Popular Posts

Wednesday, August 17, 2016

የምትሠሩልኝ ቤት ምን ዓይነት ነው? ይላል እግዚአብሄር

እግዚአብሄር ሰውን የፈጠረው ከእርሱ ጋር ህብረት ማድረግ ፈልጎ ነው፡፡ እግዚአብሄር ሰውን በመልኩና በአምሳሉ የፈጠረው ህብረታቸው የተሳካ እንዲሆን ነው፡፡ ሰው በሃጢያት ከመውደቁ በፊት ከእግዚአብሄ ጋር የተሳካ ህብረትና ግንኙነት ነበረው፡፡ ሰው ግን እግዚአብሄር ላይ ሲያምፅና በሃጢያት ሲወድቅ ከእግዚአብሄር ጋር ያለው ግንኙነት ተቋረጠ፡፡
አሁንም ቢሆን ግን የእግዚአብሄር አላማ ከሰዎች ጋር ህብረትና ማድረግ ነው፡፡ ሰው በትህትና ከኖረ እግዚአብሄር ሁሌ ከሰው ጋር ህብረት መድረግ ይፈልጋል፡፡ እግዚአብሄር ከምንሰራለት ምንም ቤት በላይ የትሁት ልብ ስጦታችን ወደ እኛ እንዲመለከት ያደርገዋል፡፡
ሰዎች ሊያስደስቱት ከሚያደርጉለት ሃይማኖታዊ እንቅስቃሴ በላይ እግዚአብሄር ወደ ትሁት ሰው እንደሚመለከት ቃሉ ይናገራል፡፡ እግዚአብሄር ታላቅ ነው፡፡ እግዚአብሄር በሰዎች እጅ በተሰራ ቤት ውስጥ አይኖርም፡፡ እግዚአብሄር ወደ ትሑትና መንፈሱም ወደ ተሰበረ ሰው ግን ይመለከታል፡፡ እግዚአብሄር በትሁት ሰው መኖር ይፈልጋል፡፡
እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ሰማይ ዙፋኔ ነው፥ ምድርም የእግሬ መረገጫ ናት፤ የምትሠሩልኝ ቤት ምን ዓይነት ነው? የማርፍበትስ ስፍራ ምንድር ነው? እነዚህን ሁሉ እጄ ሠርታለችና እነዚህ ሁሉ የእኔ ናቸው፥ ይላል እግዚአብሔር፤ ነገር ግን ወደዚህ ወደ ትሑት፥ መንፈሱም ወደ ተሰበረ፥ በቃሌም ወደሚንቀጠቀጥ ሰው እመለከታለሁ። ኢሳይያስ 66፡1-2
እኛም አገልጋዮች ለእግዚአብሄር ቤት መስራት ከፈለግን በወርቅ የተንቆጠቆጠ ቤት ከመስራት ይልቅ ትሑት፥ መንፈሱም የተሰበረ፥ በቃሉም የሚንቀጠቀጥን ሰው ለእግዚአብሄር መስራትና ማቅረብ ይበልጣል፡፡
እግዚአብሄር እኛን በመልኩና በአምሳሉ የፈጠረን ከእርሱ ጋር ህብረት የሚያደርግ ፍጡር ፈልጎ ነው፡፡ እግዚአብሄር በመልኩና በአምሳሉ የፈጠረን እርሱን እንድንረዳውና ሙሉ ለሙሉ በምድር ላይ እንድንወክለው ነው፡፡ እግዚአብሄር ምንም ሳይሰስት በመልኩና በአምሳሉ የፈጠረን በእኛ ሊወጣና ሊገባ ፣ በእኛ አልፎ ሌሎችን ሊናገርና በእኛ ተጠቅሞ ሌሎችን ሊደርስ ስለፈለገ ነው፡፡
ስለሌሎች ነገሮች ሁሉ ሲናገር "እነዚህ ሁሉ የእኔ ናቸው፥ ይላል እግዚአብሔር" የእርሱ ሊያደርገው የሚፈልገው አንድና ብቸኛ ነገር ሰውን ነው፡፡ ሊማርከውና የእርሱ ሊያደርገው የሚፈልገው የሰውን ልብ ነው፡፡ የእርሱ ሊያደርገው የሚፈልገው የሰውን ፈቃድ ነው፡፡ መጥቶ ሊኖርበት የሚፈልገው ትሁትን ልብ ነው፡፡
እግዚአብሄር የሚፈልገው ለቃሉ በህይወቱ የመጀመሪያውን ስፍራ የሚሰጠውን ሰው ነው፡፡ እግዚአብሄርን የሚማርከው ቃሉን ለማድረግ በተጠንቀቅ የሚሰማውን ሰው ነው፡፡ እግዚአብሄር የሚያርፈውና የሚኖረው ለእግዚአብሄር ቃል የዋህና ትሁት በሆነ ሰው ውስጥ ነው፡፡
ነገር ግን ወደዚህ ወደ ትሑት፥ መንፈሱም ወደ ተሰበረ፥ በቃሌም ወደሚንቀጠቀጥ ሰው እመለከታለሁ። ኢሳይያስ 66፡2 ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር share ማድረግ ቢወዱ
#ትህትና #የእግዚአብሔርቤት #በቃሉመንቀጥቀጥ #ህብረት #እምነት #የተሰበረልብ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ህይወት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment