Popular Posts

Monday, May 22, 2017

ዛሬ ተብሎ ሲጠራ

ወንድሞች ሆይ፥ ምናልባት ሕያው እግዚአብሔርን የሚያስክዳችሁ ክፉና የማያምን ልብ ከእናንተ በአንዳችሁ እንዳይኖር ተጠንቀቁ፤ ነገር ግን ከእናንተ ማንም በኃጢአት መታለል እልከኛ እንዳይሆን፥ ዛሬ ተብሎ ሲጠራ ሳለ፥ በእያንዳንዱ ቀን እርስ በርሳችሁ ተመካከሩ፤ ዕብራውያን 3፡12-13
ክርስትና የሰነፎች አይደለም፡፡ ክርስትና የጨካኞች ነው፡፡ ክርስትና የልፍስፍሶች አይደለም፡፡
ከመጥምቁም ከዮሐንስ ዘመን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ መንግሥተ ሰማያት ትገፋለች፥ ግፈኞችም ይናጠቋታል። ማቴዎስ 11፡12
ክርስትና ትጋትን ይጠይቃል፡፡ በክርስትና ትጋታችንን ከሚጠይቀው ነገር አንዱ ከወንድሞች ጋር ህብረት ማድረግ ነው፡፡
ሰይጣን አለ፡፡ የሚዋጋ ጠላት አለ፡፡ የሚያታልል የሚያስት ዲያቢሎስ አለ፡፡ ልባችንን የሚፈልግ ልባችንን ከእግዚአብሄር ቃል በተቃራኒ ቃል የሚደበድብ አለ፡፡ ካልተጠነቀቀን ክፉና የማያምን ልብ ሊኖረን ይችላል፡፡ ወደፊት ክፉና የማያምን ልብ ሊኖረኝ በፍፁም እይችልም ብሎ ሊዝናና የሚችል ሰው የለም፡፡
ሊስቱ አይችሉም ብለን በጣም የተማመንባቸው ሰዎች ሲስቱ አይተናል፡፡ መፍራት እንጂ በትቢት ማሰብ አያዋጣም፡፡
ስለዚህ እንደ ቆመ የሚመስለው እንዳይወድቅ ይጠንቀቅ። 1ኛ ቆሮንቶስ 10፡12
ሃዋሪያው ጳውሎስ እንኳን እንዳይጣል በጥንቃቄ እንደሚኖር ያስተምራል፡፡
ነገር ግን ለሌሎች ከሰበክሁ በኋላ ራሴ የተጣልሁ እንዳልሆን ሥጋዬን እየጎሰምሁ አስገዛዋለሁ። 1ኛ ቆሮንቶስ 9፡27
ነገር ግን ላለመሳት ተስፋ አለ፡፡ ሰው በየእለቱ ከወንድሙ ጋር ከተመካከረ አይስትም፡፡ ሰው በየእለቱ ከወንድሙ ጋር ህብረት ካደረገ በሃጢያት መታለል አልከኛ አይሆንም፡፡ ሰው ከክርስትያን ወንድሙ ጋር በእውነት ህብረት እያደረገ እግዚአብሄርን የሚያስክድ ክፉና የማያምን ልብ ሊኖረው አይችልም፡፡
እግዚአብሄር በህብረት ውስጥ ለልባችን ጤንነትና ለእምነታችን እጅግ ጠቃሚ ነገር ካስቀመጠ እኛም በትጋት ከወንድሞቻችን ጋር በትጋት ህብረት ልናደርግ ይገባናል፡፡
ወንድሞች በኅብረት ቢቀመጡ፥ እነሆ፥ መልካም ነው፥ እነሆም፥ ያማረ ነው። ከራስ እስከ ጢም እንደሚፈስስ፥ እስከ አሮን ጢም፥ በልብሱ መደረቢያ እንደሚወርድ ሽቱ ነው። በጽዮን ተራሮች እንደሚወርድ እንደ አርሞንዔም ጠል ነው፤ በዚያ እግዚአብሔር በረከቱን ሕይወትንም እስከ ዘላለም አዝዞአልና። መዝሙር 133፡1-3
እኛ ካለንበት ነገር መንጥቆ ሊያወጣን የሚችን ፀጋ በሌላው ወንምድማችን ውስጥ አተቀምጧል፡፡ በወንድማችን ውሰጥ ያለውን ፀጋ የምንካፈለው በንግግርና በምክክር ነው፡፡ የወንድማችንን ቃል ስንሰማ በዚያ ፀጋን እንካፈላለን፡፡  
ለሚሰሙት ጸጋን ይሰጥ ዘንድ፥ እንደሚያስፈልግ ለማነጽ የሚጠቅም ማናቸውም በጎ ቃል እንጂ ክፉ ቃል ከአፋችሁ ከቶ አይውጣ። ኤፌሶን 4፡29
ወንድሞች ሆይ፥ ምናልባት ሕያው እግዚአብሔርን የሚያስክዳችሁ ክፉና የማያምን ልብ ከእናንተ በአንዳችሁ እንዳይኖር ተጠንቀቁ፤ ነገር ግን ከእናንተ ማንም በኃጢአት መታለል እልከኛ እንዳይሆን፥ ዛሬ ተብሎ ሲጠራ ሳለ፥ በእያንዳንዱ ቀን እርስ በርሳችሁ ተመካከሩ፤ ዕብራውያን 312-13
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ወንድሞች #ፍቅር #ፀጋመካፈል #የወንድሞችህብረት #ዛሬ #እልከኛልብ #የሃጢያትመታለል #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ልብ #ህብረት #ግንኙነት #ሽቱ #ያማረ #በፍፁምሃይል #መውደድ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #መናገር #ፅናት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment