Popular Posts

Wednesday, May 17, 2017

እውነትን ተነጋገሩ

እውነትን ላለመናገር ብዙ ጊዜ እንፈተናለን፡፡ በአለም ያለዑ ብዙ ነገሮች እውነቱን እንዳንናገር ያስፈራሩናል፡፡ ነገር ግን እውነትን መናገር የምንፈራበት ዋናውን ምክኒያት ብንረዳ እውነትን በመናገር ነፃ እንወጣለን፡፡
ስለዚህ ውሸትን አስወግዳችሁ፥ እርስ በርሳችን ብልቶች ሆነናልና እያንዳንዳችሁ ከባልንጀሮቻችሁ ጋር እውነትን ተነጋገሩ። ኤፌሶን ሰዎች 4፡25
ሰው በውሸት ይታሰራል እንጂ ነፃ አይወጣም፡፡
የተሰራነውና ዲዛይን የተደረግነው ለእውነት ስለሆነ ውሸትን በተናገርን ቁጥር ህይወታችን እየተወሳሰበ ይሄዳል፡፡ ለውሸት ስላልተሰራንና ካለ ተፈጥሮአችን ስለምንዋሽ የተናገርነውን ውሸት ደግሞ ለመሸፈን በመጨነቅ ሌላ ውሸት መጨመር ግዴታ ነው፡፡
 ውሸት ደግሞ በእኛ ውስጥ ስለሌለ ውሸቱን ለመሸፈን ቀላል አይደለም እጅግ ጭንቅ ነው፡፡ ውሸትን ባበዛን መጠን ደግሞ እስራታችን እየጠበቀ ይሄዳል፡፡ እግዚአብሄር የሰጠን ፀጋ እውነትን ለመኖር ስለሆነ በዋሸን ቁጥር በራሳችን ወጭ ነው የምንዋሸው፡፡
ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ፡፡ ዮሃንስ 1፡14
ውሸትን በተናገርን ቁጥር በእኛ ዘንድ ያለው እውነተኛ መረጃ የሚያስፈልጋቸውን ሰዎች በትክክል የመወሰን እድል እናጨልማለን፡፡ እውነትን ብብነግራቸው ይወስዱት የነበረወን እርምጃ እንዳይወስዱ እናሰናክላቸዋለን፡፡
ለምሳሌ ቀጠሮ ተቀጣጥረን ስንት ሰአት ላይ ትደርሳለህ ተብለን ስንጠየቅ አንድ ሰአት እንምደሚፈጅብን እያወቅን 30 ደቂቃ እንላለን፡፡ በእኛ ጋር ያለውን እውነተኛ መረጃ ባለ መናገራችን ያ ሰው ሰላሳ ደቂቃውን ለማሳለፍ እንዳይወስን እናደርገዋለን፡፡ ባልነው ጊዜ እንደማንመጣ እያወቅን እውነቱን ስላልነገርነው ብቻ እኛን በመጠበቅ ጊዜውን እንዲያባክነው እንፈርድበታለን፡፡
በፍቅር እንያዘው እንጂ እውነትን መናገር ለእኛም ለሚሰሙንም አስፈላጊ ነገር ነው፡፡
ነገር ግን እውነትን በፍቅር እየያዝን በነገር ሁሉ ወደ እርሱ ራስ ወደሚሆን ወደ ክርስቶስ እንደግ፤ ኤፌሶን 4፡15
ስለሚመስለንና በከንቱ ስለምንጓጓ እንጂ እውነት የማንናገርለት ነገር የእኛ አይደለም፡፡ ዋሽተን የምናገኘውን ነገር የእግዚአብሄር በረከት ብለን መጥራት እንችልም፡፡ ዋሽተን በምናገኘው ነገር ላይ ከእግዚአብሄር ዘንድ ድፍረት አይኖረንም፡፡
ውሸት ከሰይጣን ማስፈራሪያ ይመነጫል፡፡ የሚዋሽ ሰው ሰውን የሚፈራ ሰው ነው፡፡
ሰውን መፍራት ወጥመድ ያመጣል፤ በእግዚአብሔር የሚታመን ግን እርሱ ይጠበቃል። ምሳሌ 29፡25
ውሸት የሰይጣን ባህሪ ነው፡፡ በመዋሸታችን ሰይጣን ይከብራል፡፡
እናንተ ከአባታችሁ ከዲያብሎስ ናችሁ የአባታችሁንም ምኞት ልታደርጉ ትወዳላችሁ። እርሱ ከመጀመሪያ ነፍሰ ገዳይ ነበረ፤ እውነትም በእርሱ ስለ ሌለ በእውነት አልቆመም። ሐሰትን ሲናገር ከራሱ ይናገራል፥ ሐሰተኛ የሐሰትም አባት ነውና። ዮሃንስ 8፡44
ስጋችንን በመጎሸም ከጥቂት ጀምረን እውነትን መናገር መማር አለብን፡፡ እውነትን ለመናገር ራሳችንን ማስለመድ አለብን፡፡
ነገር ግን ለዚህ ዓለም ከሚመችና የአሮጊቶችን ሴቶች ጨዋታ ከሚመስለው ተረት ራቅ። እግዚአብሔርን ለመምሰል ግን ራስህን አስለምድ። 1ኛ ጢሞቴዎስ 4፥7
ስለዚህ ውሸትን አስወግዳችሁ፥ እርስ በርሳችን ብልቶች ሆነናልና እያንዳንዳችሁ ከባልንጀሮቻችሁ ጋር እውነትን ተነጋገሩ። ኤፌሶን 4፡25
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ውሸት #ሀሰት #ሰይጣን #ዲያቢሎስ #ጠላት #ማታለል #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #መናገር #ፅናት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment