Popular Posts

Sunday, June 4, 2023

የአዲስ ኪዳን እና የብሉይ ኪዳን ምሪት ልዩነት



ሰው የተፈጠረው ከእግዚአብሔር ጋር እንዲግባባ በመልኩና በአምሳሉ ነው፡፡ ሰው በሃጢያት ምክኒያት ከእግዚአብሔር ጋር ከተለያየም በኋላ እግዚአብሔር መናገሩን ቀጠለ፡፡

ነገር ግን በብሉይ ኪዳን በሃጢያት ምክኒያት የእግዚአብሔር መንፈስ በሁሉም ሰው ላይ አያርፍም ነበር፡፡ በብሉይ ኪዳን የእግዚአብሔር መንፈስ በነቢያት በካህናት እና በነገስታት ላይ ለስራ ይመጣባቸው ስለዚህ ነበር፡፡ ስለዚህም እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን ለህዝቡ የሚናገረው በነቢያት ካህናት እና ነገስታት በኩል ብቻ ነበር፡፡ እግዚአብሔር ለሁሉም ሰው መናገር ስለማይችል በነቢያት በካህናት እና በነገስታት በኩል ይናገራቸው ነበር፡፡

የብሉይ ኪዳን ህዝቦች እግዚአብሔርን መጠየቅ ሲፈልጉ "የእግዚአብሔርን ቃል የምናገኝበት ነቢይ በዚህ አካባቢ የለምን?"  ብለው በመጠየቅ መሄድ ግዴታቸው ነበር፡፡   

በአዲሱ ኪዳን በክርስቶስ ኢየሱስ የመስቀል ስራ ከእግዚአብሔር ጋር ታርቀናል፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ የዳንን ሁላችን የእግዚአብሔር የቤተሰብ አባላት ሆነናል፡፡ የእግዚአብሔር የንጉስ ካህናት ሆነናል፡፡

እናንተ ግን ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃኑ የጠራችሁን የእርሱን በጎነት እንድትናገሩ የተመረጠ ትውልድ፥ የንጉሥ ካህናት፥ ቅዱስ ሕዝብ፥ ለርስቱ የተለየ ወገን ናችሁ፤1ኛ የጴጥሮስ መልእክት 2፡9

እግዚአብሔር በግላችን ለመስማት የምንችል ነቢያት ተደርገናል፡፡ በአዲስ ኪዳን ሰው እግዚአብሔርን መጠየቅ ከፈለገ በግሉ እግዚአብሔርን ይጠይቃል እንጂ እንደብሉይ ኪዳን የሚጠይቃቸው ነቢያት የሉም፡፡

በአዲስ ኪዳን ሁላችን ውስጥ የእግዚአብሔር መንፈስ በማደሩ ሁላችንም እግዚአብሄርን መስማት እንችላለን፡፡

እናንተም ከቅዱሱ ቅባት ተቀብላችኋል፥ ሁሉንም ታውቃላችሁ። እናንተስ ከእርሱ የተቀበላችሁት ቅባት በእናንተ ይኖራል፥ ማንም ሊያስተምራችሁ አያስፈልጋችሁም፤ ነገር ግን የእርሱ ቅባት ስለ ሁሉ እንደሚያስተምራችሁ፥ እውነተኛም እንደ ሆነ ውሸትም እንዳልሆነ፥ እናንተንም እንዳስተማራችሁ፥ በእርሱ ኑሩ። 1ኛ የዮሐንስ መልእክት 2፡20፣27

በአዲስ ኪዳን "እግዚአብሔር ስለእኔ ምን ይልሃል?" ብሎ መጠየቅ በአዲስ ኪዳን ውስጥ ፈፅሞ የማይገኝ ልምምድ ነው፡፡

በአዲስ ኪዳን ያሉት ነቢያት እግዚአብሔር አስቀድሞ ለእኛ የተናገረውን እግዚአብሔር እንደገለጠላቸው ሊያፀኑ ይችላሉ፡፡ በአዲስ ኪዳን እግዚአብሔር ለእኛ በግላችን ያልተናገረንን ነገር ነቢያት ተናግረው ህይወታችንን በብቸኝነት እንዲመሩት መፍቀድ አደጋ ነው፡፡

በጎቼ ድምኙን ይሰማሉ እንደሚል ከዳንን እና በግ ከሆንን ጌታን እንሰማለን፡፡ ጌታን ካልሰማን ደግሞ ጌታ ኢየሱስን የተቀብለን በግ እንሁን፡፡

በጎቼ ድምፄን ይሰማሉ እኔም አውቃቸዋለሁ ይከተሉኝማል፤ የዮሐንስ ወንጌል 10፡27

አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa


No comments:

Post a Comment