Popular Posts

Wednesday, August 24, 2016

ጥላቻ ከእግዚአብሄር አይደለም

ሰሞኑን በተነሱት የብሄር ውዝግቦች ጥላቻን የሚቀሰቅሱ የተለያዩ ንግግሮች በማህበራዊ መገናኛዎች ስንሰማ ቆይተናል፡፡ በአንድ በኩል ሰዎች ምን ያህል በጥላቻ እስራት ውስጥ እንዳሉና እንደዚህም የሚያስብ ሰው አለ እንዴ ብለን እንድንገረም አድርጎናል፡፡
መገንዘብ ያለብን ነገር ይህ የጥላቻ ንግግር የራሱ የተለየ አላማ እንዳለው ነው፡፡ ይህ የጥላቻ ንግግር አላማው እኛንም በተመሳሳይ የዘር ጥላቻ ውስጥ መክተትና እኛንም እስራት ውስጥ መክተት ነው፡፡
ይህን የዘር ጥላቻ ያስተላለፉት በጥላቻ እስራት ውስጥ እንዳሉ ባይገነዘቡትም እስራት ውስጥ ናቸው፡፡ በእነርሱ ከመናደድ ይልቅ ልናዝንላቸው ይገባል፡፡
የጥላቻ ንግግሩ አላማው እኛንም ወደዚህ ጥላቻ ውስጥ መክተትና በጥላቻ እስራት ውስጥ ያሉትን ሰዎች ቁጥር ማሳደግ ነው፡፡ ከጥላቻ ብቸኛው ተጠቃሚ ሰይጣን ነው፡፡ በጥላቻ ሌላውን በመግደል ማንም ሰው አይጠቀምም፡፡ በተለይ በጥላቻ ውስጥ ያለው ሰው ዋነኛ ተጎጂ ነው፡፡ ምክኒያቱም ጥላቻ ሌላውን ይገድልኛል ብሎ ራስ መርዝ እንደ መጠጣት ነው፡፡
በፍቅር የሚኖሩ ሰዎች ለሰይጣን በር እንደሚዘጉበትና በምህረትና በይቅርታ የሚመላለሱ ሰዎች ሰይጣን እንዳይሰራ ሽባ እንደሚያደርጉት ሁሉ በጥላቻ የተሞሉ ሰዎች ሰይጣን በምድር ላይ ስራውን እንዲሰራ ምቹ ሁኔታን ይፈጥሩለታል፡፡ የሰይጣን አላማው በጥላቻ የተሞሉ ሰዎችን መጠቀም ብቻ ግን አይደለም፡፡
ስራውን ለማስፋፋት የሚጠሉትን ሰዎች ጥላቻቸውን ማብዛት የሰይጣን ሌላው አላማው ነው፡፡ እንዲሁም ተጨማሪ የሚጠሉ ሰዎችን መመልመል ስራውን ለማስፋፋት ይረዳዋል፡፡
የጥላቻን ንግግር ሰምተው ጥላቻ ውስጥ የሚገቡትን በማጥመድ ብቻ ነው ሰይጣን የጥላቻ ስራውን በምድር ላይ የሚያስፋፋው፡፡በጥላቻ የተሞላ ሰው ደግሞ ምንም አይነት የክፋት ስራ ሊሰራ ይችላል፡፡
ነገር ግን መራራ ቅንዓትና አድመኛነት በልባችሁ ቢኖርባችሁ፥ አትመኩ በእውነትም ላይ አትዋሹ። ይህ ጥበብ ከላይ የሚወርድ አይደለም፤ ነገር ግን የምድር ነው፥ የሥጋም ነው፥ የአጋንንትም ነው፤ ቅንዓትና አድመኛነት ባሉበት ስፍራ በዚያ ሁከትና ክፉ ስራ ሁሉ አሉና። ያዕቆብ 3፡14-16
የሰይጣን አላማው የጥላቻ ንግግር አድራጊውንም እኛንም ሰሚዎቹን መግደል ነው፡፡ ሰይጣን የጥላቻ ንግግር ያደረገውን ሰው እንዳገኘው ያውቃል፡፡ ሰይጣን በዚህ የጥላቻ ንግግር ግቡ እኛንም እንድንጠላ መገፋፋትና ለሰይጣን የግድያ ዘር ለም መሬት እንድንሆንለት ነው፡፡
እኛ ግን ይህን የጥላቻ ግብዣ አንቀበልም፡፡ እንዲያውም በጥላቻ ለተያዙት እንራራለን፡፡
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
#ጥላቻ #ፍቅር #ምህረት #ይቅርታ #እምነት #ፀሎት #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ህይወት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment