Popular Posts

Wednesday, May 24, 2017

40 የእምነት ጥቅሞች (ክፍል አንድ) ዕብራውያን 11፡1-20

እምነት በተፈጥሮአዊ አይናችን የማናየውን ተስፋ ለማስረገጥ ይጠቅማል፡፡ እምነት በተፈጥሮ አይናችን የማናየውን ነገር የሚያስረዳ ነው፡፡
እምነትም ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረግጥ፥ የማናየውንም ነገር የሚያስረዳ ነው። ዕብራውያን 11፡1
እምነት እውነተኛ የእግዚአብሄር ምስክርነት እንዲኖረን ያደርጋል፡፡
ለሽማግሌዎች የተመሰከረላቸው በዚህ ነውና። ዕብራውያን 11፡2
የአለምን አጀማመር አፈጣጠር የምንረዳው በእምነት ብቻ ነው ፡፡ የሚታየው ነገር ሁሉ ከማይታየው መንፈሳዊ አለም እንደመጣ ለመረዳት እምነት ወሳኝ ነው፡፡
ዓለሞች በእግዚአብሔር ቃል እንደ ተዘጋጁ፥ ስለዚህም የሚታየው ነገር ከሚታዩት እንዳልሆነ በእምነት እናስተውላለን።ዕብራውያን 11፡3
እግዚአብሄር የሚቀበለውን መስዋእት የምናቀርበው በእምነት ነው፡፡ 
አቤል ከቃየል ይልቅ የሚበልጥን መሥዋዕት ለእግዚአብሔር በእምነት አቀረበ፥ በዚህም፥ እግዚአብሔር ስለ ስጦታው ሲመሰክር፥ እርሱ ጻድቅ እንደ ሆነ ተመሰከረለት፤ ሞቶም ሳለ በመሥዋዕቱ እስከ አሁን ይናገራል።ዕብራውያን 11፡4
ከተፈጥሮአዊ ነገር በላይ ከፍ ብለን በተፈጥሮአዊ ነገር ሳንያዝና ሳንወሰን እንድንኖር የሚያደርገን እምነት ብቻ ነው፡፡
ሄኖክ ሞትን እንዳያይ በእምነት ተወሰደ፥ እግዚአብሔርም ስለ ወሰደው አልተገኘም። ሳይወሰድ እግዚአብሔርን ደስ እንዳሰኘ ተመስክሮለታልና፤ ዕብራውያን 11፡5
እምነት ከእግዚአብሄር ጋር ያለን ግንኙነት እንዲሰምርና ጌታን ለማስደሰት ይጠቅማል፡፡ እምነት ከእግዚአብሄር ዋጋን ያሰጠናል፡፡
ያለ እምነትም ደስ ማሰኘት አይቻልም፤ ወደ እግዚአብሔር የሚደርስ እግዚአብሔር እንዳለ ለሚፈልጉትም ዋጋ እንዲሰጥ ያምን ዘንድ ያስፈልገዋልና።ዕብራውያን 11፡6
እምነት በእግዚአብሄር ዘንድ ተቀባይነትን ይሰጠናል፡፡
ኖኅ ገና ስለማይታየው ነገር ተረድቶ እግዚአብሔርን እየፈራ ቤተ ስዎቹን ለማዳን መርከብን በእምነት አዘጋጀ፥ በዚህም ዓለምን ኰነነ፥ በእምነትም የሚገኘውን ጽድቅ ወራሽ ሆነ። ዕብራውያን 11፡7
በምንም ሁኔታ ውስጥ እግዚአብሄርን እንድንታዘዝ እምነት ይጠቅማል፡፡
አብርሃም የተባለው ርስት አድርጎ ሊቀበለው ወዳለው ስፍራ ለመውጣት በእምነት ታዘዘ፥ ወዴትም እንደሚሄድ ሳያውቅ ወጣ። ዕብራውያን 11፡8
እምነት የተስፋ ቃላችንን በመመልከት የዛሬን መከራ እንድንንቅና እንድንታገስ ያደርገናል፡፡
ለእንግዶች እንደሚሆን በተስፋ ቃል በተሰጠው አገር በድንኳን ኖሮ፥ ያን የተስፋ ቃል አብረውት ከሚወርሱ ከይስሐቅና ከያዕቆብ ጋር፥ እንደ መጻተኛ በእምነት ተቀመጠ፤ ዕብራውያን 11፡9
