Popular Posts

Thursday, August 11, 2016

የፍቅር ጀብደኛ


ፍቅር የጀግኖች ነው ፡፡ ፍቅር ለአላፊ አግዳሚው ሁሉ አይደለም ፡፡ ፍቅር የምንማረው የምንሰለጥንበት ነገር እንጂ እንደው በድንገት የምንወለድበት ወይም በአጋጣሚ ራሳችንን የምናገኝበት ባህሪ አይደለም፡፡ 
 
ፍቅር ተራ አይደለም፡፡ የፍቅር ህይወት እንደ ድንገት የሚኖሩት ህይወት ሳይሆን የፍቅርን ክብሩን አይተን ራሳችንን የምንሰጠው ነገር ነው፡፡ ፍቅር ከእኛ የተለዩትን ሰዎች በመረዳት ራስን ከእነርሱ ጋር ማስተባበር ይጠይቃል፡፡ 
 
ፍቅር ለሁሉ ሰው አይደለም፡፡ የፍቅር ህይወት በአጋጣሚ የሚከሰት ክስተት ሳይሆን ተወስኖና የሚገባበትና የሚቆይበት የውሳኔ ጉዞ ነው፡፡ የፍቅር ህይወት ሰነፎች ፀንተው የሚቆሙበት /ሰርቫይቭ/ የሚያደርጉበት የአኗኗር መንገድ አይደለም፡፡ 
 
ፍቅር ለሰነፎች አይደለም፡፡ ፍቅር እኛን የማይመስሉንን ሰዎች ለመረዳት በትጋት ጥረት ማድረግን ይጠይቃል፡፡ ፍቅር ለደካሞችና ለልፍስፍሶች አይደለም ፍቅር ትግስታችንን ሲፈተን ፀንተን መቆምን የሚጠይቅ ጀብድ ነው፡፡ የፍቅር ህይወት ለለስላሶች አይደለም በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ በሰጡት ቃል ላይ ፀንቶ መቆምን የሚጠይቅ የከበረ ህይወት ነው፡፡ 
 
የፍቅር ህይወት ሌሎች ምክኒያቶች ሁሉ ሲያልቁ ለፍቅር ብቻ ብለን በትግስት የምንፀናበት የእውነተኝነት ፈተና ነው፡፡ ፍቅር ሰዎችን በደስታ ጊዜ ብቻ ሳይሆን በድካማቸው ለመሸከም የሚወሰን የክብር ውሳኔ ነው፡፡ 
 
ፍቅር ቀጥታ መስመር አይደለም፡፡ ፍቅር ብዙ ውጣ ውረዶችን ማለፍ ይጠይቃል፡፡ ፍቅር ስሜት ብቻ አይደለም፡፡ ተለዋዋጭ የሆነውን ስሜታችንን ሳንሰማ ስሜትን ዋጥ አድርጎ በውሳኔ መቆምን ይጠይቃል፡፡ 
 
ፍቅር ለትቢተኞች አይደለም፡፡ ፍቅር ሌላውን እንደሚሻል በመቁጠር በትህትና የሚኖርበት ኑሮ ነው፡፡ ፍቅር ለራስ ወዳዶች አይደለም፡፡ ፍቅር ሌላውን በመጥቀም የሚደሰቱ ፣ በሌላው ህይወት ላይ ዋጋን ለመጨመር የሚፈልጉ ፣ ለሌላው ለመኖር የሚወስኑ ከራስ ወዳድነት ከፍ ያለ የህይወት ዘይቤ ያላቸው ሰዎች የኑሮ መንገድ ነው፡፡ 
 
ፍቅር ምስኪን እኔ ለሚሉ ሰዎች አይደለም፡፡ ነገር ግን አለኝ ፣ ሙሉ ነኝ ፣ ከኔ አልፎ ለሌላው የሚጠቅም ነገር አለኝ ለሚሉ ሰዎች ነው፡፡ ፍቅር በሌላው እጠቀማለሁ ሳይሆን ሌላውን እጠቅማለሁ ለሚሉ ለደፋር ሰዎች ነው፡፡ 
 
ፍቅር ለማይረኩ ሁሌ ጎዶሎነታቸውን ለሚሰሙ ሰዎች አይደለም፡፡ ፍቅር ባላቸው ነገር ለሚረኩ ፡ ያለኝ ይበቃኛል ለሚሉ እንዲያውም ልሰጥና ላካፍል የምችለው ነገር አለኝ ብለው ለሚያምኑና ልባቸው ለሞላ ሰዎች ነው፡፡ 
 
ፍቅር እኛን ለማይወዱንና ለሚጠሉን ሰዎች በልባችን ስፍራን የማዘጋጀት የሰፊ ልባሞች ህይወት ነው፡፡ ፍቅር ሃይል አለን ብለን ሃይላችንን ለክፋት ላለመጠቀም የምናደርገው የራስን የመግዛት የጀግንነት ህይወት ነው፡፡ 
 
ፍቅር አድቬንቸር ነው፡፡ ፍቅር ጀብድ ነው፡፡ ፍቅር ጀግንነት ነው 
 
#ፍቅር #መስጠት
#ፍቅር #ጀብደኛ
#ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #የእግዚአብሄርቃል #የእግዚአብሔርፈቃድ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment