Popular Posts

Thursday, June 22, 2023

የእግዚአብሔርን ድምፅ የምንለይበት መንገድ

 


በምድር ላይ የእግዚአብሔር ድምፅ እንዳለ ሁሉ የእግዚአብሔርን ድምፅ እንዳንሰማ እና እንዳንታዘዝ የሚገዳደር የጠላት የዲያቢሎስ ድምፅ አለ፡፡

የእግዚአብሔርን ድምፅ የምንለየው ድምፁ በጨዋነት ለማቅናት የሆነ ድምፅ መሆኑ ነው፡፡ የጠላት ድምፅ አንተ አትረባም አትጠቅምም ዋጋ የለህም በሚል በማጣጣል ሲመጣ የእግዚአብሄር ድምፅ ግን በማበረታታት ትችላለህ በሚል የአክብሮት አመለካከት ይመጣል፡፡

ፈታኝም ቀርቦ፦ የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህ፥ እነዚህ ድንጋዮች እንጀራ እንዲሆኑ በል አለው። የማቴዎስ ወንጌል 4፡3

ሌላው የእግዚአብሔርን ድምፅ የምናውቀበት መንገድ ድምፁ በደስታ የሚያነሳሳ መሆኑ ነው፡፡ እግዚአብሔር ሲናገር ሰው እግዚአብሔርን ለማስደሰት በራሱ አነሳሽነት የሰማውን ለማድረግ ይቸኩላል እንጂ እግዚአብሔር ሰውን ካለፈቃዱ አያስቸኩልም፡፡

እርሱ ግን ዘወር ብሎ ጴጥሮስን፦ ወደ ኋላዬ ሂድ፥ አንተ ሰይጣን፤ የሰውን እንጂ የእግዚአብሔርን አታስብምና ዕንቅፋት ሆነህብኛል አለው።የማቴዎስ ወንጌል 16፡23

የሰይጣን ድምፅ ሲመጣ ግን ይገፈትራል፡፡ የሰይጣን ድምፅ የእኛን መረዳት አይጠብቅም፡፡ የሰይጣን ድምፅ የእኛን እርምጃ አይጠብቅም፡፡ የሰይጣን ድምፅ አሁን ካላደረከው ያመልጥሃል ብሎ ካለፈቃዳችን እንድናደርገው ያጣድፋል ያስፈራራል ያስቸኩላል፡፡ 

መንጋውን እንደ እረኛ ያሰማራል፥ ጠቦቶቹን በክንዱ ሰብስቦ በብብቱ ይሸከማል፥ የሚያጠቡትንም በቀስታ ይመራል። ትንቢተ ኢሳይያስ 40፡11

የእግዚአብሔር ምሪት አጥብቃችሁ እስክትረዱት ይታገሳችሁዋል፡፡ ባልተረዳችሁት ነገር እርምጃ እንድትወስዱ አይጠብቅባችሁም፡፡ ሰይጣን ግን እንዳያመልጥህ ለማንኛውም አድርገው በል ፍጠንን በማለት ካለፍላጎታቸን ይገፈታትረናል፡፡ 

አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa


No comments:

Post a Comment