Popular Posts

Sunday, July 30, 2017

እግዚአብሔርን የሚመስሉ የሚሰደዱበት ምክኒያት

በእውነትም በክርስቶስ ኢየሱስ እግዚአብሔርን እየመሰሉ ሊኖሩ የሚወዱ ሁሉ ይሰደዳሉ። 2ኛ ጢሞቴዎስ 3፡12
እግዚአብሔርን መስለው ሊኖሩ የሚወዱ ሁሉ ይሰደዳሉ፡፡ የስደቱን ምክኒያት ማወቅ በስደት እንድንፀና ያስችለናል፡፡ 
ህይወታችን እንግዳ ስለሚሆን ነው፡፡
እግዚአብሔርን መምሰላችን የሚታወቀው አስተሳሰባችን ፣ አነጋገራችን ፣ ፍቅራችንና ኑሮዋችን ለአለም እንግዳ በመሆኑ ነው፡፡ እግዚአብሔርን የማያውቁ ሰዎች የለመዱት ስለስጋ ማሰብን ነው፡፡ ከጠዋት እስከማታ ስጋቸውን እንዴት እንደሚያስደስቱ ያስባሉ፡፡ እኛ ደግሞ እግዚአብሄርን በኑሮዋችን እንዴት እንደምናስደስተው የመንፈስን ነገር እናስባለን፡፡ የእነርሱ ፍላጎትና የእኛ ፍላጎት እጅግ ይለያያል፡፡ እነርሱ ዋጋ የሚሰጡትን ነገር እኛ እንንቀዋልን፡፡ ስለዚህ ይቃወሙናል ያሳድዱናል፡፡   
እንደ ሥጋ ፈቃድ የሚኖሩ የሥጋን ነገር ያስባሉና፥ እንደ መንፈስ ፈቃድ የሚኖሩ ግን የመንፈስን ነገር ያስባሉ። ስለ ሥጋ ማሰብ ሞት ነውና፥ ስለ መንፈስ ማሰብ ግን ሕይወትና ሰላም ነው። ሮሜ 8፡5-6
አለምን ስለማንመስል ከአለም ስለምንለይ ነው፡፡
በአለም ያለው ባህል በስጋ ምኞት መመራት ነው፡፡ እግዚአብሔር የሚመስል ሰው የሚመራው በመንፈስ ፍቃድ ነው፡፡ አለምን ስለማንመስል በዚህም ከሰዎች ስለምንለይ ከሌላ አለም እንደመጡ ሰዎች እንደ እንግዳና መጤ በመታየታችን እንሰደዳለን፡፡
ዓለምን ወይም በዓለም ያሉትን አትውደዱ፤ በዓለም ያለው ሁሉ እርሱም የሥጋ ምኞትና የዓይን አምሮት ስለ ገንዘብም መመካት ከዓለም ስለ ሆነ እንጂ ከአባት ስላልሆነ፥ ማንም ዓለምን ቢወድ የአባት ፍቅር በእርሱ ውስጥ የለም። 1ኛ ዮሃንስ 2፡15-16
ብርሃናችን ጨለማውን ስለሚገልጠው ነው
በብርሃን ስንኖር ጨለማውን እንገልጠዋለን፡፡ ሃጢያትን የሚወዱ ሰዎች ደግሞ ጨለማቸው ሲገለጥ ደስ አይላቸውም፡፡ ስለዚህ ይቃወሙናል ያሳድዱናል፡፡
ብርሃንም ወደ ዓለም ስለ መጣ ሰዎችም ሥራቸው ክፉ ነበርና ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ስለ ወደዱ ፍርዱ ይህ ነው። ክፉ የሚያደርግ ሁሉ ብርሃንን ይጠላልና፥ ሥራውም እንዳይገለጥ ወደ ብርሃን አይመጣም፤ ዮሃንስ 3፡19-20
ከፍ ያለው ህይወታችን ሲያዩ ስለሚሳቀቁ ነው፡፡
እግዚአብሔር የሚመስሉ ሰዎች የሚሰደዱት ከፍ ያለ የህይወት ደረጃ ስለሚኖሩ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በሃጢተያት ውስጥ የሚኖሩትን ሰዎች ውርደት ያጋልጣል፡፡ ክርስትና ምንም የሚወጣለት ነገር የለም ፡፡ እግዚአብሔርን መምሰል ምንም አይወጣለትም፡፡ እግዚአብሔርን በመምሰል በንፅህና የሚኖር ሰው ሲያዩ አለማዊያን ጉድለታቸ ይታያቸዋል፡፡ ንስሃ ገብተው ተዋርደው እነርሱም እግዚአብሔርን ለመምሰል እስካልወሰኑ ድረስ በቅናት እግዚአብሔርን የሚመስሉትን ይቃወማሉ ያሳድዳሉ፡፡
የአሕዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት በመዳራትና በሥጋ ምኞትም በስካርም በዘፈንም ያለ ልክም በመጠጣት ነውርም ባለበት በጣዖት ማምለክ የተመላለሳችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃልና። በዚህም ነገር ወደዚያ መዳራት ብዛት ከእነርሱ ጋር ስለማትሮጡ እየተሳደቡ ይደነቃሉ፤ 1 ጴጥሮስ 4፡3-4
ወደመንግስተሰማያት አትሄዱም የሚል መልክት ስለሚሰጣቸው ነው፡፡
እግዚአብሄርን መፍራታችን እነርሱ አለመፍራታቸው ያስፈራቸዋል፡፡ በንፅህና መኖራችን እነርሱ በንፅህና አለመኖራቸው ያሳቅቃቸዋል፡፡ የኑሮዋችን ንፅህናን አይተውና የእነርሱን ኑሮ አይተው በራሳቸው እኔስ ወደ መንግስተሰማያት አልሄድም ብለው በራሳቸው ይፈርዳሉ፡፡ ኑሮዋችን ተመልሱ በእንደዚህ አይነት ኑሮ ወደ መንግስተሰማያት አትሄዱም ብሎ በዝምታ ይወቅሳቸዋል፡፡
በመጥፎና በጠማማ ትውልድ መካከል ያለ ነቀፋ የዋሆችም ነውርም የሌለባቸው የእግዚአብሔር ልጆች እንድትሆኑ ሳታንጐራጉሩ ክፉም ሳታስቡ ሁሉን አድርጉ፤ በእነርሱም መካከል የሕይወትን ቃል እያቀረባችሁ በዓለም እንደ ብርሃን ትታያላችሁ፥ ስለዚህም በከንቱ እንዳልሮጥሁ በከንቱም እንዳልደከምሁ በክርስቶስ ቀን የምመካበት ይሆንልኛል። ፊልጵስዩስ ሰዎች 2፡14-16
ሰይጣን ስለማይታገሰን ነው፡፡
ሰይጣን የእግዚአብሔር ጠላት የህይወት ጠላት የእኛ ጠላት ስለሆነ የእግዚአብሔርንመለክ በምድር ከላይት ማየት አይፈልግም፡፡  ሃብታም ብንሆን ወይም ዝነኛ ብንሆን ሰይጣን አይደንቀውም እግዚአብሔርን መምሰላችን ግን እረፍት አይሰጠውም፡፡ ሃብታችንን ግን እግዚአብሔርን መምሰል ላይ ካዋልነው አይታገሰውም፡፡
ከእግዚአብሔር እንደ ሆንን ዓለምም በሞላው በክፉው እንደ ተያዘ እናውቃለን። 1ኛ ዮሃንስ 5፡19
እናንተ ከአባታችሁ ከዲያብሎስ ናችሁ የአባታችሁንም ምኞት ልታደርጉ ትወዳላችሁ። እርሱ ከመጀመሪያ ነፍሰ ገዳይ ነበረ፤ እውነትም በእርሱ ስለ ሌለ በእውነት አልቆመም። ሐሰትን ሲናገር ከራሱ ይናገራል፥ ሐሰተኛ የሐሰትም አባት ነውና። እኔ ግን እውነትን የምናገር ስለ ሆንሁ አታምኑኝም። ዮሃንስ 8፡ 44-45
ያም ሆነ ይህ ሰይጣን ስለፈቀድል "አስኮናኞች ኑሩ" ስላለን ሳይሆን የምንኖረው በግድ ነው፡፡ ሰይጣን ወደደም ጠላም በአሸናፊነት እንኖራለን፡፡
ከእግዚአብሔር የተወለደ ሁሉ ዓለምን ያሸንፋልና፤ ዓለምንም የሚያሸንፈው እምነታችን ነው። 1ኛ ዮሐንስ 5፡4
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#እግዚአብሔር #ጌታ #መከተል #መከተል #ስደት #መከራ #ብርሃን #ጨለማ #ንፅህና #መምሰል #እግዚአብሔርንመምሰል #ቃል #ተማሪ #መንፈስቅዱስ #ቃሉንመስማት #ደቀመዝሙር #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #ነፍስንመካድ #መፅሃፍቅዱስ #ተከታይ #ህይወት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment