Popular Posts

Sunday, May 7, 2017

የምንቀበለው ብቸኛው ገድል

መልካሙን የእምነት ገድል ተጋደል፥ 1 ጢሞቴዎስ 612
በምድር ላይ ብዙ አይነት ተጋድሎዎች አሉ፡፡ ሰዎች ብዙ ነገር ለማድረግ ፣ ብዙ ነገር ለማግኘትና ብዙ ነገር ለመሆን ይጋደላሉ፡፡
በመፅሃፍ ቅዱስ ውስጥ ግን እንድንጋደለው የተሰጠን አንዱ ተጋድሎ የእምነት ተጋድሎ ብቻ ነው፡
የሰው ልጆች የህይወት ጥያቄ ሁሉ በክርስቶስ የመስቀል ስራ ተመልሷል፡፡ አሁን ያለው ብቸኛ ተጋድሎ በዚያ በክርስቶስ በተሰራው ስራ ላይ የመቆም የእምነት ተጋድሎ ብቻ ነው፡፡
ኢየሱስ በመስቀል ላይ ከሰራው ስራ ውጭ አሁን አንደ አዲስ የምንቆረቁረው ስራ የለም፡፡ ክርስቶስ ኢየሱስ በመስቀል ላይ ካሸነፈው ተጋድሎ ውጭ የምንጋደለው አዲስ ጠላት የለም፡፡ ኢየሱስ በመስቀል ላይ ከጨረሰው ስራ ውጭ አዲስ የምንሰራው አዲስ ስራ የለም፡፡
አሁን ያለው ተጋድሎ የእምነት ተጋድሎ ብቻ ነው፡፡ አሁን ያለው ተጋድሎ የእግዚአብሄርን ቃል ለመስማት ፣ የእግዚአብሄርን ፈቃድ ለመረዳት ፣ በእግዚአብሄር ቃል አካባቢ ውስጥ ለመቆየት ፣ የእግዚአብሄርን ቃል ለመጠበቅ ፣ በእግዚአብሄር ቃል ላይ ለመቆምና በእግዚአብሄር ቃል ላይ ለመጽፅናት ያለ ተጋድሎ ብቻ ነው፡፡   
የእምነት ተጋድሎ አይነቶች  
1.      እምነት የሚመጣው እግዚአብሄር ስለ እኛ ያለውን ፈቃድ ከመረዳት በመሆኑ የእግዚአብሄርን ፈቃድ ለመረዳት የእግዚአብሄርን ቃል መፈለግ ማጥናት መስማት የእምነት ተጋድሎ ክፍል ነው፡፡ 
እንግዲያስ እምነት ከመስማት ነው መስማትም በእግዚአብሔር ቃል ነው። ሮሜ 10፡17 
2.     የእግዚአብሄርን ቃል ስንሰማ በሙሉ ልብ በማስተዋል መስማት ሌላው የእምነት ተጋድሎ አካል ነው፡፡ 
የመንግሥትን ቃል ሰምቶ በማያስተውል ሁሉ፥ ክፉው ይመጣል፥ በልቡ የተዘራውንም ይነጥቃል፤ በመንገድ ዳር የተዘራው ይህ ነው። ማቴዎስ 13፡18-19 
3.     በክርስቶስ ኢየሱስ በመስቀል ላይ የተሰራልንን መብታችንንና ጥቅማችንን ከመፅሃፍ ቅዱስ ውስጥ ፈልገን ማግኘትና መረዳት የእምነት እርምጃ ነው፡፡ 
የእምነትህም ኅብረት፥ በእኛ ዘንድ ያለውን በጎ ነገር ሁሉ በማወቅ፥ ለክርስቶስ ኢየሱስ ፍሬ እንዲያፈራ እለምናለሁ፤ ፊልሞና 1፡6 
4.     ራሳችንን በቃሉ እውነት ከባቢ ውስጥ ለመጠበቅ ቃሉን ማሰላለስ የእምነት አንዱ ተጋድሎ ነው፡፡   
የዚህ ሕግ መጽሐፍ ከአፍህ አይለይ፥ ነገር ግን የተጻፈበትን ሁሉ ትጠብቅና ታደርግ ዘንድ በቀንም በሌሊትም አስበው፤ የዚያን ጊዜም መንገድህ ይቀናልሃል ይከናወንልሃልም። ኢያሱ 1፡8 
5.     የእግዚአብሄርን ቃል በነገራችን ላይ መናገር ነው፡፡ የአመንነውን የእግዚአብሄር ቃል መናገር በእምነት ውጤት የማግኛ መንገዱ ነው፡፡ ነገር ግን፦ አመንሁ ስለዚህም ተናገርሁ ተብሎ እንደ ተጻፈ ያው አንዱ የእምነት መንፈስ ስላለን፥ እኛ ደግሞ እናምናለን ስለዚህም እንናገራለን፤ 2ኛ ቆሮንቶስ 4፡13 
6.     ልባችንን ከጥርጥር መጠበቅ ሌላው የእመነት እርምጃ ነው፡፡ በልባችን ያለው የእምነት ቃል በጥርጥር ሃሳብ እንዳይበረዝ ፍርሃትንና ጥርጥርን የሚያመጡትን ነገሮች አለማስተናገድ የእምነት ተጋድሎ ክፍል ነው፡፡     
እውነት እላችኋለሁ፥ ማንም ያለው ነገር እንዲደረግለት ቢያምን በልቡ ሳይጠራጠር፥ ይህን ተራራ፦ ተነቅለህ ወደ ባሕር ተወርወር ቢል ይሆንለታል። ማርቆስ 11፡23 
ኢየሱስ ግን ሰምቶ፦ አትፍራ፤ እመን ብቻ ትድንማለች ብሎ መለሰለት። ሉቃስ 8፡50 
7.     የእግዚአብሄርን ቃል ካደረግን በኋላ መፅናት የእምነት ተጋድሎ ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል በማድረግ መፅናት መቀጠል የእምነት ገድል የሚጠይቀው ወሳኝ ነገር ነው፡፡ 
እንግዲህ ታላቅ ብድራት ያለውን ድፍረታችሁን አትጣሉ። የእግዚአብሔርን ፈቃድ አድርጋችሁ የተሰጣችሁን የተስፋ ቃል እንድታገኙ መጽናት ያስፈልጋችኋልና። ዕብራውያን 10፡35-36
መልካሙን የእምነት ገድል ተጋደል፥ 1 ጢሞቴዎስ 612
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#እምነት #ማየት  #ቃል #የእምነትተጋድሎ #የእግዚአብሄርቃል #ቃሉንመስማት #እወጃ #ማስተዋል #ማሰላሰል #መናገር #መፅናት #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ህይወት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ  

No comments:

Post a Comment