Popular Posts

Tuesday, May 30, 2017

የባህሪ ውበት

እግዚአብሄር የፈጠረን በመልኩና በአምሳሉ ነው፡፡ እግዚአብሄርን በምድር ላይ የፈጠረን በባህሪው እግዚአብሄርን በምድር ላይ እንድንወክለው ነው፡፡   
እግዚአብሄር በኢየሱስ የመስቀል ስራ የሃጢያት እዳችንን ሁሉ ሲከፍል እንደገና ልጆቹ እንድንሆንና ይእግዚአብሄርን ባህሪ በምድር ላይ እንድናንፀባርቅ ነው፡፡
በእግዚአብሄር ቤተሰብ ተቀባይነት አግኝተናል፡፡ በባህሪ ስናድግ ደግሞ እግዚአብሄርን በሙላት እንወክለዋለን፡፡ የህፃንነትን ባህሪ ሽረን በክርስቶስ ባህሪ ስንገለጥ ለብዙዎች በረከት እንሆናለን፡፡
ልጅ ሳለሁ እንደ ልጅ እናገር ነበር፥ እንደ ልጅም አስብ ነበር፥ እንደ ልጅም እቈጥር ነበር፤ ጎልማሳ ሆኜ ግን የልጅነትን ጠባይ ሽሬአለሁ። 1ኛ ቆሮንቶስ 13፡11
እግዚአብሄር ደግሞ የመርህ አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሄር የሰጠንን ነገር አንድናባክነው አይፈልግም፡፡ እግዚአብሄር ዘይቱን ካፍሰሱ በፊትር ዘይቱ የሚቀመጥበትን ሸክላ መስራት ማደስ ቀዳዳውን መድፈን ይፈልጋል፡፡ የተሰነጠቀና በሚያፈስ እቃ ዘይት ቢጨመርበት ለተፈለገው ያህል ጊዜ ቆይቶ ሊጠውቅም አይችልም፡፡ የተሰነጠቀና የሚያፈስ እቃ ዘይት ቢጨመርበትም ያባክናል፡፡  
እግዚአብሄር ለእኛ ስጦታን ለመስጠት ሰከንድ አይፈጅበትም፡፡ እኛ ግን ባህሪያችንን ለመስራትና በክርስቶስ ባህሪ ለማደግ ወራትና አመታት ይፈጅብናል፡፡  
በክርስቶስ ባህሪ ብዙዎችን እንድንደርስና ለብዙዎች በረከት እንድንሆን ባህሪያችንን የሚሰሩትን ሂደቶች ደስ መሰኘትና መታገስ ይኖርብናል፡፡
ይህም ብቻ አይደለም፥ ነገር ግን መከራ ትዕግሥትን እንዲያደርግ፥ ትዕግሥትም ፈተናን ፈተናም ተስፋን እንዲያደርግ እያወቅን፥ በመከራችን ደግሞ እንመካለን፤ ሮሜ 5፡3-4
ከእግዚአብሄር በምናገኘው በረከትና መጨመር ብቻ ሳይሆን በምናስተዳድርበትን ባህሪ መጎልበት ላይ ማተኮር ይገባናል፡፡ እግዚአብሄር አስተዳዳሪው ሳይሰራ ንብረቱን መስጠት አይፈልግም፡፡ አስተዳዳሪው ሃብቱን የሚጠብቅበት ባህሪ ሳይኖረው ሃብቱ ቢመጣ ከንቱ ነው፡፡
የንጉስ ልጅ ምንም የንጉስ ቤተሰብ ቢሆን ንብረቱን በሚገባ ለማስተዳደር እስኪያድግ ይጠበቃል፡፡ ያላደገ ልጅ ማስተዳደር አይችልም፡፡
ነገር ግን እላለሁ፥ ወራሹ ሕፃን ሆኖ ባለበት ዘመን ሁሉ፥ ምንም የሁሉ ጌታ ቢሆን ከቶ ከባሪያ አይለይም፥ ነገር ግን አባቱ እስከ ቀጠረለት ቀን ድረስ ከጠባቂዎችና ከመጋቢዎች በታች ነው። ገላትያ 4፡1-2
የእግዚአብሔርና የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ባሪያ ያዕቆብ ለተበተኑ ለአሥራ ሁለቱ ወገኖች፤ ሰላም ለእናንተ ይሁን።
እኛ ይበልጥ እንድናገለግለውና ተጨማሪ ሃላፊነቶች እንዲሰጠን ከምንፈልገው በላይ እግዚአብሄር ተጨማሪ ሃላፊነቶች ሊሰጠን በባህሪያችን እስክናድግ እየጠበቀ ነው፡፡ እግዚአብሄር በባህሪያችን ላይ በትጋት እየሰራ ነው፡፡ ከእግዚአብሄር አሰራር ጋር ተባብረን ለብዙዎች በረከት ለመሆን እንሰራ፡፡እንደባህሪ መሰራት ለተጠራንለት ጥሪ ፍፁም የሚያደርግ ነገር የለም፡፡
ወንድሞቼ ሆይ፥ የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ አውቃችሁ፥ ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ እንደ ሙሉ ደስታ ቍጠሩት ትዕግሥትም ምንም የሚጎድላችሁ ሳይኖር ፍጹማንና ምሉዓን ትሆኑ ዘንድ ሥራውን ይፈጽም። ያዕቆብ 1፡2-3
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #የመንፈስፍሬ #ፍቅር #ሰላም #ደስታ #ዘር #ባህሪ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #የእግዚአብሄርህይወት #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #በጎነት #የዋሃት #ራስንመግዛት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment