Popular Posts

Tuesday, December 5, 2017

የማንነት አንገብጋቢ ጥያቄ ሲመለስ

የማንነት ጥያቄ ወሳኝ ጥያቄ ነው፡፡ የማንነት ጥያቄ መመለስ ሁሉም ባይሆንም አብዛኛው የህይወት ጥያቄ ይመልሳል፡፡ የማንነት ጥያቄ መመለስ እንደ ደረጃችን መኖርን ያስችለናል፡፡ ምክኒያቱም ሰው እንደሚያስበው እንደዚሁ ነውና፡፡
የእግዚአብሄር ልጅ እንደሆነ የሚያስብ እንደ እግዚአብሄር ልጅ ይኖራል፡፡ የእግዚአብሄር ልጅ እንደሆነ የማያስብ የእግዚአብሄር ልጅ እንዳልሆነ ከደረጃ በታች የሆነ የሰው ብቻ ኑሮ ይኖራል፡፡
አንዱ፦ እኔ የጳውሎስ ነኝ፥ ሁለተኛውም፦ እኔ የአጵሎስ ነኝ ቢል ሰዎች ብቻ መሆናችሁ አይደለምን? 1 ቆሮንቶስ 3፡4
የማንነት ጥያቄ የፍጥረት ጥያቄ ነበር፡፡
እግዚአብሄር ሰውን በመልኩና በአምሳሉ ፈጠረው፡፡
እግዚአብሔርም ሰውን በመልኩ ፈጠረ፤ በእግዚአብሔር መልክ ፈጠረው፤ ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው። ዘፍጥረት 1፡27
ሰው እንደተፈጠረው በእግዚአብሄር መልክና አምሳል ይኖር ነበር፡፡ አትብላ የተባለውን በመብላት እግዚአብሄር ላይ በማመፅ በሃጢያት እስከወደቀ ድረስ በእግዚአብሄር ክብር ይኖር ነበር፡፡ ሰው በሃጢያት ሲወድቅ ብቻ ነበር የእግዚአብሄር የእግዚአብሄር ክብር የጎደለው፡፡  
ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል፤ ሮሜ 3፡23
ሰይጣንም በመጀመሪያ ጥቃት የሰነዘረው የሰው የማንነት ምስል ላይ ነው፡፡ የማንነት ምስሉ ከተበላሸ ሰው ይበለሻል፡፡ የማንነት ምስሉ ካልተበላሸ ሰውን ማበላሸት በፍፁም አይቻለም፡፡ የሰው ማንነት መስተካካለ ካለበት የሰው ማንነት ምስል ወደ ቀደመው ወደጥንቱ ምስሉ መመለስና መስተካከሉ አለበት፡፡  
የማንነት ጥያቄ የሰይጣን ፈተና መሳሪያ ነበር
ይህ የማንነት ጥያቄ በኢየሱስም የአገልግሎት ዘመን ቀጥሎዋል፡፡ ሰይጣን ኢየሱስን የፈተነው በማንነት ዙሪያ ነበር፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህ" የሚለው የሰይጣን ንግግር የእግዚአብሄር ልጅ ነኝ ትላለህ እንጂ አይደለህም የሚልን ተዘዋዋሪ መልክት ያስተላልፋል፡፡ 
ፈታኝም ቀርቦ፦ የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህ፥ እነዚህ ድንጋዮች እንጀራ እንዲሆኑ በል አለው። ማቴዎስ 4፡3
የእግዚአብሔር ልጅስ ከሆንህ የሚለው ሌላው ንግግር የሰይጣንን በማንነት ላይ ያነጣጠረ ግልፅ ጥቃትን ያሳያል፡፡
ከዚህ በኋላ ዲያብሎስ ወደ ቅድስት ከተማ ወሰደውና እርሱን በመቅደስ ጫፍ ላይ አቁሞ፦ መላእክቱን ስለ አንተ ያዝልሃል እግርህንም በድንጋይ ከቶ እንዳትሰናከል በእጃቸው ያነሡሃል ተብሎ ተጽፎአልና የእግዚአብሔር ልጅስ ከሆንህ፥ ወደ ታች ራስህን ወርውር አለው። ማቴዎስ 4፡5-6
ሌላው ሰይጣን ያነሳው ጉዳይ የእግዚአብሄር ቃል እውነት አይደለም የሚል መልክትን ያዘለ ነው፡፡ ስለማንነታችን የእግዚአብሄርን ቃል ካላመንን የማመን እድላችንን ጨርሰናል ማለት ነው፡፡ በውስኑ አእምሮዋችን ባንረዳውም እንኳን የእግዚአብሄር ቃል ነህ የሚለንን ነኝ ለማለት ፣ የእግዚአብሄር ቃል አለህ የሚለንን አለኝ ለማለትና የእግዚአብሄር ቃል ታደርጋለህ የሚለንን አደርጋለሁ ለማለት መፍራት የለብንም፡፡ እንዲያውም መፍራት ያለብን የእግዚአብሄር ቃል የማይለንን ለማለት ነው፡፡ የእግዚአብሄር ቃል የሚለንን ማለት ትእቢት ሳይሆን ትህትና ነው፡፡ የእግዚአብሄር ቃል የሚለንን አለማለት ደግሞ ትህትና ሳይሆን ትእቢት ነው፡፡ የሆነውን አይደለሁም ማለት በአጉል ትህትና ከእግዚአብሄር በላይ ፃዲቅ ለመሆን መሞከር ነው፡፡   
ትሕትናንና የመላእክትን አምልኮ እየወደደ፥ ባላየውም ያለ ፈቃድ እየገባ፥ በሥጋዊም አእምሮ በከንቱ እየታበየ ማንም አይፍረድባችሁ። ቆላስይስ 2፡18
ማንነታችንን አውቀን አናውቅም ብንል ስህተተኛ እንሆናለን፡፡ ኢየሱስ ስለማንነቱ እንዲክድና ንስሃ እንዲገባ የወቅቱ የሃይማኖት መሪዎች ሲያዋክበት እናንት የማታውቁትን ነገር አውቃለሁ በማለት እንደምትዋሹ ሁሉ እኔ እንደሆንኩ የማውቀውን ነገር አላውቅም ብል ውሸተኛ እሆናለሁ አላቸው፡፡
አላወቃችሁትምም፥ እኔ ግን አውቀዋለሁ። አላውቀውም ብል እንደ እናንተ ሐሰተኛ በሆንሁ፤ ዳሩ ግን አውቀዋለሁ ቃሉንም እጠብቃለሁ። ዮሃንስ 8፡55
የማንነት ጥያቄ የኢየሱስ አገልግሎት ጥያቄ ነበር
ኢየሱስን ለመውገር የተነሱ የወቅቱ የሃይማኖት መሪዎች ስለማናቸው ሃጢያት ነው የምትወግሩኝ ብሎ በጠየቃቸው ጊዜ የመለሱለት ስለ የትኛውም ሃጢያት ሳይሆን አንተ ሰው ስትሆን የእግዚአብሄ ልጅ ነኝ በማለትህ ነው በማለት ሊገድሉት የሚፈልጉ በማንነት ጥያቄ ዙሪያ እንደሆነ በግልፅ መልሰዋል፡፡
ኢየሱስ፦ ከአባቴ ብዙ መልካም ሥራ አሳየኋችሁ፤ ከእነርሱ ስለ ማናቸው ሥራ ትወግሩኛላችሁ? ብሎ መለሰላቸው። አይሁድም፦ ስለ መልካም ሥራ አንወግርህም፤ ስለ ስድብ፤ አንተም ሰው ስትሆን ራስህን አምላክ ስለ ማድረግህ ነው እንጂ ብለው መለሱለት። ዮሃነስ 10፡32-33
አይሁዳዊያን የእግዚአብሄር ልጅ ነኝ ማለት የአምላከ ቤተሰብ ነኝ ማለት ፣ የነገስታት ቤተሰብ አባል ነኝ ማለትና የአምላክ የቤተሰብ አባል ነኝ ማለት እንደሆነ ጠንቅቀው ያውቃሉ፡፡  
ኢየሱስም እንዲህ ብሎ መለሰላቸው፦ እኔ፦ አማልክት ናችሁ አልሁ ተብሎ በሕጋችሁ የተጻፈ አይደለምን? መጽሐፉ ሊሻር አይቻልምና እነዚያን የእግዚአብሔር ቃል የመጣላቸውን አማልክት ካላቸው፥ የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ ስላልሁ እናንተ አብ የቀደሰውን ወደ ዓለምም የላከውን፦ ትሳደባለህ ትሉታላችሁን?  ዮሃንስ 10፡34-36
የተሃድሶ ጥያቄ የማንነት ጥያቄ ነበር
ማርቲን ሉተር የዛሬ 500 አመት የበተራለት የሰው የማንነት ጥያቄ እና የደህንነት ጥያቄ መልስ ነበር፡፡ በወቅቱ የነበሩ የሃይማኖት መሪዎች ህዝቡ ምንም እንዳይደለ ፣ በነፃ መዳን እንዳደማይችል ፣ ከእግዚአብሄር ጋር በቀጥታ ሊገናኝ የሚችልበት ማንነት እንደሌለው ፣ መፅሃፍ ቅዱስን አንብቦ መረዳት እንዳይችል ፣ ለምንም ነገር ካህን እንደሚያስፈልገው የማንነት ምስሉን አጥፍተውበት በእስራት እና በጨለማ ያኖሩት ነበር፡፡ በወቅቱ የነበሩት የሃይማኖት መሪዎች ማርቲን ሉተር ስለደህንነቱ የእግዚአብሄርን ቃል ተረድቶ ስላስረዳና የእግዚአብሄር ቃል የሚለውን ስላለ እጅግ ያሳድዱት ነበር፡፡  
የማንነት ጥያቄ የእኛም ዘመን ጥያቄ ነው
አሁንም ቢሆን አንገብጋቢው ጥያቄ ይህ የማንነት ጥያቄ ነው፡፡ አሁንም ቢሆን "የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል" 2ኛ ጢሞ 3፡5 የተባሉ ባዶ ሃይማኖተኞችንና የእግዚአብሄርን ቃል የተረዱ ሰዎችን የሚያጋጨው ይህ የማንነት ጥያቄ ነው፡፡ ኢየሱስን እንደ አዳኙ የተቀበለ ሰውን የእግዚአብሄር ቃል ፀድቋል ሲል የዳነ ፃዲቅ ነን ሲል ማን ስለሆንክ ነው የሚል ጥያቄ እና ስደት ይነሳል፡፡ የእግዚአብሄር ልጅ ነን የኢየሱስ ወንድም ነን ስንል በፍፁም ሊሆን አይችልም የሚል ተቃውሞ አለ፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል የሚለንን ለማለት አንፍራ፡፡ የእግዚአብሄር ቃል ያላለንን ለማለት አንድፈር፡፡ የእግዚአብሄር ቃል ያላለንን በማለት ልንስት እንችላለን፡፡  የእግዚአብሄር ቃል ያለንን በማለት ግን ልንስት አንችልም፡፡
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #በክርስቶስ #መልክ #አምሳል #የእግዚአብሄርልጅ #ወዳጅ #የንጉስልጅ #ልጅነት ##መንፈስ #ነፍስ  #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ማየት #የእግዚአብሄርመንግስት #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #አዲስፍጥረት #ክርስቶስ #የእግዚአብሄርቤተሰብ #ማእረግ #ስልጣን #ዳግመኛመወለድ

No comments:

Post a Comment