እምነት የእግዚአብሄርን የተስፋ ቃል በትግስት እንድንጠብቅ ጉልበት ይሆነናል፡፡
መሠረት ያላትን፥ እግዚአብሔር የሠራትንና የፈጠራትን ከተማ ይጠብቅ ነበርና።ዕብራውያን 11፡10
እምነት የማይቻል ነገር እንድናደርግ ከተፈጥሮ በላይ የሆነን አቅምን ይሰጠናል፡፡
ተስፋ የሰጠው የታመነ እንደ ሆነ ስለ ቈጠረች፥ ሣራ ራስዋ ደግሞ ዕድሜዋ እንኳ ካለፈ በኋላ ዘርን ለመፅነስ ኃይልን በእምነት አገኘች። ዕብራውያን 11፡11
እምነት ከሞተ ነገር ውስጥ ህይወት እንዲወጣና እንዲበዛ ያስችላል፡፡
ስለዚህ ደግሞ በብዛታቸው እንደ ሰማይ ኮከብ እንደማይቈጠርም በባሕር ዳር እንዳለ አሸዋ የነበሩት የሞተን ሰው እንኳ ከመሰለው ከአንዱ ተወለዱ። ዕብራውያን 11፡12
እምነት በዚህ አለም እንግዳ ሆነን እንድንኖር ያስችለናል፡
እነዚህ ሁሉ አምነው ሞቱ፥ የተሰጣቸውን የተስፋ ቃል አላገኙምና፤ ዳሩ ግን ከሩቅ ሆነው አዩትና ተሳለሙት፥ በምድሪቱም እንግዶችና መጻተኞች እንዲሆኑ ታመኑ። ዕብራውያን 11፡13
እምነት ከእግዚአብሄር የሆነውን እውነተኛውን ነገር እንድንፈልግ ያፀናናል፡፡
እንዲህ የሚሉት ለእነርሱ የሚሆነውን አገር እንዲፈልጉ ያመለክታሉና። ያን የወጡበትን አገር አስበው ቢሆኑ፥ ሊመለሱ ጊዜ በሆነላቸው ነበር፤  ዕብራውያን 11፡14-15
እምነት ልባችን መዝገባችን ባለበት በሰማይ እንዲሆን ያስችላል፡፡  
አሁን ግን የሚበልጠውን እርሱም ሰማያዊ አገር ይናፍቃሉ። ስለዚህ እግዚአብሔር አምላካቸው ተብሎ ሊጠራ በእነርሱ አያፍርም፥ ከተማን አዘጋጅቶላቸዋልና። ዕብራውያን 11፡16
እምነት ከእኛ ችሎታ ያለፈ መስዋእትን እንድናቀርብና ለእግዚአብሄር ሙሉ ለሙሉ እንድንሰጥ ያደርገናል፡፡
አብርሃም በተፈተነበት ጊዜ ይስሐቅን በእምነት አቀረበ፥ የተስፋን ቃል የተቀበለው፦ በይስሐቅ ዘር ይጠራልሃል የተባለለት እርሱም አንድ ልጁን አቀረበ፤ ዕብራውያን 11፡17-18
እምነት እግዚአብሄር ለሞተው ህይወትን እንደሚሰጥ በማመን ከሞት በላይ እንድናስብ ይጠቅመናል፡፡
እግዚአብሔር ከሙታን እንኳ ሊያስነሣው እንዲቻለው አስቦአልና፥ ከዚያም ደግሞ በምሳሌ አገኘው።ዕብራውያን 11፡19
እምነት የእግዚአብሄርን በረከት በሌሎች ላይ እንድናስተላልፍ ያስችለናል፡፡
ይስሐቅ ሊመጣ ስላለው ነገር ያዕቆብንና ዔሳውን በእምነት ባረካቸው። ዕብራውያን 11፡20
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #እምነት #መናገር #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ልብ #እምነት #ቃል #ማሰላሰል #ማድረግ #ሁሉይቻላል #ደስታ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #መናገር #ፅናት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment