Popular Posts

Wednesday, May 31, 2017

የክርስቶስ ባህሪ - ትእግስት

በክርስትያን ህይወት ውስጥ ባህሪ በጣም ወሳኝ ነገር ነው፡፡ ባህሪያችን በተሰራ መጠን በእግዚአብሄር መንግስት ውስጥ ጠቃሚነታችን ይጨምራል ለብዙዎችም በረከት እንሆናለን፡፡ ባህሪያችንን ባሳደግን መጠን ደግሞ በእግዚአብሄር መንግስት ውስጥ ያለን ተፅእኖ ይጨምራል እግዚአብሄርም ለተጨማሪ ሃላፊነት ያምነናል፡፡  
እግዚአብሄር ክብር ፈጥሮናል፡፡ እኛ የራሳችን አይደለንም፡፡ እግዚአብሄር ክብሩን ሊገልጥብን በህይወታችን በትጋት ይሰራል፡፡
አንዳንዴ የእግዚአብሄር አሰራርና የኛ አስተሳሰብ አንድ ላይሆን ይችላል፡፡ መታገስ እና እግዚአብሄርን መጠበቅ የሚያስፈልገው የእግዚአብሄር አሰራርና የእኛ ፍላጎት ሁልጊዜ አብሮ ላይሄድ ስለሚችል ነው፡፡
የእግዚአብሄርን እውነተኛውን ነገር ማግኘት ከፈለግን እግዚአብሄርን መከተል አለብን ሌላ መንገድ የለውም፡፡ እግዚአብሄር የራሱ እርምጃ አለው፡፡ እግዚአብሄር በእኛ ፍጥነት አይገባም፡፡ ስለዚህ ነው ከእግዚአብሄር ጋር በትህትና ለመኖርና ለማፍራት ትእግስት ወሳኝ የሚሆነው፡፡
የእግዚአብሄርን እርምጃ ሳንጠብቅ የምናደርገው ነገር የእኛ እንጂ የእርሱ አይሆንም፡፡
በህይወታችን እግዚአብሄርን ብቻ ሳይሆን ሰውንም መታገስ ይገባናል፡፡ እያንዳንዱ ሰው የራሱ ደረጃ እና አመለካከት አለው፡፡ ከሰው ጋር አብሮ ለመኖርና ለማገልገል በዚያም ፍሬያማ ለመሆን ትግስት ይጠይቃል፡፡ ሰው ሁሉ እኛን ይምሰል ማለት ትእቢት ነው፡፡ ሰውን መታገስ ግን ትህትና ነው፡፡
ማንኛውም ሃይል ካለመቆጣጠሪያ መሳሪያው አደገኛ እንደሆነ ሁሉ ባህሪው ያልተሰራ ሰው አደገኛ ነው፡፡ ባህሪው ያላደገ ሰው  ራሱን ተቆጣጥሮ ሃይሉን በምን ላይ ማፍሰስ እንዳለበት አያውቅም፡፡ ለዚህ ነው ከሃይል ይልቅ ባህሪ ይበልጣል የሚባለው፡፡
ትዕግሥተኛ ሰው ከኃያል ሰው ይሻላል፥ በመንፈሱም ላይ የሚገዛ ከተማ ከሚወስድ ይበልጣል። ምሳሌ 16፡32
በህይወታችን ልናሳድገው የሚገባን ባህሪ ትግስት ነው፡፡ እግዚአብሄር በህይወታችን በትጋት እየሰራ ያለው ትእግስትን ነው፡፡
ይህም ብቻ አይደለም፥ ነገር ግን መከራ ትዕግሥትን እንዲያደርግ፥ ትዕግሥትም ፈተናን ፈተናም ተስፋን እንዲያደርግ እያወቅን፥ በመከራችን ደግሞ እንመካለን፤ ሮሜ 5፡3-4
ካለ ትእግስት ግን ምንም ነገር ቢኖረን ከንቱ ነው፡፡ ትእግስት ሙሉ እና ፍፁም ለበጎ ስራ ሁሉ የተዘጋጀን ፍፁም ሰዎች ያደርገናል፡፡
ወንድሞቼ ሆይ፥ የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ አውቃችሁ፥ ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ እንደ ሙሉ ደስታ ቍጠሩት ትዕግሥትም ምንም የሚጎድላችሁ ሳይኖር ፍጹማንና ምሉዓን ትሆኑ ዘንድ ሥራውን ይፈጽም። ያዕቆብ 12-3
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #የመንፈስፍሬ #ፍቅር #ሰላም #ደስታ #ዘር #ባህሪ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #የእግዚአብሄርህይወት #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #በጎነት #የዋሃት #ራስንመግዛት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment