Popular Posts

Wednesday, January 24, 2018

የፍርሃት መንፈስ አልሰጠንም

እግዚአብሔር የኃይልና የፍቅር ራስንም የመግዛት መንፈስ እንጂ የፍርሃት መንፈስ አልሰጠንምና። 2 ጢሞቴዎስ 17
እግዚአብሄር የሰጠንን ማወቅ እንድንጠብቀው እንድንንከባከበው ያደርገናል፡፡ እግዚአብሄር ያልሰጠንን ማወቅ ደግሞ እንድንቃወመውና እንዳናስተናግደው ያደርገናል፡፡
በህይወታችን በምንም አጋጣሚ ማስተናገድ የሌለብን ነገር ፍርሃትን ነው፡፡ ፍርሃት ከእግዚአብሄር አይደለም፡፡ ፍርሃት ከሰይጣን ነው፡፡ እግዚአብሄር የፍርሃትን መንፈስ አልሰጠንም፡፡
የፍርሃት አላማ ደግሞ እግዚአብሄር ከሰጠን ራእይ ማሰናከልና እና ጌታን ከመከተል ማስቆም ነው፡፡
እግዚአብሄር የሃይል መንፈስ እንጂ የፍርሃት መንፈስ አልሰጠንም፡፡
ፍርሃት እንደማንችል ፣ እንደማንበቃ ፣ እንደማይሳካልንና እንደማይከናወንልን ይነግረናል፡፡ እግዚአብሄር የሰጠን መንፈስ ግን የሃይል መንፈስ ነው፡፡ በምድር ላይ የምንኖረው በእግዚአብሄር በሚያስችል ሃይል ነው፡፡ እግዚአብሄር የሰጠንን ማንኛውንም ሃላፊነት የምንፈፅምበት ሃይል አለን፡፡ የእግዚአብሄርን ሃሳብ ለመፈፅም ከሚያስፈልገን አንድም ፀጋ አይጎድልብንም፡፡
የመለኮቱ ኃይል፥ በገዛ ክብሩና በበጎነቱ የጠራንን በማወቅ፥ ለሕይወትና እግዚአብሔርን ለመምሰል የሚሆነውን ነገር ሁሉ ስለ ሰጠን፥ በእግዚአብሔርና በጌታችን በኢየሱስ እውቀት ጸጋና ሰላም ይብዛላችሁ። 2 ጴጥሮስ 1፡2-3
እግዚአብሄር የፍቅር መንፈስ እንጂ የፍርሃት መንፈስ አልሰጠንም፡፡
የሰይጣን አለማ በፍርሃት ራስ ወዳድ እና ስግብግብ እንድንሆን ማድረግ ነው፡፡ የሰይጣነ አላ በፍርሃት ማንንም እንዳንወድ ለማንም እንዳናካፍልና ለራሳችን ብቻ አግበስብሰን እንድንኖር ነው፡፡ የሰይጣነ የፍርሃት አላማው በስስት በማንም ላይ ተፅኖ ሳናደርግ እንድናልፍ ነው፡፡ ሰው ግን የተፈጠረው ሌላውን እንዲወድና እንዲያገለግል ነው፡፡ እግዚአብሄር የሰጠን መንፈስ ከራስ አልፎ ሌላውን የሚደርስ መንፈስ እንጂ በምስኪን እኔ አስተሳሰብ ለራሱ ብቻ ኖሮ የሚያልፍ አይደለም፡
እግዚአብሄር የራስን የመግዛት መንፈስ እንጂ የፍርሃት መንፈስ አልሰጠንም፡፡
እግዚአብሄር ራሳችንን እንድንገዛ መንፈሱን ሰጥቶናል፡፡ ራሳችንን እንገዛ ይሆን ብለን በፍርሃት አንታሰርም፡፡ ሰዎችን ሁሉ የሚያድን የእግዚአብሄር ፀጋ በእኛ ላይ በሃይል እንደሚሰራ እናምናለን፡፡ እግዚአብሄር ያቀደልንን የቅድስና ህይወት መኖር የሚያስችለን ሁሉም ነገር እንደተሰጠን እናምናል፡፡ በሆነው ባልሆነው በመፈራት በቅድስና ተስፋ እንቆርጥም፡፡ አንፈራም እግዚአብሄር የሰጠን ራስን የመግዛት መንፈስን እንጂ የፍርሃትን መንፈስ አይደለም፡፡
ሰዎችን ሁሉ የሚያድን የእግዚአብሔር ጸጋ ተገልጦአልና፤ ይህም ጸጋ፥ ኃጢአተኝነትንና ዓለማዊን ምኞት ክደን፥ የተባረከውን ተስፋችንን እርሱም የታላቁን የአምላካችንንና የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ክብር መገለጥ እየጠበቅን፥ ራሳችንን በመግዛትና በጽድቅ እግዚአብሔርንም በመምሰል በአሁኑ ዘመን እንድንኖር ያስተምረናል፤ ቲቶ 2፡11-13
በሃይማኖት ብትኖሩ ራሳችሁን መርምሩ፤ ራሳችሁን ፈትኑ፤ ወይስ ምናልባት የማትበቁ ባትሆኑ፥ ኢየሱስ ክርስቶስ በእናንተ ውስጥ እንዳለ ስለ እናንተ አታውቁምን? 2ኛ ቆሮንቶስ 13፡5
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ጌታ #ኢየሱስ #ፍቅር #ፍርሃት #ሃይል #ራስንመግዛት #አላማ #መዳን #ነፃነት #ቅድስና #ሰላም #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #ብርሃን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ህይወት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ  #የዋህነት #ንፁህ

No comments:

Post a Comment