Popular Posts

Friday, January 5, 2018

እንደ ሰው ልማድ አንዋጋም

መጋደላችን ከደምና ከሥጋ ጋር አይደለምና፥ ከአለቆችና ከሥልጣናት ጋር ከዚህም ከጨለማ ዓለም ገዦች ጋር በሰማያዊም ስፍራ ካለ ከክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት ጋር ነው እንጂ። ኤፌሶን 6፡12
በሰው ልማድ ምንም እንኳ የምንመላለስ ብንሆን፥ እንደ ሰው ልማድ አንዋጋም፤ የጦር ዕቃችን ሥጋዊ አይደለምና፥ ምሽግን ለመስበር ግን በእግዚአብሔር ፊት ብርቱ ነው፤ የሰውንም አሳብ በእግዚአብሔርም እውቀት ላይ የሚነሣውን ከፍ ያለውን ነገር ሁሉ እናፈርሳለን ለክርስቶስም ለመታዘዝ አእምሮን ሁሉ እንማርካለን፥ 2ኛ ቆሮንቶስ 10፡3-5
ከምናስበው በላይ ብዙ ነገሮች መንፈሳዊ ናቸው፡፡ የሰይጣን መንፈሳዊ አለም በክፋት ይሰራል፡፡ መፅሃፍ ቅዱስ ሌባው ሊሰርቅ ሊያርድና ሊያጠፋ እንደሚመጣ ይነግረናል፡፡
ሌባው ሊሰርቅና ሊያርድ ሊያጠፋም እንጂ ስለ ሌላ አይመጣም፤ እኔ ሕይወት እንዲሆንላቸው እንዲበዛላቸውም መጣሁ። ዮሃንስ 10፡10
ጠላት ዲያቢሎስ አያርፍም ሊሰርቅ ሊያርድና ሊያጠፋ ዙሪያችንን ይዞራል፡፡
ሌባው ሊሰርቅና ሊያርድ ሊያጠፋም እንጂ ስለ ሌላ አይመጣም፤ እኔ ሕይወት እንዲሆንላቸው እንዲበዛላቸውም መጣሁ። ዮሃንስ 10፡10
ሰይጣን እኛን ለማጥቃት ሰዎችን ይጠቀማል፡፡ ጴጥሮስን ተጠቅሞ በሰው ሃሳብ ሊያጠቃው የመጣውን ዲያቢሎስ ኢየሱስ ለይቶ አወቀው፡፡ ኢየሱስ በጊዜው ጠላት ከተጠቀመበት ከጴጥሮስ ላይ አይኑን እንስቶ የዚህ የክፉ ሃሳብ ምንጩን ዲያቢሎስ እንደሆነ ሲናገር እንመለከታለን፡፡
ጴጥሮስም ወደ እርሱ ወስዶ፦ አይሁንብህ ጌታ ሆይ፤ ይህ ከቶ አይደርስብህም ብሎ ሊገሥጸው ጀመረ። እርሱ ግን ዘወር ብሎ ጴጥሮስን፦ ወደ ኋላዬ ሂድ፥ አንተ ሰይጣን፤ የሰውን እንጂ የእግዚአብሔርን አታስብምና ዕንቅፋት ሆነህብኛል አለው። ማቴዎስ 16፡22-23
ብዙ ጊዜ ግን አይናችንን ከጠላታችን ዲቢሎስ ላይ አንስተን እርሱ ለጥፋት በሚጠቀምባቸው ሰዎች ላይ ለማድረግ እንፈተናለን፡፡  
በመጠን ኑሩ ንቁም፥ ባላጋራችሁ ዲያብሎስ የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሣ አንበሳ ይዞራልና፤ በዓለም ያሉት ወንድሞቻችሁ ያን መከራ በሙሉ እንዲቀበሉ እያወቃችሁ በእምነት ጸንታችሁ ተቃወሙት። 1ኛ ጴጥሮስ 5፡8-9
እንደ እውነቱ ከሆነ እኛ የሰው ጠላት የለንም፡፡ ጠላታችን አንዱ ዲያቢሎስ ነው፡፡ እውነት ነው ሰይጣን የሰዎችን አእምሮ ተጠቅሞ እነርሱንም እኛንም ለመስረቅ ለማረድና ለማጥፋት ይመጣል፡፡
ስለዚህ የእኛ መጋደል ከደምና ከስጋ ጋር አይደለም፡፡ ከደምና ከስጋ ጋር የምንጋደል ከሆንን በተሳሳተ ገድል ህይወታችንን እያባከንን ነው፡፡ መጋደላችን ከሰው ጋር በፍፁም አይደለም፡፡
መጋደላችን ከክፉ መንፈሳዊ አለም መናፍስት ጋር ነው፡፡ ሰው በራሱ ክፉ አይደለም፡፡ ክፉን ሃሳብ በሰው ውስጥ ልከው ሰው ክፉ እንዲያደርግ የሚያደርጉት የክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት ናቸው፡፡
የሰዎችን ቅንነት የሚያበላሸውን ሰዎች ውስጥ ክፋት የሚጨምረውን ክፋትን የሚያባብሰውን ክፉን በጌታ በኢየሱስ ስም ልንቃወም ይገባናል፡፡  
ነገር ግን እባብ በተንኮሉ ሔዋንን እንዳሳታት፥ አሳባችሁ ተበላሽቶ ለክርስቶስ ከሚሆን ቅንነትና ንጽሕና ምናልባት እንዳይለወጥ ብዬ እፈራለሁ። 2ኛ ቆሮንቶስ 11፡3
ሰዎች አንድ ነገር ሲደርስባቸው እከሌ ነው ብለው ይደመድማሉ ከዚያም መጋደላቸው ከእከሌ ጋር ይሆናል፡፡ ሰዎች ስጋ ለባሽን እንጂ ከዚያ አልፈው ስጋ ለባሽን ለክፋት የሚያነሳሳውን ካላዩ እውነተኛ ጠላታቸውን አያውቁም፡፡ ሰዎች ከሰው አልፈው የክፋቱን ምንጭ ክፉ መንፈሳዊ አለምን ካላዩ ኢላማቸውን ይስታሉ፡፡ ሰዎች ግን የክፋትን ምንጭ መንፈሳዊ አለምን ከለዩና ትኩረታቸውን ከስጋ ለባሽ ላይ እንስተው ወደ መንፈሳዊ አለም ካዞሩ ችግሩን ከስሩ በማድረቅ ውጤታማ ይሆናሉ፡፡
አይናችንን ከሰዎች ላይ አንስተን የሚታለሉትን ሰዎች የሚጠቀመውንና ፈቃዱን የሚያስደርጋቸውን ከተቃወምን በሰዎችም ህይወትና በእኛም ህይወት የጠላትን ስራ ማፍረስ እንችላለን፡፡
በእነርሱም፥ በዚህ ዓለም እንዳለው ኑሮ፥ በማይታዘዙትም ልጆች ላይ አሁን ለሚሠራው መንፈስ አለቃ እንደ ሆነው በአየር ላይ ሥልጣን እንዳለው አለቃ ፈቃድ፥ በፊት ተመላለሳችሁባቸው። ኤፌሶን 2፡1
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #እምነት #ፍቅር #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ልብ #የጦርመሳሪያ #ምሽግ #አእምሮ #ሃሳብ #ማታለል #ብርቱ #ተቃወሙት #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #መናገር #ፅናት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment