዱስን ማስተማር አይደለም፡፡ ስብከት የደህንነትን ቃል በመጥቀስ ሰዎች ጌታን ለመከተል እንዲወስኑ መርዳት ብቻ ነው፡፡
ኃጢአተኞችን ሊያድን ክርስቶስ ኢየሱስ ወደ ዓለም መጣ የሚለው ቃል የታመነና ሁሉ እንዲቀበሉት የተገባ ነው፤ 1ኛ ጢሞቴዎስ 1፡15
2.     ምስክርነት ሰው ዳግመኛ እንዲወለድ መርዳት ነው፡፡
ያልተወለደ ሰው መንግስቱን ሊያይና ሊገናነባት አይችልም፡፡ ስለዚህ ሰውን ትምህርት ከማስተማራችን በፊት ዳግመኛ እንዲወለድ መርዳት አለብን፡፡ ዳግመኛ የተወለደና የእግዚአብሄርን መንግስት የሚያይ ብቻ ነው የእግዚአብሄርን ቃል ትምህርት መማር የሚችለው፡፡ ሰው ዳግመኛ ከመወለዱ በፊት ለእርሱ የእግዚአብሄር መንፈስ ነገር ሞኝነት ነው፡፡
ኢየሱስም መልሶ፦ እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም አለው። ዮሃንስ 3፡3
ለፍጥረታዊ ሰው የእግዚአብሔር መንፈስ ነገር ሞኝነት ነውና አይቀበለውም፤ በመንፈስም የሚመረመር ስለ ሆነ ሊያውቀው አይችልም። 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 2፡14
3.     ምስክርነት ክርክርን ማሸነፍ አይደለም፡፡
ምስክርነት የመፅሃፍ ቅዱስ እውቀታችን የምናሳይበት መድረክ አይደለም፡፡ ምስክርነት በትህትና የመዳኛ መንገድን ለሰዎች የምናሳይበት መንገድ ነው፡፡ የመዳኛን እውቀት ከሰጣችሁ በኋላ ላለመቀበል ለመከራከር ከሚፈልግ ሰው ጋር ጊዜ ከማጥፋት ለሌላ ሰው መመስከር ይበልጥ ይጠቅማል፡፡
ነገር ግን ሞኝነት ካለው ምርመራና ከትውልዶች ታሪክ ከክርክርም ስለ ሕግም ከሚሆን ጠብ ራቅ፤ የማይጠቅሙና ከንቱዎች ናቸውና፤ ቲቶ 3፡9
4.     ምስክርነት ሰው ኢየሱስ ጌታ እንደሆነ እንዲመሰክር መርዳት ነው፡፡
ሰው በልቡ አምኖ ይፀድቃል በአፉ መስክሮ ይድናል፡፡ ምስክርነት እግዚአብሄር በኢየሱስ በኩል ያዘጋጀውን የመዳኛ መንገድ ማስቀበልና ኢየሱስ ለሃጢያታችን እንደሞተ በልብ በማመን ኢየሱስ ከሙታን እንደተነሳ በአፍ ማስመስከር ነው፡፡
ኢየሱስ ጌታ እንደ ሆነ በአፍህ ብትመሰክር እግዚአብሔርም ከሙታን እንዳስነሣው በልብህ ብታምን ትድናለህና፤ ሰው በልቡ አምኖ ይጸድቃልና በአፉም መስክሮ ይድናልና። ሮሜ 10፡9-10
5.     ምስክርነት ሰውን ማሳመን አይደለም፡፡
ምስክርነት የእግዚአብሄርን ቃል ማወጅ ነው፡፡ ያንን ቃል ተጠቅሞ አለምን የሚወቅሰው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ቃሉን የማወጅ ስራችንን ከተወጣን በኋላ ማረፍ አለብን እንጂ የመንፈስ ቅዱስን የማሳመን ስራ ለመስራት መሞከር የለብንም፡፡
እርሱም መጥቶ ስለ ኃጢአት ስለ ጽድቅም ስለ ፍርድም ዓለምን ይወቅሳል፤ ዮሃንስ 16፡8
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#እምነት #ወንጌል #ስብከት #ቃል #ዝራ #የምድርጨው #የአለምብርሃን #የአመፃገንዘብ #የእግዚአብሄርሃይል #መንፈስቅዱስ #ቃሉንመስማት #እወጃ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ህይወት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ  

No comments:

Post a Comment